በኢየሱስ ህይወት ፤ ሥቅለት ና ትንሣኤ ፤ የፍቅርን ኃያልነት እንማራለን – መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

One word frees us of all the weight and pain in life, and that word is Love.

( Socrates )

የሰው ፈጣሪ ና ነፍሱን አስተዳዳሪ እግዚአብሔር ነው ። የሰውን ነፍስ በሲኦል ለማስተዳደር የሚፈልገው ደግሞ ሴጣን ነው ።ይህንን እውነት የገዛ አእምሯችሁ በህሊናችሁ በኩል  ዘወትር ይነግረናል ። የፈጣሪንም ሆነ የሤጣንን መኖር የሚያረጋግጥልን ዘወትር ከጥላቻ ና ፍቅር ጋር እየታገለ የሚኖረው  የገዛ አእምሯችን ነው ። የገዛ አእምሯችን እስከህሊናቸን እንድንሰነበት ያደርገናል ። አልያም ህሊና የሚባለውን የበጎ ነገር ወዳጅ የአእምሮ ክፍል አሶወግዶ መጥፎ ሃሳብን የሚያራምደው የባዶነት ቀፎ አእምሮ ከእና ዘንድ እሥከ ዕለተ ሞታችን እንዲሰነብት ያደርጋል ።

ብታምኑም ባታምኑም በሰው አእምሮ ያለው እውነት ይህ ብቻ ነው ። የሁለት ተቃራኒዎች ትግልና ውጤቱ ነው በየዕለት ኑሯችሁ በአእምሯችሁ አማካኝነት የሚስተናገደው ። የዛሬ እናንተነታችሁ አእምሮችሁ ውሥጥ በሚደረገው የክፋት ሠራዊትና የበጎ ሰራዊት ወይም የፍቅርና የጥላቻ ፍልሚያ ይወሰናል ።  ከላይ እስከታች ፤ ከሊቅ እሥከ ደቂቅ ፤ በዚህ እውነት ውሥጥ ነው የሚያልፈው ። ንጉሥ ይሁን ሌላ ሥም የተሰጠው የአገር መሪ ፤ ተራ ሟች ይሁን ዘላለማዊ ሥም ያለው ፤ ማንም ይሁን ማ በአእምሮ ውሥጥ የሚካሄደውን ጦርነት በመልካም እና በቅን ሃሳብ ድል አድራጊነት እሥካልቋጨ ጊዜ ድረሥ ህሊናውን ቀስ በቀስ በማጣት ባዶ ቀፎ ጭንቅላት ይዞ ዝዋሪ ሆኖ ፣ ህይወቱን በመንቅዥቀዥ ኖሮ  በቁጭት ወደ መቃብር እንደሚወርድ ህይወት በየቀኑ ታሳየናለች ። ከዚህ እረፍተ ቢስ የወከባ እና የመከውከው ኑሮ ፣ እከተለዋለሁ የሚለው ኃይማኖት እንኳ እንደማያድነውም ለተራ ሟቹ ታስገነዝባለች ።

ኃይማኖትህ የሚያድንህ ቅን ፣ በጎ እና ፍቅር የሚገዛህ ሥትሆን ብቻ ነው ። ከሞትክ በኋላ እንኳን ነፍስህ እረፍት የምታገኘው ይቅር በይ እና የሚፀፀት አእምሮ ኖሮህ ከሞትክ ብቻ ነው ።

ሰዎች ሆይ  ! የፈለጋችሁትን ኃይማኖት ተከተሉ ። የምትከተሉት ኃይማኖት የፈጣሪን መኖር የሚያሥገነዝባችሁ በገዛ አእምሯችሁ በኩል ነው ።የገዛ አእምሯችሁ ውሥጥ የፍቅር ና የጥላቻ ትግል በየሰኮንዱ መካሄዱን አሥተውሉ ። አንድ በጎ ሃሳብ በተቃራኒው ሃሳብ ይሞገታል ። በሙግቱም ወይ ተቃራኒው ወይ ደግሞ በጎው አሳብ ያሸንፋል ። ወይ ፍቅር ወይ ጥላቻ አእምሯችሁን ይቆጣጠራል ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ጀዋር እና ኢስላማዊት ኦሮሚያ (ለያሬድ አይቼህ መልስ)

ፍቅር ና ጥላቻ ሁሌም በአእምሯችን  ውስጥ ያለፋታ ይሟገታሉ ።    አውዳሚ ወይም ክፉ አሳብ  እና ገንቢ የሆነ ቅን ሃሳብ ሁሌም በአእምሯችን ውሥጥ መፋለማቸውን እናውቃለን ። በማያቋርጠው የተቃራኒ ሃሳቦች ትግል ፣ ድል አድራጊው   መልካሙ የፍቅር ሃሳብ  የሚያሸንፍ ከሆነ ፤ በየቀኑ መልካም ሰው ሆነን እናድጋለን ። ክፉው እና ጠማማው የጥላቻ ሃሳብ  እያየለ ና ፍቅር እየተዳከመ ከመጣ ደግሞ ፣ በየቀኑ እየሤጠንን ማደጋችን አይቀርምና ለእኛ የክፋታችን ጥግ  ባይታወቀንም እንኳን ፣ ለቅን ሰዎች ጠማማነታችን ከጅምሩ የተሰወረ አይሆንም   ። ለእኛ የማይታወቀን መጥፎው ሃሳብ ወይም ጥላቻ ቅን እና በጎ ሃሳቢውን ህሊና አሶጥቶ  አእምሯችን በዶ ቀፎ እንዳደረገው ልባቸው በፍቅር የተሞላ ሰዎች ከእኛ ይበልጥ ይገነዘባሉ ፡፡

እናም ማስተዋል ካለን ፣ ሰው ሁሉ ሲወለድ ሁለት ምርጫ በአእምሮው ይዞ እነደሚወለድ ከገዛ አእምሯችን የዘወትር ንትርክ እንገነዘባለን   ።ሁሌም ህይወት ሁለት ተቃራኒ ምርጫ ነው  ያለት ፡፡ በበጎና በቅን ፣ በፍቅር መንገድ  ሁሌም በመጎዝ ህይወቱን አጣፍጦ ፣ ህሊናን አርክቶ እሥከ ዕለተ ምት መኖር አንዱ ምረጫ ሲሆን  ሁለተኛው ምርጫ ፤  በተቃራኒ መንገድ በመጎዝ ፣ በቅጥፈት ፣ በማጭበርበር ፣ በብልጣብልጥነት ፣ በተንኮል ፣ በማታለል  ፤ በጭካኔ ፣ በግፍ ፣ በአጠቃላይ በጥላቻ አእምሮውን ሞልቶ ፣ህሊና ቢስ ሆኖ ለሥጋ ብቻ ተገዝቶ ፣ ዘወትር አየተደናበሩ በመኖር ፣ በቁጭት መሞት ።

ይኸው ነው ። የሴጣን ደቀመዝሙር ከሆንን  የሤጣንን ፣ ፈቃድ ፈፃሚ ፤ ህሊናውን የተነጠቀ ሰው መሆናችን እርግጥ ይሆናል ። እናም ለአእምሮአችን የበላይ አካሉ  ሴጣን ሆኖ እናገኘዋለን ። ትዕዛዝ ሰጪው አዛዥና ናዛዡ እርሱ ሆኖ ያርፈዋል  ።

ህሊናችን የሴጣንን ፈቃድ ፈፃሚ “ በለሌላ ማዕረግተኛ “ ከሆነ   ፤  የበላዩ ሤጣን ሥጋን በጣም በሚወደው ነገር ገዝቶታል ማለት ነው  ። የተገዛ ህሊና ቢስ ሥጋ  ደግሞ የገዢውን ፈቃድ ፈፃሚ ነው ፤ የሚሆነው ። የሴጣን ፈቃድ ደግሞ የታወቀ ነው ። ጥላቻ ፣ክፋት ፣ ተንኮል ፣ ሴራ ና ሸር ፣ ጠልፎ መጣልና ወጥመድ ፣ እንግልት ና መከራ ፣በመጨረሻም ፣ መፈጠርን የማያሥጠላ ሥቃይ ና ሞት ነው ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ወልቃይት፤ ከተከዜ ፖለቲካ እስከ ቀይ ባህር ጂኦ-ፖለቲካ - ሙሉዓለም ገ/መድኀን

ሞት እንጂ ህይወት የሴጣን ፈቃድ አይደለም ። ጥላቻ እንጂ ፍቅር የሴጣን ፈቃድ አይደለም ። የሴጣን ፈቃድ ተጀምሮ እሥኪጨረሥ በሰው መካከል ጠብን መዝራት እና ሞትን ማዋለድ ነው ።

ሰው ቆም ብሎ በማሰብ በአእምሮው ውሥጥ እየተመላለሰ ፣ የፍቅርን አሳቢ አእምሮ ያለመታከት የሚዋጋውን የሤጣን መንፈሥ ከአእምሮው ካላሶጣ በሥተቀር በዚች ምድር ላይ ሰላም ከቶም አይኖርም ።

የዓለም ሰላም ማጣት መንስኤ በሰው አእምሮ የነገሰው የጥላቻ መንፈስ ነው ። የጥላቻ መንፈስ ሁል ጊዜም ከፍቅር ፣ ከመተሳሰብ ፣ ከመዋደድ መንፈስ ጋር አይዋደድም ። እነዚህ የእሱን ጥቅም የሚያሳጡ አድርጎ ሥለሚመለከታቸው በዓለም እንዲኖሩ አይፈልግም ።

ዓለም ዛሬ እየተናወጠች ያለችው አእምሮአቸው በጥላቻ በተሞላ ሰዎች ነው ። የእነዚህ ሰዎች አእምሮ ፍቅርን ገደል በመክተት ጥላቻን አንግሦልና ፣አንዳችም ቀና እና በጎ ነገር አያሥብም ። ከላይ እንደጠቀስኩት ከልጅነቱ ጀምሮ ፍቅርን በማሶጣት ጥላቻ ብቻ  በህሊናው  እንዲቀመጥ በማድረጉ    የሤጣን ደቀመዝሙር ሆኖል ።

የሤጣን ደቀመዝሙር የሆነ ሰው ደግሞ ፣ ከፋትን ፣ መጥፎ ነገሮችን በሙሉ እንደ በጎ በመቁጠር  ጥላቻውን ሙጥኝ ብሎ እንደሚኖር የዛሬ 2013 ዓ/ም ታይቷል ።

የዛሬ 2013 ዓ/ም እየሱስ ሲሰቀል ከጥቂት በፍቅር ልባቸው ከተሞላ ወንዶችና ሴቶች በሥተቀር ብዙሃኑ ምንም ሐጢያት የሌለበትን ” ኢየሱስን ሰቀሉትና በርባን የተባለውን ነፍሰ ገዳይ ፍቱልን ፡፡ ” በማለት ጲላጦስን በጩኸታቸው ብዛት አሥገድደውት እንደነበር አሥታውሱ ።

ማርቆስ 15

¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯

  1. በዚያም በዓል የለመኑትን አንድ እስረኛ ይፈታላቸው ነበር።
  2. በዓመፅም ነፍስ ከገደሉት ከዓመፀኞች ጋር የታሰረ በርባን የተባለ ነበረ።
  3. ሕዝቡም ወጥተው እንደ ልማዱ ያደርግላቸው ዘንድ እየጮኹ ይለምኑት ጀመር።

9  ጲላጦስም፦ የአይሁድን ንጉሥ እፈታላችሁ ዘንድ ትወዳላችሁን? ብሎ መለሰላቸው፤

10 .የካህናት አለቆች በቅንዓት አሳልፈው እንደ ሰጡት ያውቅ ነበርና።

  1. የካህናት አለቆች ግን በርባንን በእርሱ ፈንታ ይፈታላቸው ዘንድ ሕዝቡን አወኩአቸው።

12 .ጲላጦስም ዳግመኛ መልሶ፦ እንግዲህ የአይሁድ ንጉሥ የምትሉትን ምን ላደርገው ትወዳላችሁ? አላቸው።

  1. እነርሱም ዳግመኛ፦ ስቀለው እያሉ ጮኹ።
  2. ጲላጦስም፦ ምን ነው? ያደረገው ክፋት ምንድር ነው? አላቸው። እነርሱ ግን፦ ስቀለው እያሉ ጩኸት አበዙ።
ተጨማሪ ያንብቡ:  ፈተናን መስረቅ ለስብሃት ነጋ ትግል ለሌላው ወንጀል ያደረገው ማነው?

ያ ፣ የዛን ጊዜው በግፈኞች የሚመራ “ የመንጋ ፍርድ “ እኛ እንድንማርበት ከ2013 ዓ/ም በፊት ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ በራሱ መከራ  ሥቃይ ፣ ምት እና ትንሣኤ  ያሳየን ነው።

ዛሬ ደግሞ ፣ ስለ እኛ ሥለ ፍጡራኑ ፣ ዘላለማዊ ህይወት  ሲል ዓምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  መከራ ና ሥቃይ አይቶ መሠቀሉን የምናሥብበት ቀን ነው ።   በዚህ ቀንም የፍቅርን ኃያልነት እንመሰክር ዘንድ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅር ያስገድደናል ።

ክርስቲያን ወድሞቼ ና እህቶቼ ሆይ እሥቲ ዛሬ ቆም ብለን በአእምሯችን ውሥጥ የነገሰው ማን እንደሆነ እንመርምር ?  በአእምሮችን የነገሰው ፍቅር ነው ወይሥ ጥላቻ ? ይህንን በእርግጠኝነት መመለሥ የነገ ህይወታችንን ያቃናልናል ።

እውን ክርስቲያን ነን እያልን በዘር ና በቋንቋ በመቦደን ወንድምና እህታችንን እናገላለንን ? እንዲህ የምናደርግ ከሆነ እኛ በሴጣን ቁጥጥር ሥር መሆናችንን አውቀን ከወጥመዱ በዚህ በትንሣኤ ቀን በመላቀቅ ንሥሐ እንግባ ።

እወቁ ዘረኛ በጥላቻ የገዘፈ የዘር ቀንበሩን ካላወለቀ አይፀድቅም ። በምድርም ላይ እየተቅበዘበዘ ይኖራል እንጂ ፣ የህሊና ሠላም ከቶም አይኖረውም ። ይልቁንስ ሳይረፍድበት ጥላቻን ከልቡ በማሶጣት ፍቅርን ቢያነግስ ነፍሱ በሐሴት ትሞላለች ፡፡

 

1ኛ ቆሮንቶስ 13

¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯

¹ በሰዎችና በመላእክት ልሳን ብናገር ፍቅር ግን ከሌለኝ እንደሚጮኽ ናስ ወይም እንደሚንሽዋሽዋ ጸናጽል ሆኜአለሁ።

² ትንቢትም ቢኖረኝ ምሥጢርንም ሁሉና እውቀትን ሁሉ ባውቅ፥ ተራሮችንም እስካፈልስ ድረስ እምነት ሁሉ ቢኖረኝ ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ።

³ ድሆችንም ልመግብ ያለኝን ሁሉ ባካፍል፥ ሥጋዬንም ለእሳት መቃጠል አሳልፌ ብሰጥ ፍቅር ግን ከሌለኝ ምንም አይጠቅመኝም።

⁴ ፍቅር ይታገሣል፥ ቸርነትንም ያደርጋል፤ ፍቅር አይቀናም፤ ፍቅር አይመካም፥ አይታበይም፤

⁵ የማይገባውን አያደርግም፥ የራሱንም አይፈልግም፥ አይበሳጭም፥ በደልን አይቆጥርም፤

⁶ ከእውነት ጋር ደስ ይለዋል እንጂ ስለ ዓመፃ ደስ አይለውም፤

⁷ ሁሉን ይታገሣል፥ ሁሉን ያምናል፥ ሁሉን ተስፋ ያደርጋል፥ በሁሉ ይጸናል።

⁸ ፍቅር ለዘወትር አይወድቅም፤ ትንቢት ቢሆን ግን ይሻራል፤ ልሳኖች ቢሆኑ ይቀራሉ፤ እውቀትም ቢሆን ይሻራል።

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share