March 19, 2021
19 mins read

ለአሜሪካ ደፋር ጫና የአንድ ተራ ዜጋ ምላሽ – መነሻ (አንድነት ይበልጣል – ሐዋሳ)

western countires

አንድነት ይበልጣል – ሐዋሳ – መጋቢት 10 / 2013

የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ትናንት ያወጣው መግለጫና ያቀረበው ጥያቄ ዋናው ፍሬ ነገር የሚከተለው ነው፡፡

  • ግጭት ይቁም
  • የኤርትራ ወታደሮች እና የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ ያሰፈራቸው የአማራ ክልል ኃይሎች በአስቸኳይ ይነሱ
  • ለተፈፀሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እና ግፎች በኢትዮጵያ መከላከያ ውስጥም ሆነ በህወሓት፣ በኤርትራ ኃይል ወይም በአማራ ክልል ኃይል ተጠያቂ አካል መኖር አለበት፤
  • “ግጭት ይቁም”
    • ተጨባጭ ሁኔታው ሳይፈቅድ፣ “የዓለም ፖሊስ ነኝ” ያለ የውጭ ኃይል ትዕዛዝ ስለሰጠ ብቻ፣ ግጭት አሁኑኑ ሊቆም አይችልም፤ ምክንያቱም፡
  • አሁንም በጠላት ወያኔ በኩል የደፈጣ (አንዳንዴም የአጥፍቶ ጠፊ) ጥቃት አለ፤
  • በሌላ በኩልና በዋነኝነት፣ በክልሉ ብቻ ሣይሆን በመላ ሐገሪቱ ሕግ የማስከበርና፣ ሰላምና መረጋጋትን መልሶ የማስፈን ሥራ በፌዴራል መንግሥት ገና መሠራት አለበት፤
  • ከሐገርና ከጎረቤትም አልፎ ለቀጠናችን ጭምር የጸጥታ ነቀርሳ ሊሆን የሚችልን ሕገወጥ የሕወሐት የሽብርተኛ ቡድንና እንቅስቃሴውን፣ መርዙን ጨርሶ የመንቀልና በአጠቃላይ በቀጠናው ላይ የደቀነውን የጸጥታ ሥጋት ከምንጩ የማድረቅ ሥራ መሠራት አለበት፤
  • ከለውጡ ወዲህ በተለይ በትግራይ የሰሜን እዝ ልዩ ልዩ ክፍሎች ላይ ክህደት፣ ድንገተኛ ጥቃትና ግፍ የተሞላበት ጭፍጨፋ እንዲሁም በማይካድራ ጭካኔ የተሞላበትን የዘር ማጥፋት የፈጸሙ የሕወሐት ወንጀለኞችን ለሕግ/ፍርድ የማቅረብ ሥራ ተጠናክሮ መሠራት አለበት፤ ይህ እየተሠራ ነው፤ የተፈለገው ግብ እስኪሳካ ድረስ ይቀጥላል፤ ይህ መቶ በመቶ ባይሆንም፣ ባመዛኙ በቅርቡ እንደሚሳካ ይታመናል፤ ይህ እስኪሆን ድረስ የሕግ ማስከበሩን ሥራ ለማቆም እንቸገራለን!
  • “የኤርትራ ወታደሮችና የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ ያሰፈራቸው የአማራ ክልል ኃይሎች በአስቸኳይ ይነሱ”፤
    • የሐገር ውስጥ የጸጥታ ኃይሎችን በየትኛውም የሐገሪቱ ክፍል ለጸጥታ ማስከበር ሥራ ወይም የሐገር ሕልውና አደጋ ላይ በሚወድቅበት ጊዜ ለብሔራዊ ግዳጅ የሚያሠማራው የሐገሪቱ ፌዴራል መንግሥት ነው፡፡ አስፈላጊና ጠቃሚ ሆኖ ባገኘው ጊዜ ይህንን መፈጸም፣ የሌላ የማንም ሣይሆን የኢትዮጵያ መንግሥት ብቻ መብት፣ ኃላፊነትና ሕጋዊና ታሪካዊ ግዴታም ነው፤
  • ፌዴራል መንግሥት አስፈላጊ ሆኖ ባገኘው ጊዜ ሁሉ (የሐገሪቱንና የሕዝቧን ህልውና በአንድ ወይም በሌላ መንገድ የሚጎዱ ነገሮች ሲከሰቱ) በየትኛውም ክልል የሚገኝ የጸጥታ ሐይልን ከክልሉ መስተዳድር ጋር በመነጋገር ችግር ወደተፈጠረበት የሐገሪቱ ሌላ ክልል ግዳጅ ለማሰማራት መብቱ ብቻ ሣይሆን ህጋዊና ታሪካዊ ግዴታውም ነው፡፡
  • በታሪክ ውስጥ የኢትዮጵያ ጸረ ወራሪ ድሎች ሁሉ የተገኙት ከመላ ሐገሪቱ የተውጣጡ ጀግኖች ልጆቿን ደምና አጥንት በመገበር ነው፤ የቅርቦቹ የአድዋና የካራማራ ድሎች እንኳ የተገኙት በትግራይና በሶማሌ ጀግኖች ወገኖቻችን መስዋዕትነት ብቻ አልነበረም፤ አሁንም ከዚህ የተለየ ነገር አልተፈጠረም፣ አይፈጠርምም!
  • የሐገር ህልውና ከፍተኛ አደጋ ላይ የወደቀ ሆኖ ባገኘው ወቅት፣ አደጋውንም በውስጥ አቅም ብቻ መቀልበስ አዳጋች ሆኖ ሲያገኘው፣ የወዳጅ ሐገር መንግሥታትን ወታደራዊም ሆነ ሌላ ድጋፍ መጠየቅ፣ ሲገኝም ማስገባትና መጠቀም፣ የችግሩን ጥልቀትና ግዝፈት የሚያውቀው የሉዓላዊ ሐገር ኢትዮጵያ መንግሥት ብቻ መብት ነው፤የኢትዮጵያም ሆነ የሌሎች ሐገራት ታሪክ የሚያሳየውም ይህንኑ ነው፡፡
  • በሶማሌ ወረራ ጊዜ የኩባ፣ የየመን የሩሲያ ወዳጆቻችን ከጎናችን ተሰልፈው የሕይወት፣ የአካልና የኃብት መስዋዕትነት እንደከፈሉልንና ታሪካዊ ውለታ እንደሠሩልን የምናስታውሰው ከከፍተኛ አክብሮትና ምሥጋና ጋር ነው፡፡ ከነዚህ መካከል ሩሲያን የመሰሉት አሁንም ከጎናችን መሆናቸውን ስናስብ ጥሩ ስሜት ይሰማናል፡፡
  • ደቡብ ኮሪያም፣ ሐገራችን ኢትዮጵያ በፈተናዋ ጊዜ የከፈለችላትን መስዋዕትነት እስከዛሬ ድረስ በማስታወስ በልዩ ልዩ መልክ ምሥጋናዋን ትገልጻለች፡፡
  • “ለተፈፀሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እና ግፎች በኢትዮጵያ መከላከያ ውስጥም ሆነ በህወሓት፣ በኤርትራ ኃይል ወይም በአማራ ክልል ኃይል ተጠያቂ አካል መኖር አለበት”፤
  • በጦርነት ወቅት ሆን ተብሎም ሆነ ሊያመልጡት በማይችሉት አስገዳጅ ምክንያት፣ በንፁሐን ሰላማዊ ሰዎች ላይ የሚደርስ ጉዳት ተጣርቶ ተገቢ ሕጋዊ እርምጃ መወሰድ አለበት፤ ይህ አያጠያይቅም፤
    • የማጣራቱ ሥራ የሚሠራው ግን ነጻና ገለልተኛ በሆኑ፣ ብቃት ባላቸው በዋነኛነት ሐገር በቀል በሆኑ፣ በተጨማሪም ቀጠናዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ድርጅቶች በየግልና በትብብር ሊሆን ይችላል፤
      • ከሐገር ውስጥ ተዋናዮች፣ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እና የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ በግልና በትብብር ሥራቸውን እንዲሠሩ የሚያስችል ምቹ ሁኔታ ሁሉ ሊፈጠርላቸው ይገባል፡፡
      • “መተንፈስ አልቻልኩም” እና “የጥቁሮችና የእስያውያንም ሕይወት ዋጋ አለው” ለሚሉ የቤታቸው የብዙኃን ጩኸቶች ጆሮ የማይሰጡና የመብት ረገጣቸውን ሥርዓታዊ በሆነ መንገድ አሁንም እያስቀጠሉ ያሉ አካላትን ደግሞ እናውቃቸዋለን፡፡ ለነዚህ አካላት ይህንን ምንነታቸውን በተለይ እንደ አሁኑ ባለው አጋጣሚ ማስታወስና “ቤታችሁን አጽዱ” ማለት ግድ ይሆንብናል፡፡
      • ዛሬም “የዓለም ፖሊስ ነን” በሚል ድርቅና ከቤታቸው ውጭ ተፈጸሙ የሚሏቸውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች ካልመረመርን ብለው ያዙን-ልቀቁን ይላሉ፡፡ እነዚህ የራሳቸው ድብቅ ፍላጎትና ተልእኮ ያላቸው የውጭ ኃይሎች፣ የማጣራቱ ሥራ ራሳቸው በፈጠሯቸውና በሚደጉሟቸው ዘመናዊ የትሮይ ፈረሶቻቸውና በሰብዓዊ መብቶች ነጋዴዎች አማካኝነት “ይሠራ” ሲሉ ግን “አይቻልም!” ማለት የኩሩ ሰዎች/ሐገሮች መብትም ግዴታ ነው!
      • የአፍሪካ የሰዎችና የሕዝቦች መብቶች ኮሚሽን፣ የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንና ካውንስል ዓለም አቀፍ ሕግና ደንቦችን እንዲሁም ደረጃዎችን በጠበቀ መልኩ ከሐገር ውስጥ የሰብዓዊ መብቶች አካላት ጋር በመተባበርም ጭምር እንዲመረምሩ ሁኔታዎችን ማመቻቸት ይገባል፤ በተለይ የተባበሩት መንግሥታት ክንፎቹ፣ አንዳች ጫና በሌለበት ነገር ግን ከሚጠበቁበት መሥመር እንዳይወጡ በጥብቅ እይታ ውስጥ ሆነው የማጣራቱን ሥራ እንዲሰሩ ቢፈቀድላቸው ዘርፈ ብዙ ጥቅም ይኖረዋል፤
      • በየዘርፉና በየደረጃው የሚገኙ የኢትዮጵያ መንግሥት ልዩ ልዩ አካላትም፣ ገለልተኛ መረጃ ሰብሳቢዎች በጉዳዮች ላይ የመንግሥትን እይታና ምላሽ ለማግኘት በሚጠይቁበት ጊዜ (Corroboration) በቂ ዝግጅት አድርጎ ሙሉ ትብብር ማሳየት ግድ ነው፡፡
      • በተለይ ባለፉት 3 ዓመታት፣ በስም የሰብዓዊ መብትና የዴሞክራሲ ድርጅቶች፣ በተግባር ግን ሌላ ሆነው የተገኙ አካላትን እናውቃለን፣ እነዚህ አካላት በሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ምርመራ ስም፡
    • ለህገወጦች የፖለቲካ ሽፋንና የሕዝብ ግንኙነት ድጋፍ ሲሰጡ የቆዩ፣
    • በአጋጣሚው ሕገ ወጥ የገንዘብ ዝውውር (Money Laundering) ሲፈጽሙ የነበሩ፣
    • ጭፍን ወገንተኝነትና ድብቅ የኢኮኖሚ ፍላጎት አንግበው ለጦር መሣሪያ ገበያ መድራት ሁኔታዎችን ሲያመቻቹ የነበሩ፣
    • ድብቅ የፖለቲካ ፍላጎት በውስጣቸው ይዘው ምዕራባውያን የማይፈልጓቸው መንግሥታት ከሥልጣን እንዲባረሩ፣ አሻንጉሊት መንግሥታት በሥልጣን እንዲቆዩ ወይም ወደሥልጣን እንዲመጡ/እንዲመለሱ በየሐገሩ ነውጥን በልዩ ልዩ መልክ ሲደግፉና ሲያስተባብሩ የኖሩ የስም ሰብዓዊ መብት ድርጅቶችን እናውቃለን፤
    • የእነዚህ ድርጅቶች ውስጣዊና ውጫዊ ቁመናቸው፣ አናታቸው፣ ወገባቸውና እግራቸው ጋር ያሉ ሁኔታዎች፣ የወረቀት ላይና የምድር ላይ ማንነታቸው ወጥነት የሌለውና እጅግ ግራ የሚያጋባም ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜና በአንዳንድ ጉዳይ ከአናታቸው ተበላሽተው ሌላ ጊዜና በሌላ ጉዳይ ደግሞ ወገባቸው ወይም እግራቸው ላይ ሲጠለፉና ያልተቋቋሙባቸውን ፍላጎቶች ሲያራምዱ ይስተዋላሉ፤
    • እነዚህ ድርጅቶች የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የሰብዓዊ መብቶች ነጋዴዎች ሆነው በንጹሃን ደምና ሰቆቃ የሚነግዱ የለየላቸው ሙሰኞችም አሉባቸው፤
    • ከዓለም አቀፍ ሜዲያ ጋር የተለየ ትስስር ይፈጥራሉ ወይም ይፈጠርላቸዋል፤
    • በየሐገሩ ደግሞ እነርሱን የመሰሉ የሰብዓዊ መብቶች ነጋዴዎችን በአማካሪነትና በድብቅ አስተባባሪነት ሰይመው፣ የምድር ላይ ሥራውን የሚያሳልጡ ተላላኪዎችን (መረጃ ሰብሳቢዎችን፣ ምስክር አገናኞችን) መልምለው፣ (የቀለም አብዮትና የዲጂታል ግንኙነት ሣይቀር) ሥልጠናና ሥምሪት ሰጥተውና ከፍለው እየተቆጣጠሩ ያሰራሉ፡፡
    • የኢትዮጵያ መንግሥት በእጅጉ ሊጠነቀቅና ያለይሉኝታ ሊጠብቅ የሚገባው እነዚህን ነጋዴዎች፣ ተላላኪዎችና ቅጥረኞቻቸውን ነው፡፡
      • “ተጠያቂ አካል መኖር አለበት” በሚለው በዚህ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ጥያቄ ውስጥ፤ አራት ተጠያቂ አካላት ተጠቅሰውበታል፤
    • ይህ ጥያቄ በቀላል የሂሳብ ቀመር ሲታይ፣ በትግራይ በቅርቡ በተደረገው ጦርነት በንጹሃን ላይ ለደረሰው ዘርፈ ብዙ ጠቅላላ ጉዳት የሕወሐት ድርሻ 1/4ኛ ብቻ የሆነ የሚያስመስል ስሜት የሚፈጥር ነው፡፡ ለየዋሕ ተመልካች፣ 3/4ኛ የሚሆነው የንጹሃን ጉዳት፣ በቀሪዎቹ ሦስት አካላት (በኢትዮጵያና በኤርትራ መንግሥታት እንዲሁም በአማራ ክልል መስተዳድር) በተናጠል፣ በጥንድ ወይም በአንድነት የተፈጸመ ያስመስላል፡፡ ለኔ ይህ እጅግ መሠሪ የሆነ አቀራረብ ነው፡፡
    • ባለፉት 30 ዓመታት፣ በተለይ ባለፉት 3 የለውጥ ጅማሮ አመታት፣ አሁንም በተለይ ከ5 ወራት ወዲህ፣ እዚህ የተጠቀሱት አራቱ አካላት የነበራቸውን ሚና የኢትዮጵያና የኤርትራ ሕዝብ፣ ዕውነትን የሚፈልግ ማንኛውም አካልና እንዲሁም ተከሳሽም ቢሆኑ የኢትዮጵያና የኤርትራ መንግሥታት፣ የአማራን ጨምሮ የክልል መንግሥታት (ጎበዙን ሙስጠፌን ጠይቁት) ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያውቀውን ዕውነት ጨረፍ አድርገን ለማየት ያህል፤
    • ለጦርነቱ የቻለውን ሁሉ ለዓመታት ዝግጅት ሲያደርግ የነበረው ሕወሐት ነው፤ የመንግሥትና የግል ተቋማትንና ንብረቶቻቸውን የሕዝቡን ጥሪት (ሥንቅ ዝግጅት) ሣይቀር ለጦርነቱ ዝግጅት ዓላማ ሲያውል እንደነበረ እናውቃለን፤
    • ጦርነቱን በድንገት የጀመረው ሕወሐት ነው፤
    • የሰሜን እዝ የመከላከያ ልጆቻችንን በተኙበት የጨፈጨው … ከማረካቸውም በኋላ በከባድ መኪና የደፈጠጣቸውና እንኳን በገዛ ወገንና በማንኛውም ሰብዓዊ ፍጡር ላይ ሊፈጸም የማይገባ ግፍና ነውር የፈጸመባቸው ሕወሐት ነው፤
    • በተሸነፈበት ጊዜና ቦታ ሁሉ መሠረተ ልማቶችን ያፈራረሰው፣ በትግራይ ሕዝብ ላይ የሰው አውሬ ፈቶ የለቀቀውና ሕዝቡ አሁን ለሚገኝበት ቁሳዊ፣ ሥነልቦናዊ፣ የሞራል ቀውስና ሥብራት የዳረገው ሕወሐት ነው፤
    • ይህ ሁሉ የወንጀል ዕውነትና የወንጀለኛ ማንነት በግልጽ በሚታወቅበት ሁኔታ በጅምላ ሁሉንም የጦርነት ተዋናዮችና ተመልካቾች በእኩል ይመርመሩልኝ ማለት ክፉ ድብቅ ፍላጎትና ዓላማን ከሚያሳብቅ በቀር በኢትዮጵያውያን/ኤርትራውያን ላይ የሚያመጣብን ይህ ነው የሚባል ዕዳ የለም፡፡

ስለዚህ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ምርመራው ከላይ በጠቀስኳቸው መርሆዎችና ቅድመ ጥንቃቄዎች መሠረት ቢደረግ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት፣ የኤርትራም ሕዝብና መንግሥት (በልዩ ሁኔታ እንየው እንኳን ብንል፤ የአማራ – ወልቃይት ጠገዴ፣ ራያ – ህዝብና ክልል መስተዳድር) ያተርፉበታል እንጂ አንዳች የሚጎዱበት ነገር አይኖርም፡፡ እንዲያውም እንደ ሐገርና ሕዝብ የምንማረው ብዙ ነገር ይኖራል፤ በጥንቃቄ ከተዘጋጀና ከተጠረዘ የሰብዓዊ መብቶች ምርመራ ሠነድም ትውልድም ይማርበታል፡፡

ፈጣሪ ይርዳን!

 

1 Comment

  1. በምን ላመሥግንህ እውነቱን ብለሃል
    ድፍረት ብቻ ሳይሆን ደላ አስመዝዘኸኛል።
    አይ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አንቶኒ ብሊንከን
    እድሜውም አጭር ነው በሃሰት ወላፈን።
    በተጋሩ ጉቦ አይምሮው የዞረ የሐሰት ጠበቃ
    የሚያልቅስ አጥቶ ብቻውን አደረ በጠፉ ጨረቃ።
    የሀገሩ ዜጎች የሚበሉት አጥተው ሲለምኑ ሣይ
    መጠለያ የለም ማደሪያቸው ድልድይ።
    ጉዱን ተሸክሞ መታየት ወደደ ማቅራራት ሞከረ
    ፉከራው ቀረርቶ ከንቱ ሆኖ ቀረ።
    ይህችን ስንኝ እንድጽፍ የገፋፋኝ በኢትዮጵያ ሀገርችን ጣልቃ ገቦችን ( የዓለም ፖሊስ ነን) ባዮችን በተሰጠው መልስ መርካቴን ለመግለጽ እና ለሀገራችን የሚያስፈልገውን ቅድመ ዝግጂት እና መፍትሄውን በዝርዝር በመገለጹ ተመሳሳይ ጽሁፎችም ቢጨመሩ ለዲያስፖራው ህብረተስም ግንዛቤ ከመስጠቱ ባሻገር ትምህርትም ይሆናል ብየ በማመን ነው።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

158280342 4095651263789804 5258198032540187241 n
Previous Story

እንዳስቀመጧቸዉ  ስላሉ ነዉ ! – ማላጅ

Next Story

በወቅታዊ ጉዳይ ዙሪያ ከአብን የተሰጠ መግለጫ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop