ትላንትና ጉሊሶ፣ ዛሬ ደግሞ ዳቢሳ፣ ነገና ከነገ ወዲያስ? – ከመርሐጽድቅ መኮንን አባይነህ

/

የጸና የሕግ ስርአትና እርሱን በመሬት ላይ ለማስተግበር ሥልጣን የተሰጠው የዘመነ መንግሥት አለ በሚባልበት አገር በብሔራዊ ማንነቱና በሚናገረው ቋንቋ ብቻ እየተመረጠ መሽቶ በነጋ ቁጥር በግፍና በገፍ የሚጠቃው የአማራ ህዝብ በአሁኑ ወቅት በእውን አለሁ ሊል የሚችለው የቱንም ያህል ሲጨፈጨፍ ውሎ ቢያድር ህዝብ በጠባዩ ሞቶ ስለማያልቅ ብቻ መሆን ይኖርበታል፡፡

ሀገራችን ኢትዮጵያ አጥብቃ በምትከተለው ብሔር-ተኮር ፌደራላዊ ስርአት ሳቢያ በያንዳንዱ ክልል መንታ መንግሥታት እንዳሏት ይታወቃል፡፡ እጅግ የሚያሳዝነው ጉዳይ ግን ከነዚህ ጣምራ መንግሥቶቿ መካከል አንዱስ እንኳ በወጉ እናስተዳድርሃለን ሲል በስሙ የሚነግድበትንና የሚመጻደቅበትን ምስኪንና ለፍቶ አዳሪ ማሕበረ-ሰብ ደህንነት ዝቅተኛ በሆነው ደረጃ የመጠበቅም ሆነ የመከላከል አቅምና ፍላጎት የሌለው መስሎ መታየቱ ነው፡፡

መላ የመተከልን ክፍለ-ግዛት ወደምድረ-በዳነት ሲለውጥ ከከራረመ በኋላ በተለይ ወለጋ ውስጥ በየእለቱ እየሆነ ያለውና ጀሯችን እስኪቆሽሽ ድረስ ክፉኛ እያመመን የምንሰማው ዘግናኝ የንጹሃን ወገኖቻችን ጅምላ የዘር ጭፍጨፋ ወይም እልቂት እስከመቸ ድረስ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ለመረዳት ተስኖናል፡፡ እነሆ በምስራቅ ወለጋ ጉሊሶ የተፈጸመው ጭፍጨፈፋ በሆሮ ጉድሩ አቢ-ደንጎር ዳቢሳ በተሰኘው ጎጥ መደገሙን ሰማን፡፡ የካቲት 27 ቀን 2013 ዓ.ም የቀጠለው እልቂት አሁንም አላባራም፡፡

ነገሩን የበለጠ ያከበደው ሁልጊዜ በዳቦ ስም የሚጠራው የደፈጣና የአፈና ቡድን ፈጽሞታል እየተባለ ጠዋት ማታ በሚለፈፍልን ዜና-መዋእል  እውነተኝነት ላይ ሳይቀር ያን ያህል ልንተማመን አለመቻላችን ይመስለኛል፡፡

ሌላው ቀርቶ ኦ.ነ.ግ ሸኔ በመባል ስሙ በተደጋጋሚ የሚነሳው ህቡእ ሀይል የራሱ የኦ.ነ.ግ ወታደራዊ ክንፍ ይሁን ወይም ሌላ የታጠቀ ቡድን በውል ለማወቅ አልተቻለንም፡፡ ታጣቂው ሐይልም ሆነ መንግሥቶቻችን ይህንኑ በሚገባ አስረግጠው እስካሁን ድረስ አልነገሩንም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዜግነትን መቀየር በተመለከተ አንዳንድ ነጥቦች - ባይሳ ዋቅ-ወያ1

ለመሆኑ ኦ.ነ.ግ ሸኔ ማን ነው?

ተጠሪነቱስ ለየትኛው አካል ይሆን?

ቀድሞ ነገር ኦ.ነ.ግ ሸኔ የኦ.ነ.ግ ስሪት ወይም ድርጅታዊ ቅጥያ ካልሆነ በኦ.ነ.ግ ስም የሚጠራው ለምንድን ነው?

ከመሀል አገር የሚዘወርበትና የሚደገፍበት እድል ከሌለስ መንግሥት ኦ.ነ.ግ ሸኔ እያለ የሚያንቆለጳጵሰውን ይህንን አሸባሪ ቡድን እንዴትና ለምን መደምሰስ አቃተው?

በኦ.ነ.ግ ሸኔ አጋፋሪነትና ተቆርቋሪነት በሚገባ የሚጠረጠሩና በወንጀል መመርመር ያለባቸው የኦ.ነ.ግና የኦ.ዴ.ፓ ካድሬዎች ይኖሩ ይሆን እንዴ ጎበዝ?

እንዲያ ካልሆነማ ኦ.ነ.ግ ሸኔ በመሬት ላይ የሚንቀሳቀስና በተፈላጊነት የተመዘገበ አሸባሪ ቡድን ሳይሆን በአይን ሊታይና በእጅ ሊዳሰስ የማይችል ረቂቅ መንፈስ መሆኑ እኮ ነው

በመሰረቱ ይህ እሳቤ ኦሮሞ ሆኖ ከመፈጠርና ከማደግ ጋር በጭራሽ አይገናኝም፡፡ የኦሮሞ ማሕበረ-ሰብ በግብሩ ለዘመናት አብሮት የኖረውን አማራ በድንገት እየተነሳ አንዳች ርህራሄ በጎደለው አፈጻጸም እንደፍሪዳ አጋድሞ የሚያርድበት፣ ከዝርፊያ የተረፈውን ሀብትና ንብረቱን የሚያወድምበትና ከቀየው የሚያፈናቅልበት ምክንያት አይኖረውም፡፡ በስሙ የሚነግዱና በማንነቱ የሚቀልዱ ጽንፈኞች መኖራቸው ግን ፈጽሞ ሊስተባበል አይችልም፡፡

እንደሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎች ሁሉ ዛሬ ኦሮምያ እየተባለ በሚጠራው ክልል ውስጥ ከማእከላዊው መንግሥት በተጨማሪ በጅጉ የተጠናከረ ቁመና ያለው የሚመስል ክልላዊ መንግሥት ጭምር እንደተደራጀለት እንታዘባለን፡፡ በየትኛውም እርከን የተቋቋመና የተደራጀ መንግሥት መኖሩ ከታወቀ ደግሞ የዚህ ወይም የዚያ መንግሥት ቀዳሚና አይነተኛ ግዴታና ኀላፊነት የሚያስተዳድራቸውን ዜጎችና ማሕበረ-ሰቦች ደህንነት መጠበቅና ከጥፋት መከላከል እንደሆነ የሚያከራክር ጉዳይ አይደለም፡፡

ታዲያ ዘወትር ክፉኛ እየተሸማቀቅን የምንሰማውና የምንመለከተው ይህ ሁሉ የዘር ፍጅት ሲፈጸምና ከሞት የተራረፉት ዜጎቻችን በአማጽያኑ አረመኔያዊ ክትትልና ገፋኢነት በየጊዜው እየተሳደዱ ከየመኖሪያ ቀያቸው እንዲፈናቀሉ ሲደረግ በቅርብ ሊታደጋቸው ይገባ የነበረው የኦሮምያው ክልላዊ መንግሥት የማንን ጎፈሬ ያበጥራል እንበል?

ተጨማሪ ያንብቡ:  የበረሃው ጂኒ ፣ የባህሩ ጋኔል  - በልጅግ ዓሊ

ማእከላዊ መንግሥቱስ ቢሆን በዚህ ደረጃ ዝምታን የመረጠበትና አይኔን ግንባር ያርገው ያለ በሚመስልበት አኳኋን የበዛና ገደብ-የለሽ ቸልተኝነት የሚያሳየው ለምን ይሆን?

በግልጽ ሕግ ተደንግጎ ሲገኝ ማድረግ ብቻ ሳይሆን አለማድረግም እኮ በኀላፊነት ያስጠይቃል፡፡

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share