ሰይጣን ለወያኔ እጅ ሰጠ! – ይነጋል በላቸው

ሰይጣንን እስካሁን የምናውቀው ተወዳዳሪ በሌለው ጭካኔው ነበር፡፡ አሁን ግን በወያኔ ተበለጠ፡፡ ሰይጣን የወያኔን ያህል ዐረመኔና ጨካኝ ለመሆን እንደገና ቢፈጠርም አይችልም፡፡ ራሱንም እስኪገርመው ድረስ አስከንድተውታል፡፡

ሰሞኑን እንዲህ ሲባል ሰማሁ፡፡ ሊቀ ሣጥናኤል ነው አሉ፡፡ ልጁ መበላሸት እንደጀመረ ተረዳና “አንተ ልጅ ከወያኔ ጋር መዋል ጀምረሃል እንዴ? ደኅና የነበረው ጠባይህ ተለዋውጦብኛል” አለው አሉ፡፡ ሰይጣን ከተፈረጀበት የጭካኔ ደረጃ እንዲወርድ ያደረጉት ወያኔዎች ምን ያህል ጨካኝ ቢሆኑ ነው ግን? አዲስ የልጆች ማስፈራሪያ አገን፡፡ ልጅ ሲረብሽ ወይም የሌለንን ነገር ውለዱ ሲለን  “ዋ! ወያኔን እንዳልጠራልህ!” ማለት ነው ከእንግዲህ፡፡ “ጭራቅ መጣብህ…” ብንል ኃይል የለውም፡፡ ጭራቅን የሚያስንቅ ወያኔ አለልን፡፡ ሁለት ልጃገረዶችን ህጋቸውን ከወሰደ በኋላ አርዶ በግራካሱ ገደል የሚከት አንጋፋ ወያኔ ከጭራቅ ካልበለጠ ማን ሊገዳደር ይችላል?

ዱሮ ያየሁት አንድ ፊልም አሁን ድረስ ትዝ ይለኛል፡፡ “The Evil that Men Do” ይላል ርዕሱ፡፡ ዩቲዩብ ላይ ተጭኖ ከሆነ እዩት፡፡ የሰው ልጅ በቁሙ ሲጠበስና ሲዘለዘል ታያላችሁ፡፡ ወያኔም ያደረገውና እያደረገ ያለው ከዚህ ቢብስ እንጂ አያንስም፡፡

ሕወሓት ጫካ እያለ በባዶ ስድስት ምን ያደርግ እንደነበረ ይታወቃል፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስካሁኒቷ ቅጽበት ስንት ሚሊዮን አማሮችን እንደገደለ፣ እንዳሳደደና እንዳሰደደ፣ እንዳመከነ፣ እንዳኮላሸና ሌላ ሌላም ሊናገሩት የሚዘገንን ጠያፍ ነገር እንዳደረገ ፈጣሪ ብቻ ነው የሚያውቀው፡፡ ደግነቱ ግን ያን ሁሉ ብድራቱን አንድዬ መክፈል ጀምሯል፡፡ ሰው ግን ሞኝ ነው – የዘራውን እንደሚያጭድ ብዙ ሰው አያውቅም፡፡ የተረገዘ ሕጻን ተወልዶ የአባቱን ገዳይ በሚበቀልባት ሀገር በሰው ላይ ግፍ መሥራት ይዘገያል እንጂ ብድሩ አይቀርም፡፡

ሰውን ከነነፍሱ መቅበር፣ ሰውን በጨለማ ቤት ውስጥ አጉሮ በርሀብ መግደል፤ ወንድን በወንድ ማስደፈር፣ ሴትን በሴት ማስጠቃት፣ የጋሉ ግዑዝ ነገሮችን በሰውነት ቀዳዳዎች መሰካት፣  ጥፍርን መንቀል፣ በፈላ ዘይት ሰውነትን መጥበስ፣ ዐይንን በጉጠት ማፍሰስ፣ እግርና እጆችን መቆራረጥ፣ አገር አማን ብለው የተኙ ወታደሮችንና ሲቪሎችን መረሸን፣ ሕዝብን በታንክና በመትረየስ መረፍረፍ፣ ድልድይና መንገድን የመሳሰሉ ታኅታይ መዋቅሮችን በፈንጂና በቦምብ ማውደም፣ ዜጎችን በጅምላ በርሀብ መቅጣት፣ አማሮች እንዳይወልዱ በዘዴ ማምከን፣  ሕጻናትን ለጦርነት ማሰለፍ፣ ባንክን መዝረፍ፣ የሀገርን ሀብት በእሳት ማጋየት …. የወያኔ የደስታ ምንጭ እንደሆነ ለዘመናት ዘለቀ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የገጠማት አንዱ ፈተና ጦስ መውጫ የታጣለት ‹‹የብሔር ፖለቲካ›› አዙሪት ነው!

የድህነታችን መንስኤ በተለይ አሁን በጣም ግልጽ  ነው!

እያንዳንዱ ወያኔና የወያኔ ቤተሰብ በቢሊዮን የሚገመት ገንዘብ አለው፡፡ ያቺ የመለስ ዜናዊ ልጅ በየአውሮፓ ከተሞች በምሽት ክበቦች ለመንዘላዘል የምትጠቀምበት በስሟ የተመዘገበ ከአምስት ቢሊዮን ዶላር የበለጠ ገንዘብ እንዳላት ይነገራል፡፡ በብር ምቱት፡፡ የአንዲቷ ሰምሃል እንዲህ ከሆነ በመለስ ስም፣ በአዜብ ስም፣ በሌሎች ቤተሰቦቿ ስም፣ በአቦይ ስብሃትና በልጆቹ ስም፣ በሥዩም መስፍንና በልጆቹ ስም፣ በአባይ ፀሐዬና በልጆቹ ስም፣ በሁሉም ወያኔዎችና በልጆቻቸው ስም…. እጅግ ብዙ ዶላር አለ፤ እጅግ ብዙ ቤትና ሀብት ንብረት አለ፤ እጅግ ብዙ ፋብሪካና የንግድ ተቋማት አሉ – በሌላ በኩል መቶ ምናምን ሚሊዮኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ ምሣውን እንደምንም ቀምሶ ለራቱ ይጨነቃል፡- ድንቁርናን የተመረኮዘ ሆዳምነትና ስግብግብነት በፈጠረው ዕንቆቅልሽ ተወጥረናል፡፡ በእያንዳንዱ ጎምቱና ግልገል ወያኔ እጅ የገባውን ሀብትና ንበረት፣ በ30 እና 40 ዓመታት ውስጥ የተመዘበረውንና በሀገር ውስጥም በውጭም የተቀመጠውን በብዙ ቢሊዮን የሚገመት ገንዘብ አስቡ (እንዴ! የ16 እና የ17 ዓመት ዕድሜ ኮልኮሌ ወያኔ እኮ ሀመርና ቪ8 ነው አዲስ አበባ ላይ የሚያሽከረክረው – የአሁኑን አታስዋሹኝ አላውቅም፤ በፊት ግን እኔ በሸፋፋ ጫማ ቸርችርል ጎዳናን ሳዳርስ የልጅ ልጄ የሚሆን ጩጨው ወያኔ እንዲያ ነበር የሚቀናጣው፡፡ የጋራ ሀገር እንዳለችን የምናውቀው ጦርነት ሲኖር ብቻ ነው፡፡ በዚያም ወቅት እነሱ ሲምነሸነሹ የኛ ልጆች ዘምተው ያልቃሉ፡፡

ወያኔን ለመዋጋት ደርግ በ17 ዓመታት ለጦርነቱ ያወጣውን 40 እና 50 ቢሊዮን ዶላር ደግሞ ጨምሩበት፡፡ ሀገሪቱም እኛም እስትንፋሳችን መገኘቱ ታዲያ አያስገርምም ትላላችሁ?… ይህን ሁሉ ገንዘብ በብር ምቱትና ደምሩልኝ፡፡ ወያኔ አራት ኪሎን ከያዘች ጀምሮ ወደ ትግራይ ዋሻዎችና የምድር ውስጥ ቤቶች በሌሊትም በቀንም አጓጉዛ የወሰደችውንና ለኢትዮጵያ ጥፋት የምትጠቀምበትን ገንዘብና ሀብትና ንብረት፣ እንዲሁም የጦር መሣሪያ ወደ ገንዘብ ለውጡትና ይህንንም ደምሩልኝ፡፡ ለአንዲት ሚሳይል የሚወጣውን ሳትረሱ ያ ሁሉ የጦር መሣሪያ በኔና ባንተ ላብ መገዛቱን አስታውስና የኛ ድህነት መሠረቱ ምን እንደሆነ አጢንልኝ፡፡ በ46 ዓመት የሽፍትነትና የመንግሥትነት ዕድሜያቸው ስንትና ስንት ትሪሊዮንና ምናልባትም – ትንሽ ላጋንነው – ኳትሪሊዮን ብር እንደዘረፉን ተገንዘቡ፡፡ ይህ እንግዲህ ባፍ ጢሙ የደፉትን ትምህርት፣ ባፍ ጢሙ የደፉትን ሰብኣዊነት፣ ባፍ ጢሙ የደፉትን ሃይማኖት፣ ባፍጢሙ የደፉትን ዐዋቂና አስተዋይ ትውልድ፣ ገደል የከተቱትን ብሔራዊ ስሜት፣ እንጦርጦስ የዶሉትን የአብሮነት ሀገራዊ ሕይወት ወዘተ. ከግምት ሳናስገባ ነው፡፡ እሱ እሱ ከታሰበ ያሳብዳል – ያላበድን ካለን፡፡ ምን ያላደረጉን ነገር አለ? ምንስ ያልሆንነው አለ? የሚያሳዝነው የመረገማችን ቅጥ ማጣቱ አሁን ያለንበትም እንደበፊቱ መግማማቱ – ግጥ ገጠምኩ ልበል?  ከወያኔ ዘረኝነትና በሙስና የበከተ ሥርዓት ወጥተን ወደ ኦህዲዳዊ የበሸቀጠ አዲስ አፓርታዳዊ ሥርዓት እንገባለን ብዬ በፍጹም አስቤ አላውቅም፡፡ ዕድላችን ጠማማ ነው፡፡ ማነው “ዕድሌ…  ጠማማ… ጠማማ…. ከሰው የተለዬ …” ብሎ በአንድ ዘፈኑ ያቀነቀነው?

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአስቆርቱ ይሁዳ እንኳን ህሊና ነበረው! - በላይነህ አባተ

ቢሆንም … ቢሆንም እግዚአብሔር ቅን ፈራጅ አምላክ ነው፡፡ ሥራውን ጀምሯል፡፡ የጅማሬው ሥኬት በግምታዊ የመቶኛ ሥሌት ቢገለጽ እስካሁን ባለው ሁኔታ አምስት ግፋ ቢል አሥር በመቶ ቢሆን ነው፡፡ ዋናው ገና ነው፡፡ በአራቱም አቅጣጫ በነሱ ጦስ እየታረደና ደሙ እንደጅረት እየፈሰሰ ያለው የአማራ ዕንባ ራሱ ለነዚህ እርጉማን የመጨረሻ ሲዖላዊ ፍዳ ከበቂ በላይ ነው፡፡  ኦሮሙማም እንዳቅሚቲ ወተር ወተር እያለች ነው – ግን ንገሯት “ እሥረኛን ከመንግሠተ ሰማይ ሣይቀር አመጣላሁ ብላ በትዕቢት ተወጠጥራ ለነበረችው ወያኔ ያልሆነ ‹አራት ኪሎ› በያዝሽው መንገድ ላንቺም አይሆንም፤ ይልቁንስ ዕድልሽን  በከንቱ አታበላሽ” በሏት፡፡ ካላመነችኝ ወደ ዘመዶቿ ጠጋ ትበልና ሞራ ታስነብብ – ግፋ ቢል አንድ የፍየል ሙከት ብትገዛ ነው፡፡

የሆኖ ሆኖ ለምን ድሃ እንደሆን አያችሁልኝ አይደል? በቅመሱልኝ ያለቀውን ኢኮኖሚያችንን፣ በሙስና የተመዘበረውን ሀብታችንን የሚያይ ታዛቢ የበረንዳ አዳሪውንና ያጣ የነጣ ድሃውን መብዛት ሲመለከት አይደንቀውም፡፡  ያለ መንግሥት መኖር ዕዳው ከዚህም በላይ ነውና፡፡

የኔ ተማሪ የነበረ የያኔው ግልገል የአሁኑ ጎልማሣ ወያኔ በአሜሪካን ሀገር በ110 ሽህ ዶላር ልዩ ሊሞዝን ይንፈላሰሳል እዚህ የአቶ ሐጎስ ልጅ ገና በ12 ዓመቱ በቂ የኮቸሮ ራሽን እንኳን ሳይሰጠው ከአቅሙ በላይ የሆነ መትረየስ ተሸክሞ ወያኔን ከሞት ሊያድንና ወደነበረበት ሥልጣን ሊመልስ ይንጠራወዛል – “ተቀልዷል፣ ተቀልዷል፣ ተቀልዷል…” የምትለዋን የብርቱካን ዱባለን ዘፈን ተጋበዙልኝ በዚህች አጋጣሚ፡፡ ምን ዓይነት የታሪክ ዕንቆቅልሽ ውስጥ ነው የምንገኘው ግን ወገኖቼ? ዓለም መቼም አይታው የማታውቀው ቡድን ነው ሕወሓት፡፡ በስማም!!! መጥኔ ለወለዳቸው፤ ያገባስ ይፈታቸዋል – ለነገሩ ከአሁን በኋላ ሞት እንጂ የምን ፍቺ ነው፡፡ “ሲያልቅ አያምር!” ይሉ ነበር ወይዘሮ ባፈና – በ‹ካድማስ ባሻገር› ብለው ይሆን እንዴ ግን?

ተጨማሪ ያንብቡ:  አባይ...አባይ፤ የታላቁ የአባይ ግድብ እና የድርድር ውጣ ውረድ

 

“Satan surrendered to TPLF” ብለህ አንድኛህ አንባቢ ይቺን አጭር መጣጥፍ እባክህን ወደ እንግሊዝ አፍ ተርጉምልኝ፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share