በየክልሉ የሚታየው የፖለቲካ ሕብረት መላላትና መገፋፋት ለኮሮና ቫይረስ መራቢያ መሣሪያ ነው! – አንድነት ይበልጣል

አንድነት ይበልጣል
ከሐዋሳ ሚያዝያ 12/ 2012

 

በአሁኑ ጊዜ መላውን ዓለም በተለይም በቁሳዊ ሐብት፣ በቴክኖሎጂ፣ በሣይንሳዊ ዕውቀትና አሠራር የበለጸጉ ሐገራትን በእጅጉ እያጠቃ ያለው የኮሮና ቫይረስ በሽታ (ኮቪድ19) ለኢትዮጵያ ሐገራችንና ለሕዝባችንም በአይነቱ የተለየ እጅግ አሳሳቢ ፈተናና አደጋ ይዞ መጥቷል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት በፌዴራል ደረጃ በሽታውን ለመከላከልና ሊያስከትል የሚችለውንም ብሔራዊ ውድመት ለመቀነስ በከፍተኛ የኃላፊነትና የአገልጋይነት ስሜት የተሞላ፣ በዕውቀትና በከፍተኛ ቅንጅት የሚመራ፣ በልባዊ የቁርጠኝነት ስሜትና በእናሸንፋለን ሙሉ ተስፋ የሚገፋ ርብርብ ሲያደርግ እየተመለከትን ነው፡፡

 

ሳይደግስ አይጣላም

  • እስኪ ዕውነት እንናገር፤ በዚህ የፈተና ወቅት ያሉን መሪዎች እነ መለስ ዜናዊ፣ ስብኃት ነጋ፣ ዓባይ ጸሀዬ፣ ጌታቸው አሰፋና ረዳ፣ በረከት ስምዖን፣ አለምነው መኮንን፣ አብዲ ኢሌ፣ ኢስማኤል፣ አባዱላ ገመዳ፣ ሽፈራው ሽጉጤ ቢሆኑ ኖሮ ምን ይውጠን ነበር?! (የአዲስ አበባ፣ የሐረርና የድሬዳዋ ገዢዎች እነማን ነበሩ?) እነ ደብረጽዮንና ከላይ የጠቀስኳቸው ወያኔዎች (ጊዜ እንኳን ረድቷቸው/ከእንቅልፍ ባነው) በዚህ ወቅት በትግራይ ክልል ድንቅ ውጤት ባስመዘገቡና ይህ የኔ ምልከታ ፉርሽ በሆነ!
  • እስኪ ተመልከቱት፣ በዚህ የፈተና ወቅት የኢትዮጵያ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እንዳለፉት 25 ዓመታት በሁለት ሲኖዶስ ተከፍላ ቢሆንና በተጨማሪም የሲኖዶስና የምዕመናን ግንኙነት እንደቀድሞ የሻከረ ቢሆን ኖሮ ዛሬ በዚህ የኮሮና ፈተና ወቅት ምን ይውጠን ነበር!?
  • እስኪ ተመልከቱት፣ ሐጂ ሙፍቲን የመሰሉ የእስልምና ብቻ ሣይሆን የሐገር አባቶችና ሽማግሌዎች እንደቀድሞ ተገፍተው ቀርተው ቢሆን ኖሮና በጠቅላላ የኢትዮጵያ ሙስሊም የሐይማኖቱን ነጻነት አጥቶና ከገዛ ሐገሩ ጉዳይ ተገፍቶ እንደተሰደደና እንደታሠረ ቢሆን ኖሮ ኢትዮጵያ በዚህ የፈተና ወቅት ምን ይውጣት ነበር?! …

እኔ በበኩሌ እግዚአብሔርን የማመሰግንበት ሌሎች ሚሊዮን ምክንያቶችም አሉኝ፡፡ ወደ ተነሳሁበት ጉዳይ ላምራ፡፡

 

በክልሎች የሚታየው የፖለቲካ አንድነትና ኮሮናን ለመዋጋት ያላቸው ዝግጁነት

ክልሎች ለኮሮና ወረርሽ ፈተና ትኩረት ሰጥተው እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን በመገናኛ ብዙኃን ከሚያቀርቧቸው ዘገባዎች መረዳት ይቻላል፡፡ ነገር ግን የዓለም ጤና ድርጅት የኢትዮጵያ ጽ/ቤት በቅርቡ ባወጣው የአነስተኛ ዳሰሳ ውጤት ላይ እንደገለጸው በሽታውን ለመከላከል በክልሎች ደረጃ ያለው ዝግጁነት ገና ብዙ ሥራ የሚጠይቅ ብቻ ሣይሆን የዝግጁነት ደረጃቸውም ከክልል ክልል ይለያያል፡፡ የጤና ድርጅቱ ዘገባ ከተሰማ በኋላ በክልሎች ዝግጁነት ደረጃ ላይ መሻሻል ሊኖር እንደሚችል ቢገመትም የተግዳሮቱን አሳሳቢነት አይለውጠውም፡፡ ኮሮናን ከመዋጋት አንጻር፣ ለኔ በክልሎች ላይ ለተጋረጠው ትልቅ ተግዳሮት ዋነኛው መንስኤ የሚመስለኝ ከአቅርቦት፣ ከመሣሪያና ከሙያተኛ እጥረት በማይተናነስ መልኩ በውስጣቸው የሚታየው የፖለቲካ አንድነት መላላትና አለመረጋጋት ነው፡፡ በፌዴራል ደረጃ ያለው የአመራር አንድነትና መናበብ ስሜት በእያንዳንዱ ክልልም እየታየ አይደለም፡፡ የኮሮናን በሽታ ለመከላከል የተሻለ ዝግጁነት አላቸው የተባሉትም ክልሎች ቢሆኑ ሌላ ከፍተኛ ችግር ውስጥ ናቸው፡፡ በውስጣቸው ባሉ ፖለቲካዊ አለመረጋጋቶች፣ ሽኩቻዎችና የጸጥታ መደፍረስ ምክንያት ያላቸው የአመራር አንድነትና በአመራሩና በድርጅቶች እንዲሁም በሕዝብ መካከል ያለው መናበብ ወረርሺኙን ለመከላከል በሚያስችል ደረጃ አሰተማማኝ ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ ነገሩ ሁሉ ትኩረት የሚሰርቅና ኃይልን የሚበትን ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዛሬም ዐማራውን ነጥሎ የማጥቃቱ ዘመቻ ተጠናክሮ ቀጥሏል (ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት )

እንደ ኮሮና ቫይረስ የመሰለውን ሐገራዊ ፈተናና ቀውስ ለመመከትና ለመሻገር የፖለቲካ አንድነትና ሕብረት እጅግ ወሳኝ ነገር ነው፡፡ በገዢው ፓርቲ አመራር መሐል፣ በገዢውና በተፎካካሪ ፓርቲዎች መካከል፣ በተፎካካሪ ፓርቲዎች መሐል፣  በመንግሥትና በሕዝብ መካከል አንዲሁም በዜጎች መካከል ያለው የፖለቲካ አንድነትና ሕብረት በየደረጃው የኮሮና ቫይረስን በሽታ በመዋጋት ረገድ የስኬታችንን ልክ ይወስነዋል፡፡ በፌዴራል ደረጃ ያለው የፖለቲካ አንድነትና ሕብረት ጉዳይ ለኔ ተስፋ ሰጪ ሆኖ ይታየኛል፡፡ ትልቅ መሰናክል የሚታየው በክልሎች ደረጃ ነው፡፡ የፖለቲካ አንድነትና ሕብረት መላላት፣ የኮሮና ቫይረስን ወረርሺኝ በመመከት ጥረት ላይ የሚያሳድረውን አሉታዊ ተጽዕኖና የኋላ ኋላም ሊያስከፍል የሚችለውን ውድ ዋጋ ከወዲሁ ለመገመት የክልሎቻችንን ተጨባጭ የፖለቲካና የጸጥታ ሁኔታ በወፍ-በረር መቃኘት ይጠይቃል፡፡ (በጎደለ ሙሉበት)፡፡

 

የክልሎች ወቅታዊ የፖለቲካ አንድነት መላላትና የጸጥታ መደፍረስ ሁኔታ

  • ትግራይ ክልል አመራሮች የሚታየው ለውጡን ያለመቀበል አቋም፣ ከፌዴራል መንግሥት ጋር የመኮራረፍ ሁኔታ ያስከተለው መሳሳብና ቢያንስ አርፎ ያለመቀመጥ ሁኔታ፤ አዲስ በተከፈተው የትግራይ ብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤትና በሕወኃት መካከል የተጀመረውና መቀጠሉ የማይቀረው መገፋፋት፣ እንዲሁም እነ አረና፣ ትዴፓና አ(ሲምባ)ዴፓን የመሰሉ የክልሉን የፖለቲካ ኃይሎች እንደባለድርሻና እንደአጋር የማየቱ ባህል ገና ያልተጀመረ መሆኑ፣ ኮሮናን ከመከላከል አንጻር የክልሉን ትኩረትና ኃብት እንዲበታተን ማድረጉ የማይቀር ነው፣
  • አማራ ክልልም የሚታየው የፖለቲካ ኃይሎች አንድነት መላላት ትኩረት-ሰራቂ ጋሬጣ ነው፡፡ ከጀርባቸውም ይሁን ከሩቅ ማንም ኖረም አልኖረም፣ በዋነኛነት በፋኖ የሚገለጹት ኢመደበኛ አደረጃጀቶች የጋረጡት የጸጥታና የሉአላዊነት ተግዳሮት ከፍተኛ ነው፡፡ በአብን በኩል “ነገርን በደላላ የማፈላለግ”ና የጎንዮሽ የጭቅጭቅ አጀንዳ እየፈጠሩ የማከፋፈል የትንኮሳ “ሥራ” ላይ መጠመድ ይታያል፡፡ (በዚህ ወቅት ዕርዳታ/ምግብ ማከፋፈል ሲገባ!) እንዲሁም እስካሁን ያልተመለሱ ምናልባትም ገና መሠረታዊ ለውጥን መጠበቅ የሚኖርባቸው የአማራ ማንነት ጥያቄዎች (ወልቃይት፣ራያ፣ ቅማንት ወዘተ) አሉ፡፡ እነዚህ ተደማምረው ማን ነው ልክ? መቼ ሲሆን ነው ልክ? አጣዳፊው የቱ ነው? የሕዝቡ ጥቅምስ በዕውነት የሚጠበቀው በማንና እንዴት ነው? በሚሉ ጥያቄዎች ዙሪያ ሕዝቡን ለውዥንብር የዳረጉት፣ ግራ ያጋቡት፣ ይይዝ – ይጨብጠውን ያሳጡት – በሚያሳዝንና በሚያስቆጭ የጣት መቀሳሰር ሁኔታ ውስጥ ያስገቡት ይመስለኛል፡፡ መከፋፈል አለ፡፡ ይህ ምልከታ በከፊልም ቢሆን ዕውነትነት ካለው፣ የክልሉ ሕዝብና መንግሥት የኮሮና ቫይረስን ወረርሺኝ ለመመከትና ለመሻገር ምን ትኩረትና አቅም ሊኖረው ነው?
  • ኦሮሚያ ክልል በታጠቁ ኃይሎች (ኦነግ ሸኔ)፣ በሰላምና በጉልበት አማራጮች መካከል ገና ዥዋዥዌ ውስጥ ባሉ ጽንፈኛ የፖለቲካ ኃይሎች እና ሁሉንም ጉዳይና አጋጣሚ ለፖለቲካ ትርፍ ማግኛ መጠቀም በሚፈልጉና ከብሔር-ብሔር ጨዋታ ለመውጣት ባልተዘጋጁ ጃዋር-መራሽ አክቲቪስቶች የሚፈጠረው ተግዳሮት የክልሉ መንግሥትና ሕዝብ ትኩረት ላይ ተጽእኖ ማሳደሩ አይቀርም፡፡ እነ ኦፌኮና ኦነግ ግን ምንድነው በትክክል የሚፈልጉት? ሁኔታውን የከፋ የሚያደርገው ደግሞ በክልሉ መንግሥትና ብልጽግና ፓርቲ መዋቅሮችም ውስጥ የጽንፈኛ ኃይሎች ወኪሎችና የተረኛነት በሽታ የሚያንገዳግዳቸው አካላት አሁንም መኖራቸው ነው፡፡ ታዲያ በምን አእምሮ፣ ልቡናና ቀልብ ነው እነዚህ የነጃዋርና ሸኔ ተላላኪ ሰዎች በኮሮና ቫይረስ በሽታ ላይ የታወጀውን የመከላከል ጦርነት የሚመሩትና ለድል የሚያበቁን?
  • የደቡብ ክልል የአመራር አንድነት ካጣ ሰነባብቶአል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ የሕዝብን ጥቅም ማዕከል ባላደረገ ምክንያት የዞንና ወረዳ መስተዳድሮችና ልሒቃኖች በሚያነሱት የክልልና ዞን እንሁን ሙግት፣ ብሽሽቅ፣ መሳሳብና ምን ቸገረኝነት ክልሉ የአመራር አንድነት አጥቷል፡፡ ይህም የኮሮናን ወረርሺኝ በመመከት ረገድ የክልሉን አቅም ደካማ እንደሚያደርገው አያጠራጥርም፡፡
  • ቤኒሻንጉል ክልል ጂኦግራፊያዊ አቀማመጡ መነሻ ሆኖ በክልሉ የሚፈጠሩ ልዩ ልዩ ተግዳሮቶች፣ የክልሉ መስተዳድር የኮሮናን ወረርሺኝ በተባበረ ክንድ ለመመከት እንቅፋት ሲሆንበት እየታየ ነው፡፡ ሰሞኑን የክልሉን ጸጥታ ለማረጋጋት የተቋቋመው የሲቪል ኮማንድ ፓስት ሥልጣኑን በመከላከያ ኃይል ለሚመራ ኮማንድ ፖስት ማስረከቡ ችግሩ እስካሁን አለመፈታቱን ያሳያል፡፡ ክልሉ ለዋናዋናዎቹ ክልሎች ያለው ቅርበትና አዋሳኝነት፣ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ መገኛና ለሱዳን ድንበር ቅርብ መሆኑ፣ የትግራይ ክልል አመራሮች በአማራና በኦሮሞ ክልሎች እንዲሁም በመላ ሐገሪቱ አለመረጋጋትን ፈጥሮ ለማቆየት የሥምሪት፣ የሥልጠናና ተልእኮ ማስተላለፊያና መሸጋገሪያ መሆኑ ሁሉ ተደማምሮ ለክልሉ ብቻ ሣይሆን ለሐገርም በሁሉም ረገድ ከባድ ፈተና ነው፡፡
  • በሶማሌ ክልል በቅርቡ የታየው አስደንጋጭ መንገራገጭ አሁን መፍትሔ ያገኘ ይመስላል፡፡ ነገር ግን ቀውሱ በአንድ ቀን ተከስቶ በአንድ ቀን እልባት ያገኘ አይደለም፡፡ ስለዚህ በሌሎች ክልሎች የሚታየውን ያህል ባይሆንም፣ እዚህም በአመራሩ ውስጥ ሊፈጠር የሚችለው ክፍተት እና ከስደትና ከመሣሪያ ትግል ከተመለሱ አንዳንድ አካላት ጋር አልፎ አልፎ የሚታየው መሳሳብ የኮሮና ቫይረስን በመከላከል ጥረት ላይ ትኩረትን አይሰርቅም፣ ኃይልን አያሳሳም አይባልም፡፡ ቢሆንም ሙስጠፌ ጀግና ነው፤ ሽመልስ አብዲሳ ደጋግሞ ቢያገኘው ይጠቀማል፣ ይጠቅማል፡፡
  • አዲስ አበባም ቢሆን በነኢንጂነር ታከለ ኡማና በአመራር ቡድናቸው ደረጃ የሚታየው ሰው-ሰው እና ሐገር-ሐገር የሚል ብቃትና ዝግጁነት ያለው አመራር በመስተዳድሩ መዋቅር ዝቅተኛ እርከኖች ላይ እየታየ ነው ለማለት ይከብዳል፡፡ እነባልደራስ ዙሪያ የቆየው መሳሳብም ከአብን የ”ነገር በደላላ” አካሄድ የተሻለ እንዲሆን እመኛለሁ፡፡ በዚህ ረገድ የኢዜማ ፓርቲ ወቅታዊ አቋም ብስለትና አርቆ ተመልካችነት የሚታይበት፣ ለሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎችም በአርአያነት የሚጠቀስ መሆኑ ይሰማኛል፡፡
  • በሐረሪ ክልልና በድሬደዋ መስተዳድርም የጠራ ነገር እየታየ አይደለም፡፡ የኮሮናን ቫይረስ ተከላክሎና ተዋግቶ ለማሸነፍ ያላቸው ዝግጁነትም የሚታየው በዚሁ ልክ ነው፡፡
ተጨማሪ ያንብቡ:  የሁለቱ ሰልፎች ወግ - ሰሎሞን ጌጡ ከኑረምበርግ

 

የፖለቲካ አንድነትና ሕብረት – የኮሮናን ፈተና ለማለፍ መከተል ያለብን መንገድ

ከላይ የተዘረዘሩት የፖለቲካና የጸጥታ ችግሮች ሁሉ በአንድ ገጻቸው የሚያሳዩት የኮሮናን በሽታ ለመከላከል ከፊታችን የተደቀነውን ትልቁን ተግዳሮት ነው፡፡ መከፋፈልና መገፋፋት ተጨምሮበት ይቅርና በሙሉ አንድነትና አቅም ብንሰራም እንኳን የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ማሸነፍ የማይቻል ባይሆንም እጅግ ከባድ መሆኑ ግን አይቀርም፡፡ በሽታው እንደ ሐገር የጋረጠብንን አደጋና የሚያስከትለውን ሁለንተናዊ ቀውስ ለመቀነስ በምናደርገው ርብርብ ሁሉም-ዓይነት ሐገራዊ ወረታችን መሟጠጡና የለውጥ ፍጥነታችን መጓተቱም የማይቀር ነገር መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡ በዚህም የተነሣ በርካታ ከሥራ አጥነት፣ ከድህነት፣ ከጸረ ዴሞክራሲና ከጸረ አንድነት ቅርቃሮች የመውጫ ተስፋ-ሰጪ ትልሞቻችንና ጅምሮቻችንም ለወደፊት መተላለፋቸውና መራዘማቸውንም እያየን ነው፡፡ በዚህ ላይ የፖለቲካ መከፋፈልና የሕብረት መላላት ሲጨመርበት እጅግ የባሰ ዋጋ ያስከፍላል ነው፡፡

ለአንዳንዶቻችን አልታይ ካላለን በቀር መሳሳብ፣ መጎነታተልና መጋጨት፣ በሌላ ገጻቸው የሚያሳዩን አማራጭ ደግሞ መፍትሔውን ነው፡፡ ይህም በፖለቲካ ኃይሎች መካከል መ          ቀራረብ፣ መቻቻል፣ ሰላማዊና ሕጋዊ መስተጋብር መፍጠር፣ የጋራ ጉዳዮችን ለይቶ በሕብረት መሥራት፣ የሚብሰውን ማስቀደም፣ የሚደርሰውን ማቆየት፣ የራስን አማራጭ አቅርቦ ምርጫና ውሳኔውን ለሕዝብ የመተው ሌላው ገጽታ ነው፡፡ ይህን በጎ ገጽታ ማየትና መሞከር ይገባል፡፡ ማንም እና ምንም ብንሆን የኮሮና በሽታ የመጣው በሁላችንምና በእያንዳንዳችን ላይ ነው፡፡ መንግሥትነት፣ ሕዝብነት፣ ገዢ ፓርቲነት፣ ተቃዋሚ ፓርቲነት፣ ኃይማኖት፣ ብሔር፣ ፆታ፣ ዕድሜ፣ ኃብታምነት፣ ባለጸጋነት፣ ደሃነት፣ የተማረ/ያልተማረ፣ በባሕር ማዶ ወይም በሐገር ውስጥ መኖር፣ የሶሻል ሜዲያ አርበኛ መሆን፣ ታዋቂ ወይም ተራ ሰው መሆን በዚህ በሽታ ፊት ጉልበታቸው የጎላ ልዩነት የለውም፡፡ ይልቁንስ በጎ ልዩነት የምናመጣውና በሽታውን የምናሸንፈው የፖለቲካ አንድነት ወይም ሕብረት በመፍጠርና ለሰላም ዕድል በመስጠት ነው፡፡ ለሁሉም ጊዜ አለውኮ!! በምርጫ፣ በጉልበትም ሆነ በሴራ አሸንፎ ሥልጣን ለመያዝም፣ በውስጥ ሽኩቻ መንበር ለመቆናጠጥም፣ የክልል ማዕረግ ለማግኘትና ለመንፈላሰስም፣ ወይም የፈለግነውን የብሔር ማንነትና የራስ አስተዳደር ለመጎናጸፍም ሐገርና ሕዝብ በጤናና በሕይወት መኖር አለባቸው፡፡ የሐገርና የሕዝብ ጤናና ሕይወት በሚታይ አደጋ ላይ ወድቆ ይህ ግድ ሣይሰጠን ለፖለቲካና ኢኮኖሚ ፍላጎታችንና ለግል የበላይነትና የሥልጣን ጥማችን ብቻ መደናበር ራሱ የጤና ሊሆን አይችልም፡፡ እዚህ ላይ የሚመለከተው ሁሉ ልብ ሊገዛ ይገባል፡፡ የጋራ ችግር እንደተጋረጠበት ዜጋ ሁላችንም አቅማችን በሚፈቅደው ሁሉ ርብርብ አድርገንና ከኛ የሚጠበቀውን ፈጽመን ሕዝባችንና ሐገራችን ወረርሹኙን እንዲያሸንፉ፣ እንዲረጋጉና ወደተጀመረው የለውጥና የዕድገት ጎዳና በተቻለ ፍጥነት እንድንመለስ መተጋገዝ አለብን፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዘመነ ፍዳው እንዲያጥር ለምትፈልጉ ወገኖች ሁሉ!

 

የመጨረሻው አማራጭ

በሕዝብ በጤና የመኖር መብት ላይ ቁማር በሚጫወት ሁሉ ላይ እና ገደብ ባጣ ሕገወጥነት ላይ ተመጣጣኝ ኃይል የመጠቀም ሕገመንግሥታዊ ብቸኛ ሥልጣን ያለው በተለይ የፌዴራል መንግሥቱ እርምጃ ሊወስድ ይገባል፡፡ እርግጥ በአንድ ድንጋይ “ዘጠኝ ወፍ” ሊሆንበት ነው፡፡ በታሪክ ሂደት አንዳንዴ ይህን መሰል መዋከብ ማጋጠሙ ያለና የሚኖር ነው፡፡ ስለዚህ የኃገሪቱን ኃብት አስተባብሮ ኮሮናን ለመዋጋት እንዳይቻል ግልጽ እንቅፋት የሚሆኑትን ጉዳዮችና ኃይሎች በከፍተኛ ፍጥነትና ቁርጠኝነት ልክ ሊያስገባቸው ይገባል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም ወቅታዊነትና ተገቢነት እዚህ ላይ ነው፡፡ ከዚያም ወደ ዋናው ሥራ ማለትም ወረርሺኝና መቅሰፍቱን የመዋጋቱን ሥራ ወደ ማስተባበርና መምራት ሥራ መመለስ አለብን፡፡ ከዚያ ደግሞ … (በምልከታዬ ላይ የጎደለውን ሙሉበት፣ የጎበጠውን አቅኑት)፡፡

ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ሕዝቧን  ከሁሉም ዓይነት መቅሰፍት ይታደግልን!!

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share