የዛሬ ወሬዎችና መጪው ጊዜ – መሳይ መኮነን

ኦፌኮ በምስራቅ ሀረርጌ አያሌ ሺዎች በተገኙበት የምርጫ ቅስቀሳ አደረገ። ኦነግ በሚሌኒየም አዳራሽ ደጋፊዎቹ ጋር ጉባዔ አካሄደ። ኢዜማ በአዲስ አበባ በተለያዩ ወረዳዎች ቅስቀሳውን ቀጠለ። ልደቱ አያሌው ለኢዜማ እውቅና እንዳይሰጠው ምርጫ ቦርድን ጠየቀ። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በደቡብ አፍሪካ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ጋር በስታዲየም ተወያዩ። እስክንድር ነጋ በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል የጠራው የፓርቲ መስራች ጉባዔ ተከለከለ። ሆቴሉ ተደራቢ የሙዚቃ ዝግጅት በመኖሩ ለሌላ ቀን አስተላልፉት አልኩ እንጂ አልከለከልኩም ሲል አስታወቀ። እስክንድር ”ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ” የተሰኘ ፓርቲ መመስረቱን ከተከለከለው አዳራሽ ውጭ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ይፋ አደረገ። ወለጋን ከኦነግ ሸኔ ርዝራዥ የማጽዳቱ ዘመቻ ተጠናክሮ በመካሄድ ላይ ነው። የደምቢዶሎው የተማሪዎች እገታ ላይ የመንግስት መግለጫ በማስረጃ የተደገፈ ባለመሆኑ ቅሬታን ፈጠረ። ሌላም …ሌላም።

ኦፌኮ በአንድ እግሩ ምርጫ ላይ ቆሟል። በሌላኛው እግሩ ደግሞ ከአንድነት መንግስት ውጪ የአብይ ብልጽግና ብቻውን መንግስት የማይሆንበትን የትኛውንም እንቅስቃሴ በማድረጉ ላይ በእጅ አዙር እየሄደበት ነው። ኦነግን የተጣመረበትና የኦሮሞ ሚዲያ ኔትወርክ ባለቤትን ወደ ፓርቲው ያስገባበት ምክንያት ምርጫን ብቻ ታሳቢ በማድረግ ነው የሚለው ግርድፍ ድምዳሜ ስህተት ነው። ምርጫ ከመካሄዱ በፊት የአንድነት መንግስት ጥያቄ ጤናማ አይደለም። ካላሸነፍን አልያም የአንድነት መንግስት ካልተቋቋመ ሀገሪቱን በቀውስ ሲጥ እናደርጋታለን የሚል መልዕክትም ያዘለ ይመስላል። ለዚህም ፓርቲውን የተቀላቀለው የኦኤም ኤን ባለቤት ”election has consequences” ብሎ ቀድሞ ነግሮናል። ዶ/ር አብይና ፓርቲያቸውን ጥምብ እርኩሳቸውን እያወጣ በገለጸበት በቅርብ ጊዜው ቃለመጠይቅም ለአቅመ መንግስት የሚያበቃ ወንበር ካነሳቸው እንኳን ከህወሀት ጋርም ቢሆን ተጣምሮ ቤተመንግስት ለመግባት እቅድ እንዳለው አስታውቋል። ህወሀትን መጣመር ኢትዮጵያ ላይ መዓት ከማምጣት ያለፈ ትርጉም የለውም። ፕ/ር ህዝቄልን ከጀርባው ያነገበው የኦፌኮና የኦነግ ጥምር ጉዞ በምርጫ ለማሸነፍና ካልተሳካም ለመጪው ምርጫ ለመዘጋጀት ነው ብሎ የሚጃጃል ያለ አይመስለኝም። ምርጫን ማሸነፍ አልያም ሞት ብሎ ከተነሳው ጥምረት የሚጠበቀው ምን ሊሆን እንደሚችል የኢትዮጵያን ፖለቲካ በቅርበት ለሚከታተልና የኦሮሞ የፖለቲካ ድርጅቶችን አካሄድ ለሚመረምር ተመልካች በቀላሉ የሚረዳው ነገር ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሃገራችን ኢትዮጵያ በፈረንጆች ኣዲስ ዓመትስ? -ገብረየሱስ!

ኦፌኮ ምስራቅ ሀረርጌን በደጋፊዎቹ ሲያጥለቀልቅ ኦነግ ደግሞ ደጋፊዎቹን በአውቶቢስ ጭኖ ከተለያዩ የኦሮሚያ ክልል አከባቢዎች አዲስ አበባ በማስገባት በሚሌኒየም አዳራሽ ጉባዔውን አካሂዷል። ኦነግ በአዲስ አበባ ጉባዔ የመጥራት መብት እንዳለው እሙን ነው። አዲስ አበባ የሁሉም ኢትዮጵያዊ መዲና እስከሆነች ድረስ። ሆኖም ወለጋን በእጅ አዙር እያመሱ አዲስ አበባ ላይ ለምርጫ የሚሆን ግርግር መፍጠሩ ግምት ላይ ይጥላል። በመሰረቱ ”አዲስ አበባ የኦሮሞ ናት” የሚል የቁም ቅዥት ውስጥ የሚንሳፈፈው የኦሮሞ ኢሊቶች አደገኛ አካሄድ የገፋው እንጂ አዲስ አበባ ለኦነግ የምርጫ ቅስቀሳ ትክክለኛ ቦታ ሆና አይደለም። ኦነግ አሁን ካለው ቁመና አንጻር ከወለጋ ውጪ የመራጭ ውክልና የለውም። እንኳን አዲስ አበባ ቀርቶ ጂማ፡ አዳማ፡ ባሌና በበርካታ አከባቢዎችም የኦነግ ህዝባዊ መሰረት የላላና በሌሎች የኦሮሞ ድርጅቶች የበላይነት የተያዙ ናቸው። በቀላል ስሌት ካሰብነው ደግሞ ጥቂት በማይባሉ የኦሮሚያ ክልል ከተሞች የኢትዮጵያ ብሄርተኝነትን የሚያቀነቅኑና በዜግነት ፖለቲካ ላይ የተመሰረቱ ሃይሎች ከኦነግ የበለጠ ተቀባይነት አላቸው። እናም የኦነግ የአዲስ አበባው የዛሬው ግርግር የምርጫ ቅስቀሳ አካል ከመሆኑ ይልቅ ”አዲስ አበባ ኬኛ” የሚለው ቅዠት ማሳያ መድረክ ነው ማለት ይቻላል።

ኢዜማ ድምጹን አጥፍቶ እየሰራ ይመስላል። ከሰሜን መቀሌ እስከደቡብ ሀዋሳ፡ በመሀል አዲስ አበባ እያደረገ ያለው ቅስቀሳ ከሌሎች ፓርቲዎች በተሻለ እየተንቀሳቀሰ እንደሆነ የሚያመላክት ነው። ከእነጉድፎቹም ቢሆን ኢዜማ ሀሳብ ላይ ያተኮረ፡ ከዘርና ጎሳዊ አመለካከት የራቀ ፖለቲካዊ ፉክክርን የመረጠ ለመሆኑ በየከተሞቹ ከሚያደርጋቸው እንቅስቃሴዎች መረዳት ይቻላል። ለእኔ የዜግነት ፖለቲካን የሚያራምድ የትኛውም የፖለቲካ ድርጅት ምርጫዬ ነው። ኢትዮጵያን በጎሳ ከረጢት ውስጥ አስገብቶ ዲሞክራሲንና ፍትህን አመጣለሁ የሚል የፖለቲካ ሃይል ቀድሞውኑ ባይፈጠር እመርጣለሁ። ከተፈጠረም እንዳይሳካለት ምኞቴ ነው። ለኢዜማም ሆነ በኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት ላይ ለተቋቋሙ ቡድኖች ያለኝ አወንታዊ አመለካከት ከዚህ መርህ ብቻ የመነጨ ነው። እነልደቱና ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት የመሰረቱት ”አብሮነት” ከመጠላለፍ ወጥተው፡ ቀውስ ከማራገብ አጀንዳ ርቀው፡ ባነሷቸው ኢትዮጵያን የማዳን አቋሞች ላይ ትኩረት በመስጠት ቢሰሩ እኔን መሰል ደጋፊ ማግኘታቸው አይቀርም። ኢዜማ ፍቃድ አይሰጠው የሚለው የልደቱ አዲሱ ነጠላ ዜማ ባለቀ ሰዓት መለቀቁ አብሮነታቸው የፖለቲካ ስልጣን ለመያዝ ያለመ ሳይሆን ባይሳካም እንኳን ሌላውን ጠልፎ ለመጣል በመሆኑ ለደጋፊዎቻቸው ቅስም የሚሰብርና ያልተጠና እርምጃ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኢቲቪ “ያልተገሩ ብዕሮች” ዘጋቢ ፊልምና ያልተገራው አቀራረብ (ነቢዩ ሲራክ)

የእስክንድር የዛሬው ውሎ በእጅጉን ስሜቴን ነክተውታል። የእስክንድር ዓላማ ምንም ይሁን ምን የተጠራው ስብሰባ መደናቀፍና መከልከል የለበትም። ኦነግ አዲስ አበባ ላይ አሸሼ ገዳሜ እያለ፡ እነኢዜማ ያለከልካይ እንዳሻቸው ቅስቀሳ እያደረጉባት ባለችው ከተማ እስክንድርና ደጋፊዎቹን መሰብሰቢያ ቦታ መከልከል በየትኛውም መለኪያ ተቀባይነት የለውም። ጉዳዩን በተመለከተ በግሌ ለማጣራት ሞክሬአለሁ። የአዲስ አበባ ፖሊስ ም/ኮሚሽነር ዘላለም መንግስቴ ጋር ተደጋጋሚ ስልክ ደውዬ አልተሳካልኝም። አዲስ አበባ ከንቲባ ጽ/ቤት የፕሬስ ሴክሬተሪያቷን ግን በስልክ አዋርቼአታለሁ። የበላይ አካል ከልክሏል የሚባለው ትክክል አይደለም ብላኛለች። ምክንያቱን ራሱ ሆቴሉ መግለጫ ይሰጥበታል በማለት የስልክ ንግግራችን ተቋጭቷል። ኋላ ላይ የሆቴሉን መግለጫን ሰማሁት። ቀልድ ነው። እንዲህ ዓይነት ሰበብ ለፖለቲካችን አይመጥንም። ከዚህ ቀደም እስክንድር የጠራቸው መድረኮች የተከለከሉበት ምክንያትን በተመለከተ አንዳንድ ለአደባባይ መብቃት የማይችሉ ጉዳዮች ስላሉ እዚህ ላይ ማንሳት አያስፈልግም። የዛሬው ግን ፈጽሞ ተገቢ አይደለም። ለማርተኞችና ቀውስ ጠማቂ ዩቲዩበር ሚዲያዎች የወሬ ቀለብ ከማቀበል ያለፈ አንዳችም ጥቅም የለውም።

ማጠቃለያ

መጪውን ጊዜ በተመለከተ የእኔ አቋም ነው። የመጀመሪያው አቋም ምርጫው በዚህን ወቅት ባይካሄድ የሚል ነው። መንግስት ከቆረጠና ምርጫ ቦርድም ተዘጋጅቼለሁ ብሎ ከወሰነ ግን የሆነ ነገር መደረግ ያለበት ይመስለኛል። የዚህ ምርጫ ትልቁ ስኬት መሆን የሚገባው ሰላማዊ መሆኑ ብቻ ነው። የ2012 ምርጫ ሀሳቦች የሚፋጩበት፡ ስልጡን የሆነ የምርጫ ፉክክር የምናይበት አይደለም። ለዚያ የተዘጋጁ በጣት የሚቆጠሩ ፓርቲዎች ካልሆኑ በቀር አብዛኞቹ ጡንቻቸውን ተማምነው፡ ቀውስን ግብ አድርገው የሚንቀሳቀሱ ናቸው። አንዳቸውም የኢኮኖሚም ሆነ መሰል አማራጭ ሀሳቦች የላቸውም። ፕሮግራም እንኳን ቀርጸው የሚንቀሳቀሱ አይደሉም። አንድዬና ብቸኛ የምርጫ መቀስቀሺያ አጀንዳቸው ጥላቻ ነው። ግባቸው ወንበር አግኝተው ኢትዮጵያን በፈለጓት መልኩ ከእንደገና ጠፍጥፎ መስራት ካልሆነም መበታተን እንጂ ከዛ ያለፈ አጀንዳ የላቸውም። ኢትዮጵያ እነዚህ ሃይሎች የፖለቲካ ስልጣን ከያዙባት ብትንትኗ መውጣቱ የማይቀር ነው። ኦነግና ጥምረቱ ኦሮሚያ ክልል ላይ መንግስት ሆኖ፡ ህወሀት ትግራይን ይዞ፡ ሌሎች ጽንፈኛ ሃይሎችም እንደየድርሻቸው ወንበር አግኝተው የሚያጠናቅቁት ምርጫ ከሆነ በማግስቱ ኢትዮጵያ ስለምትባል ሀገር ማሰብ ቂልነት ነው። ይህ ምርጫ ኢትዮጵያ እንደሀገር ትቀጥል ወይስ የዩጎዝላቪያ ዓይነት ትንንሽ ሀገራት ወደምትሆንበት ምዕራፍ ጉዞ ትጀምር የሚል ምርጫዎች የቀረቡበት ምርጫ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ወያኔ በአምሳሉ የፈጠረው የአየር ሃይል ሲፈተሽ | አርበኞች ግንቦት 7

የኢትዮጵያ ህዝብ ኢትዮጵያን የማዳን እድሉን በእጁ ይዟል። በዚህ ምርጫ በሚሰጠው ድምጽ የኢትዮጵያን ህልውና ያረጋግጣል። በግሌ ይህ ምርጫ ዲሞክራሲያዊ፡ ፍትሃዊ ምናምን የሚሉት መገልጫዎች የቅንጦት ይመስሉኛል። ብልጽግና ፓርቲ የ2012ቱን ምርጫ ሰላማዊ ብቻ እንዲሆን በማድረግ ለሚቀጥለው ለ2017 ኢትዮጵያን ማዘጋጀት ይኖርበታል። በግርግር ወንበር ይዘው ሀገሪቱን ወደትርምስ ለመክተት ቀን ከሌሊት የሚሰሩ ሃይሎች በሚርመሰመሱባት ኢትዮጵያ ስልጣን ላይ ያለው መንግስት ትልቅ ሃላፊነት አለበት። ጫጫታ ሊፈጠር ይችላል። ድምጻችን ተሰረቀ የሚል እስከ ቀውስ የዘለቀ ማዕበል ሊቀሰቅሱ እንደሚችሉ ይገመታል። ለእነዚህ ሃይሎች በምርጫ ስም ሀገሪቱን አሳልፎ ከመስጠት የበለጠ ቀውስ ግን ኢትዮጵያ ላይ እንደማይፈጠር መታወቅ አለበት።

እናም ብልጽግና ፓርቲ ይህን ምርጫ ሰላማዊ ሂደቱን ጠብቆ እንዲካሄድ በማድረግ በሚቀጥሉት አምስት አመታት ምርጫ ቦርድን ጨምሮ ሌሎች የዲሞክራሲና የፍትህ ተቋማትን ገለልተኛ ተቋማዊ አቅም ገንብተው ለዲሞክራሲያዊና ፍትሃዊ ምርጫ እንዲዘጋጁ ቃል ገብቶ ሀገር የመምራት ሃላፊነቱን ሊቀጥል ይገባል። መጀመሪያ ኢትዮጵያ መቀጠል አለባት። ይህ ምርጫ ኢትዮጵያን አረጋግቶ የማስቀጠል ሃላፊነት ለብልጽግና ፓርቲ ከመስጠት ያለፈ ውጤት እንዲኖረው መደረግ የለበትም።

(በሀሳብ ለሚሟገት የውይይት መድረኩ ክፍት ነው። የስድብና የዘለፋ አቁማዳውን ሸክፎ ገጼ ላይ ለሚመጣ ግን ጆሮ ግንዱን ብዬ እስከማባረር የደረሰ በፌስቡክ የተሰጠኝ መብት እንዳለኝ ለማስታወስ ያህል ነው

2 Comments

  1. Mesay said:
    “ኦነግ አሁን ካለው ቁመና አንጻር ከወለጋ ውጪ የመራጭ ውክልና የለውም። እንኳን አዲስ አበባ ቀርቶ ጂማ፡ አዳማ፡ ባሌና በበርካታ አከባቢዎችም የኦነግ ህዝባዊ መሰረት የላላና በሌሎች የኦሮሞ ድርጅቶች የበላይነት የተያዙ ናቸው። በቀላል ስሌት ካሰብነው ደግሞ ጥቂት በማይባሉ የኦሮሚያ ክልል ከተሞች የኢትዮጵያ ብሄርተኝነትን የሚያቀነቅኑና በዜግነት ፖለቲካ ላይ የተመሰረቱ ሃይሎች ከኦነግ የበለጠ ተቀባይነት አላቸው።”

    እንዴት አባትክ አወቅሀዉ ወንዳገረድ? ማስረጃህን ከዲሲ ሥጋ ቤቶች ነዉ ያገኘሀዉ፧ ወይስ ኦሮምያ ያውም ወለጋ ሂደህ ነዉ?

  2. Liji Messy, don’t you think that we had enough about the dirty political game being played by those so-called EPRDF’s reformists who are getting more cynical and stupidly hypocritical and conspiratorial after a few months of their ascending to the throne in the Arat Kilo palace? Don’t we had enough to be the advocates of these types of disingenuous and deceiving politicians of ethnocentric politics whose hands are badly stained with the blood of thousands of innocent Ethiopians ? Don’t the people of Ethiopia deserve much better than this sir? I know you are a good Ethiopian . But I have to say that you are damaging that goodness by allowing yourself to continue as a defender of those who continued playing the political game of EPRDF with different names and highly cynical way of reorganization ( prosperity) . You say Whatever Eskindir’s aim or goal or objective may be . Why you seem reluctant or hesitant to say that there is nothing wrong with the very effort and objective of Eskindir than paying high price for the sake of exercising the very basic political and human rights of citizens ? Is there any dirty and dangerous political game than forcing innocent citizens not use the meeting hall they paid for and gather in the streets of their own home city in order to form their party ? Why you are you afraid to strongly condemn this extremely idiotic political behavior and action of those EPRDF’s reformists who have no areal sense of regret and confession for what they have done to the innocent people of Ethiopia for a quarter of a century ? Why you seem loosing your moral strength to say that Eskidir has done and is not doing wrong as far as the very political reality in the country is concerned . And that reality is nothing but the very dirty political game of EPRDF/prosperity that desperately needs to be peacefully and democratically challenged . That is what Eskindir is doing ! Nothing hidden! So, if you are not courageous enough to say what is crystal clear but keep going around the bush, I am afraid you are ruining your own professional as well as social credibility !
    With all due respect sir! L

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share