ሀገሬን ሰላም ያሳጣት፣  የፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች እና የሴራ ፖለቲከኞች ህቡ ግንባር መሆኑ መታወቁ በራሱ ታላቅ ድል ነው

  መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ
  በአንደበታቸው ጤፍ የሚቆሉ ፣ግባቸው በአላዋቂዎች ጭፍን ድጋፍ  የመጨረሻውን ሥልጣን መጎናፀፍ የሆነ፣ለዚህም ሥኬት ተጨባጩን የህዝብ ንቃተ ህሊና የኑሮ ና ባህል ሁኔታ እንደመሠላል የሚጠቀሙ፣ የተዋጣላቸው የፖለቲካ ትያትረኞች  በአንድ ወገን ፤ ኢትዮጵያን ወደማያባራ ግጭት በመክተት ከልማታዊ ተግባሮ በማሠናከል ጥቅማችንን ማሥጠበቅ እንችላለን ባዮች በሌላ ወገን ሆነው ፣ በዚች የሰው ዘር መገኛ አገር እየተተራመሱ ነው።
    (ሁላችንም አፋር ነን።ሁላችንም አፈር ነን።የዓለም ህዝቦች ሁሉ ኢትዮጵያዊያን ነን።)
    እናም  ትርምሱ ቀጥሏል።አንደኛው ሥልጣን ወዳድ ኃይል፣ማን ከማን ያንሳል በሚል ሥሜት ከመተባበር ይልቅ ፣ዛሬም “ቋንቋ ወይም ሞት !” እያለ ይነጣጠላል። ይነጣጥላል።
    ሌላኛው  በኢትዮጵያ መጥፋት እንዲያልፍለት  ቆዳውን በሚያዋድደው የፖለቲካ ልሂቅ እና በግብዙ ጎሠኛ አማካይነት የእርስ በእርሥ ጦርነት እንዲነሣ  በእጅ አዙር ገንዘብ ከፍሎ ብጥብጥ እና ሽብርን በመፍጠር “መንግሥት የዜጎችን ደህንነት መጠበቅ እንኳን አልቻለም። “በማሰኘት ተጨማሪ ወከባ እንዲፈጠር ያደርጋል።አንደኛው እና ሁለተኛው እየረፉ ፣ትንፋሽ እየወሰዱ፣በመደጋገፍ ሌላ ሁከት፣ሌላ ብጥብጥ፣ሌላ ሽብር ያለማቋረጥ  እይደግሱ መሸሻ ፣ መጠጊያ ና መከላከያ የሌለውን ህዝብ መከራውን ያሥበሉታል።
    የሽብር ድግሱ  ሰለባም  ወይም  ግንባር ቀደም ተጠቂ ፣ኑሮው ከእጅ ወደአፍ የሆነው  ምንዱባኑ ነው።ይሁን እንጂ ፣ማንም ወርዶ ያለአንዳች ድራማ እንዴትነህ? ወቅታዊው የፖለቲካ፣የኢኮኖሚ እንዲሁም የማህበራዊ ሁኔታ በአንተ ኑሮ ላይ ያሥከተለብህ ተፅእኖ አለን?ብሎ የሚጠይቀው ወይም በደምሳሳው እሳት ብርቅ የሆነበትን ጎጆውን በመቅረፅ ፣ የወገንህ ኑሮ ይህን ይመሥላል ብሎ በፀፀት ወደቀልባችን እንድንመለሥ የሚያደርግ የቀጥታ ሥርጭት የሚያቀርብ የቴሌቪዢን ጣቢያ የለም።( ታች ወርዶ ለመሥራት ፍቃደኛ ቢሆኑም እንደልብ ለመንቀሳቀሥ የፀጥታው ሁኔታ ያገዳቸው ሚዲያዎች እንዳሉ ባንዘነጋም።)
     እባካችሁ ኃቀኛ የቴሌቪዢን መሥኮቶች፣ ምንዱባኑ  እየኖረ ያለውን የሰቆቃ ህይወት  በግልፅ ይተርክ ዘንድ እስቲ ለራሱ  መድረኩን ልቀቁለት።  በእያንዳንዱ ጓዳ ያለውን ሰቆቃ ፣እንግልት ፣ወከባ፣እሥር ወዘተ  ዜጋው ይተርከው ዘንድ መድርክ አያገኝም። ግና የጠገበው ፖለቲከኛ እና ያገባኛል ባይ አፈኛ እና ብዕረኛ ወይም የእርጎ ዝንብ ወይም የጠላ ትንኝ፣ ልክ በራሱ ላይ እንደደረሰ እየተንዘረዘረ በየቴሌቪዢን መሥኮቱ እና በየሚዲያው ብሶት ሲያወራ ሁሌም  ይዳመጣል።
    በቀቢፀ ተሥፋ ለዘለዓለም ዓለም፣ “ዶሮ ማታ” እየተባለ የሚኖረው ምንዱባን ( ኢዬቻ) የየደቂቃውን ውሎ ና አዳር  አመዛዛኝ ህሊና ላላቸው የዓለም ህዝቦች ሁሉ  መተረክ እንዳይችል ጋሬጣ መሆናችሁን እናንተ ብትክዱም ሥልጡኑ ዓለም በረቀቀው ቴክኖሎጂ ሥለምንዱባኑ የሰቆቃ  ኑሮ ጠንቅቆ ያውቃል። “የጠላ ትንኞቹ” የየምጅላቶቹን አሥከሬን እያወጡ ከሚያሥለቅሱት ይልቅ ፣ የዛሬ ና የአሁን የኑሮ እሳት እየጠበሰ የሚያሥለቅሰው ተጨባጩን የዘወትር አበሳ ና የህይወት እንግልት ለመቀልበስ የሚችልበትን መንገድ ለምን አያመላክቱትም።
    የምንዱባኑ የባዶ አንጀት ጩኸት ፣ ከእናንተ ተረት ፣ ተረት አሥቀድሞ መፍትሄ እንደሚሻ እያወቃችሁ ፣ ምቾታችሁን እና ድልቅቄያችሁን  በገሃድ እያሳያችሁ በቋንቋው በመፎገር፣ “ለአንተ ቆመናል። ፣የነዛ ምንጅላቶች የአንተ ጠላት ነበሩ።” ብትሉት  አይሰማችሁም።   ቆሻሻ ትርክታችሁ ለእናንተ እና  ለአፈ ጮሌው ፖለቲከኛ በትርምሥ ውሥጥ መሽሎኪያ የሥልጣን መንጠላጠያ ዘዴ እንጂ  ለደሃው ህዝብ የሆዱን ጩኸት  ማሥቆሚያ መላ እንዳልሆነ አሥቀድሞ ያውቃል። ከፍትህ አንፃርስ ቢሆን “ልጅ በአባቱ ሐጥያት ይቀጣል እንዴ?…ኦሪታውያን …የፍትህ መቃብር ሁላ!”
     ፍትህ በቦታዋ ብትኖር ኖሮ ፣ እያንዳንዱ ሰው መብቱን ከግዴታው አንፃር በመገንዙብ ለንግግሩ ሉጋም ያበጅለት ነበር። ህዝብም በመገናኛ ብዙሃንና በማህበራዊ ሚዲያ፣ በበሬ ወለደ ኡኡታ! የውሻ ሞት አይሞትም ነበር።
    በግልፅ እንደሚታየው በኢትዮጵያ፣የመገናኛ ብዙሃን ፣የጥላቻ ጦርነት ማሥጀመሪያ  ፊሽካ የሚነፋባቸው ሆነው መገኘታቸው እሙን ነው።የቋንቋውን  ፖለቲካ ተቆጣጥረው ግፋ በለው፣ውረድ በለው ግደል ተጋደል በርታ ወገኔ፣በጎሣ አጥንት በቋንቋህ ወኔ”እያሉ “የአንድ ቋንቋ ተናጋሪ ሞት በሺ ቋንቋ ተናጋሪ ሞት ይመነዘራል።”የሚል የሴጣን መፈክር እያሰሙ ፣ከሥሌት ይልቅ ለሥሜት ቅርብ የሆነውን ወጣት ከጎናቸው ለማሰለፍ የሚቀሰቅሱም ዛሬ ፍትህን ገድለው፣  ለታላቅ የአጥፊነት ሥኬት በቅተዋል።
     እርግጥ ነው፣  በግል ቴሌቪዥኖቻቸው ሣይቀር  የሚፈልጉትን የፖለቲካ አጀንዳ የሚያራምዱ አሉ።የምርጫ ቅስቀሳው ከወዲሁ ተጧጡፏል። ያውም በተረት ተረት እና በእንካ ሠላንትያ ታጅቦ!
     አንዳንዶች  እጅግ ሳቢ በሆነ አቀራረብ የጎላ ርዕሥ ሰጥተው፣ በሚጥም አንደበት፣እንደዝነኛ የመድረክ ሰው፣ ልብ አንጠልጣይ ተረት ለልጆች እንደሚያወሩ ሁሉ አንገታቸውን በየአራቱም ማዕዘን አሥሬ እያዞሩ፣ ግንባራቸውን በማኮሳተር፣ አይናቸውን በማጉረጥረጥ ፣ከንፈራቸውን በመንከሥ፣ጥርሳቸውን ለዓመል ቢሊጭ እያደረጉ፣ በእጃቸው ንቅናቄ ፣የማትታለብ ሆኖሞ ትልቅ ግት ያላት ላም በሰማይ ላይ ሥለው በማሳየት ፣  ”  አየሃት የወደፊቷን ላማችንን ፣እኔ ያንተ ቋንቋ ተናገሪ እና የአንተ ቋንቋ ተሟጋች ሥልጣን ስይዝ በዚች ላም ወተት አጠግብሀለሁ።  ግቷን አየኸው አይደል። እንኳን ለአንተ ለዓለም ይተርፋል።እናም እኔ ሥልጣን እንድይዝ ግደል።ተጋደል።ሥልጣን ይዤ ታላቋን’ ….’ከመሠረትኩ  በኋላ ከእኛ ቋንቋ ውጪ የሚናገረውን ጠራርገን ገደል በመክተት ነፍጠኞች ህልም ነው የሚሉትን ወተት ለብቻችን እንጋታለን።ያን ጊዜ  ያቺ ሰማያዊዋ ላም ወተቷን ለማን እንደምትሰጥ ጠላትም ወዳጅም ይገነዘባል።… ” በማለት፣ከቤተሰብ ጥገኝነት ተላቆ ፣እንጀራ ቆርሶ ለመብላት የሚፈልገውን  ግን፣ግን ሥራ ማግኘት ሆነ የዕለት ጉርስ ማግኘት ከባድ የሆነበትን ወጣት ፣ በቀቢፀ ተሥፈ እንዲሞላ እያደረጉት እንደሆነ ሳይ፣ምነው የዚህ ትውልድ አባል የሆነው ጥቂት ወጣት እንዲህ ተጃጃለሳ?የጥንቱ የቀኃሣ ትውልድ ወጣት እኮ አባቱ ” ተመልከት ሰማይ ላይ ጤፋ ሲወቃ…” ቢለው ልጅየው” እብቁ አይኔ ውሥጥ ገባ።እሥቲ ና አውጣልኝ። ” ብሎ በውሸት እንኳ እንደበለጠው አልሰማም እንዴ!?።ይህንን በቀቢፀ ተሥፋ የተሞላውን   ውሸታሙን ፖለቲከኛ በውሸት ባንበልጠው እንኳን የፀሐይ ዮሐንሥን “ሥጥ እንግዲህ” የተሰኘውን ዘፈን  በመዝፈን ይህንን በጥራቃ እንዴት አፉን ማሥያዝ ያቅተናል???(በእርግጥ ለሰጪው በሰጠህ ልክ ልትሰጠው ይገባሃል።)
    በቀቢፀ ተሥፋ የተሞላውን ፖለቲከኛ በፀሐዬ ዘፈን ልናሥቆመው ይቅርና  ፣በማይገመጥ የህልም ዳቦ ፣ ጠርሙሱ ተሰብሮ የፈሰሰ ውሃ እንደገና ጠርሙሱ ህያው ሆኖ ፣ ውሃውም በውሥጡ ሞልቶ ፣ እጠጣዋለሁ ብሎ አይኑን አፍጥጦ ሲያልምና ህልሙንም አመዛዛኝ ህሊና ለሌላቸው ሢያጋባና  ይህንን እብደት ከጎዳ ወደሳሎን ፣ከሳሎን  ፣ወደሰገነት፣ከሰገነት ወደጎዳና ይዞ ሲወጣ ልናስቆመው አልቻልንም።
    ይህንን በምላሱ ጤፍ ቆይ እንኳን እኛ ቀርቶ ተመጣጣኝ ኃይል በህገወጦች ላይ የመጠቀም መብት ህግ ያጎናፀፈው አሸጋጋሪው መንግሥት  ሊያሥቆመው አልቻለም።ህጉ የሰጠውን የህግ ሉጋም ከመጠን በላይ ሥለአላላው እንዴት አድርጎ ወቅታዊ ምላሽ በፍጥነት ይስጥ ?
  ትላንት በህዝብ ሥም ሥልጣን ይዘው የነበሩ የቅርቦቹ መንግሥታት (ደርግ እና ህወሃት ኢህአዴግ ) ለምንዱባኑ የከተማና የገጠር ንዋሪ ከቤተሰቦቻቸውና ከራሳቸው የበለጠ  ያደረጉለት አንዳች አንጀት የሚያርስ ነገር ባይኖርም ፣ ህግን በማሥከበር አንፃር አይታሙም። ህወሓት ኢህአዴግ ያልኩት የመለሥን ኢህአዴግ  እንደሆነ ይሰመርልኝ።(ከብዝበዛ አንፃርም ደርግና ህወሓት  ጫማና ኮፍያ ናቸው)
   የዛሬው አሻጋሪ መንግሥት (በታሪክ አጋጣሚ የተሸከመውን አደራ እንዳትዘነጉ) ደግሞ ፣ ቀድሞ የዘረፉት፣ የደም ገንዘብ ያልበቃቸው  በኢትዮጵያዊያን መሥዋትነት ሃጥያታቸው የተሠረየላቸው እና ወደሀገራቸው የገቡ ፓለቲከኞች እና አክትቪሥቶች ይህቺን ሀገር ሦርያ ለማድረግ ያለእንቅልፍ እየሰሩ እና እያሤሩ  እንደሆነ፣ ብልሆች  ያሥተውላሉ።
    “ለምንዱባኑ  ህዝባችን፣ ለዚህ እና ለዛ ቋንቋ ተናጋሪ ሦሥት ጊዜ መብላት ነው፣የምንጨነቀው ። “እያሉ  ከደርግ ጀምሮ ሲንከባለል የመጣ ያለፈበት፣የነፈሰበት የካድሬ ፉገራ እየተጠቀሙ ውሥጥ ለውሥጥ ሀገር የማተራመሥ አጀንዳቸውን ያሠርፃሉ።
   በእውነቱ፣   እኛ  የምናምነው ፕሮፖጋንዳን ሳይሆን ምድር ላይ ያለውን ተጨባጩን እውነት ነው።  እውነቱ ኢትዮጵያን የማዳከም እና አቅመ ቢሥ የማድረግ አጀንዳ የዛሬ ሳይሆን የትላንት የፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች አጀንዳ መሆኑን ነው ።
     ኢትዮጵያን የማተራመሥ አጀንዳ፣ሰላም የማሳጣት አጀንዳ ፣ ቋንቋ፣ጎሣና፣ኃይማኖት ላይ አነጣጥሮ እርስ በእርስ የማበላላት አጀንዳ ፣ለዘመናት በፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ጠረንጴዛ ላይ የነበረ እና ዛሬም ያልተነሳ አጀንዳ መሆኑ ይታወቃል።(የአረብ ሊግ ለኢትዮጵያ ፖርላማ የፃፈውን ና  በአባይ ጉዳይ በቀድሞ ቅኝ ገዢዎች ውል መገዛት አለባችሁ።የሚል ለግብፅ አጋርነቱን የገለፀበትደብዳቤ ይህንን እውነት ያረጋግጥልናል።)
      በሀገር ውስጥም ከፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ባልተናነሰ፣ ይህቺን ሀገር አቅመ ቢሥ ለማድረግ የሚጥሩ እንዳሉ እያሥተዋልን ነው።እነዚህ የተለያየ ሺፋን ያላቸው ግለሰቦች ቡድኖች እና ሚዲያውች በምላሳቸው ጤፍ የሚቆሉ በቆዳቸው፣በአነጋገራቸው ኢትዮጵያዊያን ቢመሥሉ በተግባራቸው ግን የነዛ ወገን መሆናቸውን አሳይተዋል።
  ለማንኛውም፣እነዚህን ከወዲሁ መጠንቀቅ ይበጃል። በማለት ትሁት ምክሬን አቀርባለሁ።  ካልተጠነቀቅ ናቸው፣የኢትዮጵያን እድገትና ብልፅግናን ከማይሹ ጋር   በህቡ በማበር   ወደታላቅ   የማይቀለበሥ የግድያ ሤራ፣ ሊያመሩ ይችላሉ።ብለን ከወዲሁ መጠርጠር ብልህነት ነው።  ይህ ሴራ እንደሚኖር የጠረጠርነው እዚህና እዚያ ቢላዋ ሲሣል ጆሮአችን እየሰማ ሥለሆነ ነው። (በናዝሬቱ ታላቅ ሤራ ተገርመን ሳናባራ   በቅርቡ በፌደራል  ዩኒቨርስቲዎች የተከሰተው የንፁሐን ተማሪዎች ግድያ የቢላዋውን አሥከፊነት እንዳሳየን አንዘነጋም።)
     ይህ  ሲሳል  ፉጨቱ እየተሰማን ያለው  ቢላዋ መቼ እና በማን በኩል በታላቅ ሰው፣ አንገት ላይ እንደሚያርፍ ባላውቅም ፣ታላቁ ሰው “በጊዜ በቢላዋ ቀልድ የለም”  እሥካላሉ እና ህጋዊ እርምጃ እስካልወሰዱ ጊዜ ድረሥ ይኸ ሊፈፀም እንደሚችል እገምታለሁ።ይህን አሥደንጋጭ ፅሁፍ ጠቅላይ ሚኒሥቴሩ እንደሚያነቡትም እገነዘባለሁ፣እኔን እንደማኪያቬሊ ቁጠሩኝ እና እመኑኝ አልላቸውም።ሆኖም ግን በአገርኛው  ሊቅ በአቶ   ከበደ ሚካኤል ተረት ና ምሳሌ  “እጅግም ሥለት ይቀዳል አፎት፣እጅግም ዕውቀት ያደርሳል ከሞት።” በሚለው እውነታውን እንዲገነዘቡት በታላቅ ትህትና እለምናቸዋለሁ።(ማኪያቬሊ ለውዳሴ ሥትል ውግዘትን አታብዛ ይልሃል። ለቁርሥ ያሰቡህን ከቁርሥ በፊት የፊት መታጠቢያ ውሃ አርጓቸው ነው። ባጭሩ።)
    ጠ/ሚ  አብይ ተረት እና ምሳሌውንም ሆነ The prince የተሰኘውን የማኪያቬሊ ፅሁፍ በውል እንደሚያውቁት እገነዘባለሁ።እናም ለዚች መከራዋ ላላባራ ሀገር መፍትሄ ማምጣት የሚቻለው ሁሉም ሰው የህግ የበላይነትን ማክበር ሢችል እንደሆነ በተጨባጭ ማሳየት ካልቻሉ የኢትዮጵያ ህዝብ እጣው ጥርስ ማፋጨት እንደሚሆን ከወዲሁ ሊገነዘቡ ይገባል። ይህ እንዳይሆን ከሀገር አሌንታው መከላኪያ  ጋር  የተቀናጀ የህግ ማሥከበር ሥራ ሊሰራ ይገባል።ለፍትህ ልእልና ሊቆም ይገባል። በማለት ትሁት ምክሬን እለግሣለሁ።
    አሁን እንደማሥተውለው በአንዳንድ የሀገሪቱ ክልሎች በሥመ ፌደራሊዝም “ጋንጊሥተሮች “እንደግል አሽከሮቻቸው በሚቆጥሯቸው ሚሊሻዎች እና ጥቂት ፖሊሶች እንዲሁም በእሥርቤቶቻቸው በመመካት ፣ህዝቡን በማሸበር ጉልበት እና አቅም አልባ አድርገውታል። ለጊዜው።  የህግ የበላይነትን ለማሥፈን የግድ መከላከያው  ጣልቃ መግባት ይኖርበታል።…
      በነገራችን ላይ ፣ምርጫው በልዩ አሥቸኳይ ገዜ አዋጅ የሀገር መከላከያ ሠራዊቱ ፀጥታውን በማሥከበር  ካልተሳትፈ በሥተቀር ዴሞክራሲያዊ፣ነፃ፣ሰላማዊ እና ተአማኒ  ሊሆን እንደማይችል ከወዲሁ መገመት ቀላል ነው።
       ማንም  የግል ጥቅሙን እያጋበሰ በባለአምሥት ኮኮብ እና ቤተመንግሥት በመሰለ ቪላ በቅንጦት እየኖረ እና ቋንቋውን ለሚናገረው ሃማላ እና ጎዳና ላይ አዳሪ  ዱዲ ሳይቸር፣ ቋንቋዬ ጎሣዬ፣ወዘተ እያለ በህዝብ ደም መነገዱን ባፋፋመባት ሀገር፣ ሰላማዊ ምርጫ እንዲህ እንደዋዛ ሊደረግ አይችልም።
    ሜንጫን የሚበልጥ ክላሽ እና እሥናይፐር እንዳለህ ከወዲሁ ካላሳወቅኸውና በሰላማዊ መንገድ ተወዳድሮ በህዝብ ይሁንታ ብቻ ሥልጣን መያዝ አማራጭ የሌለው ብቸኛ መንገድ መሆኑን ኮስተር ብለህ ካላሳወቅኸውበሥተቀር ፣ቀድሞም ዓላማው በቢላዋ መጫወት ነውና  በቀላሉ ጠብ ሊያነሳሳ ብጥብጥ እና ሁከት ሊፈጥር ይችላል።ምርጫው ተጭበርብሯል ።አሸናፊው እኔ ነኝ።
     ይህንን መፃኢ እውነት የመላው ሀገሪቱ ዋሥ እና ጠበቃ የሆነው መከላከያ እና  የመከላከያ ኃይሉ የበላይ አዛዥ  በመገንዘብ  ፣ለልምጪም ጅራፍ እንዳለ  እና ሁሉም የፖለቲካ ሥልጣንን ለማግኘት የሚፎካከር በህግ አግባብ ቅሬታውን ለሚመለከታቸው የፍትህ ተቋማት ማቅረብ እንጂ፣በኮብል እሥቶን ፣በዱላ በሜንጫ ና ገጀራ ሥልጣንን ማግኘት ከቶም እንደማይቻል፣የሀገር መከላከያ ሠራዊቱ  ዛሬ ላይ ሆኖ የሀገር፣የመንግሥት እና የህዝብ አለኝታነቱን በተግባር ማሳየት እንደሚችል ማሥገንዘብ አለበት።
         ማን ነበር “አለንጋውን የደበቀ ልጁን መረን ይለቃል ያለው ???”…እውነቱን ነው።ለመልካም ሥራና ለጥረት ሽልማት እና ማበረታቻ እንዳለ ሁሉ፣ ለጥፋት እና ለብልግና ተመጣጣኝ  ቅጣት ግድ ነው።
     ህግ የማሥከበር ተግባር በወጉ ካልተካሄደ ከትላንት ወደ ባሰ ትርምስና መፈናቀል ይህቺ ሀገር መዘፈቋ አይቀርም።
      ከህግ በላይ በመሆን ፣ምክንያታዊ የሆነ አንዳችም   የርዕዮተ ዓለም ሀሳብ ሳይኖራቸው፣  ጭብጥ በሌለው፣” የቋንቋ አተካራ ”  ብቻ፣ ይህቺን ሀገር ለማጥፋት የሚጥሩ  ሴረኞች በቸልታ ሊታዩ አይገባቸውም።(ሥማ አንተ ቋንቋ፣ቋንቋ የምትለው፣በኦሥሎ የጠቅላያችን የሽልማት መደረክ “ቤቲጂን” ያጀቧት የኖርዌይ ዜጎች፣የኦስሎ ኮረዶች  አማርኛ ተናጋሪ ጎንደሬዎች ናቸው እንዴ።ቋንቋ መግባብያ ብቻ ነው።አታከብድ። እሺ።ቤቲጂዬ እግዜር ይባርክሽ። አንቺም ሳታካብጂ ላፈቀርሽው የኦሮምኛን ቋንቋ ብቻ ለሚያውቅ ኢትዮጵያዊ ወንድምሽ   ፍቅርሽን በቋንቋው ገልጠሽለታል።…በአንቺ  ዓይነት ጥበባዊ ገለፃ በተጨባጭ ተጋብተው የልጅ፣ልጅ ልጅ… አይተው የሚኖሩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን እንዳሉ  የታወቀ ነውና ዘረኝነት ይውደም !! ፍቅር ይንገሥ!! እንላለን።)
   በእውነቱ ሀገራችንን በእጅ አዙር እየናጣት ያለው የተቀናጀ የሴራ ፖለቲካ ነው።ቋንቋ፣ጎሥና ኃይማኖት የላይ ታሪኩ ቢሆንም ዋናው ታሪክ ሁለት ነው።አንዱ  ፣ ሥልጣንን አግኝቶ ለመንደላቀቅ ማሰብ  ሲሆን ሌላው በሐሰት ትርክት እና በፈጠራ ወሬ ሀገር እንዳትረጋጋ በማድረግ ፣ብልፅግናችን ህልም ሆኖ እንዲቀር በህዝብ ሥም እየማሉ በጀርባ የራሥን ሀብት ማከማቸት ነው።ሌላው ሁሉ የሐሰት ትርክት ሽፋን ነው።
     አትሞኙ፣ ኢትዮጵያን ሁሌም በግጭት ተናጭ የሚያደርጋት እኔ ከሞት ሰርዶ አይብቀል የሚሉ ወይም እኔ ከሞትኩ ዳቦ መጋገር ይቁም ባይ ፓለቲከኞች  መብዛታቸው ነው።እንወክለዋለን የሚሉትን ህዝብ ሳያማክሩ እና ይሁንታን ሳያገኙ  እኔ ሥልጣን ካልያዝኩ ለጎሣውና ቋንቋው የወገንኩለት ህዝብ አያልፍለትም ።እሱም ያለ እኔ እኔም ያለሱ ከንቱ ነን። በማለት እጅግ ግብዝነት በሞላው ፖለቲካዊ አሥተሳሰብ የመጨረሻውን  የሥልጣን  ወንበር ለማግኘት የፖለቲካ ትግል ውሥጥ በመግባታቸው ነው። (  በማንኛውም ሀገር የከፍታውን ወንበር አንድ ሰው ቢቀመጥበትም፣ወንበሩ በተለይም በአብዛኛው አፍሪካ ሀገር  ሁሌም እንደንጉሥ ወንበር ሥለሚታይ  የግጭት ሰበብ መሆኑ  ያሥገርማል።)
    የሀገር ልጅን ሤራ በጣጥሰው በከፍታው ወንበር ላይ ዱቅ ለማለት የቻሉ፣ በእጅ አዙር በቅንነት እና ከጥቅም አንፃር የሚረዷቸው የአውሮፓ፣የኢሲያ እና የአሜሪካ ባለሀብቶች ያሥፈልጓቸዋል።እናም ወደ አንዱ ቢያዘነብሉ አያሥገርምም።በዚህ አሥገዳጅ የዓለም ሥርአት ውስጥ  ንዋይ በዝቶበት ጭንቅላቱ በእብሪት የተወጠረ   የአፍሪካ ሰው ራሱ ሸቀጥ የሚመሥለው ከበርቴ ሊገጥማቸው እንደሚችል ቀድመው ባለመገንዘብ በአልጠግብ ባዩ ከበርቴ ሰበብ ሀገራቸውን ከድህነት ማውጣት ያልቻሉ የአፍሪካ  ሀገሮችም  ጥቂት እንደማይባሉ ይታወቃል።
   አንድ አንድ  የበለፀጉ ሀገራት  ከበርቴዎች  ፣ አፍሪካዊያንን ሁሌም ተበዝባዥ ለማድረግ ሲሉ  የወረደ እንሥሣዊ አቋም በአፍሪካ ህዝቦች ላይ ትላንትም ዛሬም እያንፀባረቁ ቢሥቱዋሉም ቅሉ፣ ለኢትዮጵያ ጠ/ሚ  አብይ አህመድ በኖቤል ሽልማቱ ወቅት   ሥልጡኑ የአውሮፓ ህዝብ እና መንግሥት  የሰጠውን ልባዊ ክብር እና አድናቆት ሥናሥተውል ፣በደምሳሳው አውሮፖዊ፣ኢሲያዊ፣አሜሪካዊ ሁሉ  አእምሮ ቢሥ እንዳልሆነ በድፍረት   ለመመሥከር እንችላለን።
  ዛሬ እነማን ናቸው የጠቅላይ ሚኒሥቴሩን የሠላም ተጋዳይነት አናምንም እያሉ ያሉት? በነገራችን ላይ እዚሁ እኛ ከተማ (ናዝሬት) በ1990ዎቹ ውሥጥ ባርች የሚባል አንድ ልማደኛ ሰካራም ነበር።መንገድ ላይ ያሥቆምህና ካልመታሁ ይልሃል። በንዴት ዞር በል  ብለህ ሥትገፈትረው ይወድቃል።ከወደቀበትም ሆኖ ፣ “አንተ እኔን ገፍትረህ ጣልከኝ? እኔ አላምንም? ! “ይልሃል መሬት ተዘርሮ ”  መሬት ላይ ወድቆ” እኔ አላምንም ?!” ምን ዓይነት ድርቅና ነው?
   በነገራችን ላይ ማንም አመነ አላመነ   ሁሉም እንቁላል በአንድ ቅርጫት ውሥጥ  እንዳለ ከጠ/ሚ በላይ  የሚያውቅ የለም። … “ከውጪም ከውስጥም  ያለህ ተቃዋሚ ግባ”  ተብለህ  እንሆ ሁልህም በሀገርህ ላይ ነህ።..በነፃነትም እየኖርክ ነው።ነፃነትህ ቀጣይ እንዲሁን ለህግ ተገዢ መሆን እንዳለብህ አትዘንጋ። … እንግዲህ ጨው ለራስህ ሥትል ጣፍጥ ነውና ወይ ከፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ጋር አልያም ከኢትዮጵያ ጋር ወግን፣ እውነተኛ ጨው አልያም ዲንጋይ መሆን ነው ምርጫህ።…ከፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ጋር መወገን ከቶም አያዋጣኽም።የአንተና የመሰሎችህን  የሴራ ፖለቲከኞችን  የእንቁላል ቅርጫት የያዘው አብይ መሆኑን አትርሳ።
ተጨማሪ ያንብቡ:  ወጣት ሆይ! እደግ! ተመንደግ! - በላይነህ አባተ

1 Comment

  1. Hilawi (aka dwg), what a masterful piece. God bless you man! You finally diagnosed our beloved country’s chronic disease.

Comments are closed.

Share