የተጣበቁት መንትዮች እና አስጨናቂው የ6 ሰዓታት ቀዶ ሕክምና – በመላኩ ብርሃኑ (ከአዲስ ጉዳይ መጽሔት)

/

ልዩ ዘገባ

በመላኩ ብርሃኑ
ይህ ታሪክ ተጣብቀው የተወለዱት የኢትዮጵያዊያኑ መንትዮች ማሪያ እና ሮዛ ታሪክ ነው። እነሱን ለማለያየት እስካሁን ባለው መረጃ በሀገራችን የሕክምና ታሪክ በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነው ቀዶ ሕክምና ተካሂዷል። ተሳክቶ ይሆን?… አዲስጉዳይ መጽሔት ሂደቱን ተከታትሎ ታሪኩን እንዲህ ዘግቦታል።

ሰኞ ጳጉሜን 4 ቀን 2005 ዓ.ም
ማታ

ዶክተር ፍሬሁን አየለ ወደ ቤቱ የደረሰው እንደወትሮው ቀለል ካለ ስሜት ጋር አልነበረም፡፡ የዛሬዋ ሰኞ ካለፉት አምስት ቀናት በተለየ አካሉንም አዕምሮውንም በሥራ ብዛት ውጥረት ውስጥ ከትታው ያለፈች ቀን ናት፡፡ ይህች ቀን ለዚህ የ36 ዓመት ወጣት የህፃናት ቀዶ ህክምና ባለሙያ በሥራ ዘመኑ ከባድ የሚለውን ውሳኔ ያሳለፈባት ዕለት ናት፡፡ ከ10 ዓመት በፊት ከጥቁር አንበሳ ህክምና ኮሌጅ ተመርቆ ከወጣ በኋላ በነበሩት የሀገር ውስጥም ይሁን የውጭ ሀገራት የሥራና የሥልጠና ዓመታት የዛሬውን ዓይነት የርሱን ውሳኔ የሚፈልግ ከባድ የሕክምና ጉዳይ ገጥሞት አያውቅም፡፡ በኢትዮጵያ የሕክምና ታሪክ ውስጥም ምናልባትም የመጀመሪያው የሆነው ተጣብቀው የተወለዱ ሁለት ህፃናትን በቀዶ ህክምና የማለያየት ኃላፊነት በዶክተር ፍሬሁን እጅ ላይ ወድቋል፡፡ የኮሪያ ሆስፒታል ከወሊሶ ቅዱስ ሉቃስ ሆስፒታል የተላኩለትን ተጣብቀው የተወለዱ መንትያ ህፃናት (Conjoined twins) በሆስፒታሉ ወደ ሚገኘውና ዶክተር ፍሬሁን ወደሚመራው “ቤታኒ ኪድስ” የተባለ ግብረ ሰናይ የህፃናት ቀዶ ሕክምና መስጫ ማዕከል ያስተላለፈው ሙሉ ኃላፊነቱን ለዚህ ወጣት ዶክተር ሰጥቶ ነው፡፡ እናም የነዚህን ሕፃናት ሕይወት ማትረፍ ከፈጣሪያቸው ቀጥሎ በዚህ ዶክተርና በባልደረቦቹ እጅ ላይ ወድቋል፡፡
ለወትሮው ብዙም የማያስጨንቀው የህክምና ሥራው ዛሬ ግን ከእንቅልፉ እስኪቀስቅሰው የመንትዮቹ ማሪያ እና ሮዛ ጉዳይ አዕምሮውን ወጥሮ ይዞታል፡፡ ያም ሆኖ ስለዚህ ከባድ ጭንቀት ለባለቤቱ የውብዳር ሳሙኤልም ሆነ ለሁለት ህፃናት ልጆቹ ኒስ እና ሳቤላ ትንፍሽ አላለም፡፡ “ይህ ክስተት የተፈጠረው ባለቤቴ በወለደቻቸው የእኔ ልጆች ላይ ቢሆን ምን አደርግ ነበር? ያለኝ አማራጭ በቀዶ ሕክምና ሕይወታቸውን ለማትረፍ መወሠን ብቻ ነው፡፡ ስለዚህም ደፍሬ ወስኛለሁ” ይላል፡፡ እንዴት እርሱም ሆነ በኢትዮጵያ ውስጥ አንድም ሐኪም ሞክሮት የማያውቀውን ይህን ቀዶ ጥገና ለመሥራት ኃላፊነቱን እንደወሰደ ሲናገር።
የዚያን ዕለት ሌሊት እነዚህ መንትዮች ከተወለዱበትና ወደ ኮሪያ ሆስፒታል ከመጡበት ረቡዕ መስከረም 29 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ እስከዛሬዋ ሰኞ ምሽት ድረስ የነበሩትን ውጣ ውረዶች ወደ ኋላ ተመልሶ ማሰብ ጀመረ፡፡

ረቡዕ ነሐሴ 15 ቀን 2005 ዓ.ም
ወሊሶ

ከአ/አ በ138 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በምትገኘው ወሊሶ ከተማ የተገነባው የቅዱስ ሉቃስ የካቶሊክ ሆስፒታል አስካሁን ባደረገው የማዋለድ ታሪክ ውስጥ የዛሬው ዕለት የተለየ ገጠመኝ ያስተናገደበት ሆነ፡፡ አንዲት የገጠር ሴት በሰዎች እርዳታ ወደ ሆስፒታል ስትደርስ በምጥ እየተሰቃየች ነበር፡፡ ከዚህ ቀደም ቅድመ ወሊድ ክትትል አላደረገችም፡፡ ቀኗ ደርሶ ምጧ ሲመጣም በቤት ውስጥ በባህላዊ ዘዴ እንድትወልድ ጥረት ሲደረግ ቆየ፡፡ አልተቻለም፡፡ የእናትየው ስቃይ ሲከፋና ልጆቹን ከማህፀኗ ማውጣት ሲያስቸግር ጊዜ ሰዎቹ ወደዚህ ሆስፒታል አመጧት፡፡ ሐኪሞች እናትየው ያለችበትን ስቃይና የሁኔታውን አስቸኳይነት ተመልክተው ወዲያውኑ በቀዶ ሕክምና (C-section) እንድትገላገል ወደ ኦፕራሲዮን ክፍል ይዘዋት ተጣደፉ፡፡ ከማህፀኗም ልውጣ እያለ ሲያስጨንቃት የነበረው ፅንስ ወጣ። ለአዋላጆቹ ባለሙያዎች አስደንጋጭ ክስተት ነበር። እናትየው ላለፉት ዘጠኝ ወራት በማህፀኗ ተሸክማቸው የቆየችው ሕጻናት መንትዮች ናቸው፡፡ ከደረታቸው እስከ እምብርታቸው የታችኛው ክፍል ድረስ ፊት ለፊት የተጣበቁ መንትያ ሴት ህፃናት። ህፃናቱ በሕይወት አሉ፡፡ ይተነፍሳሉ፣ ይንቀሳቀሳሉ፣ ያለቅሳሉ። አፈጣጠራቸው ግን እጅግ አስደንጋጭና ለተመልካችም መቋቋም የማይቻል ሐዘን የሚፈጥር ዓይነት ነው፡፡ ባለሙያዎቹ ሕፃናቱን ወደ ሙቀት ክፍል ወስደው እናትየውን ተገቢ ሕክምና ሰጥተው አስተኟት፡፡ ይህች ሴት በሆስፒታሉ የቆየችው ግን የቀዶ ሕክምና ስፌት ቁስል እስኪጠግላት ድረስ ብቻ ነበር፡፡ አንድ ማለዳ ማንም ሳያያት፣ የሄደበችበትንም ሳትናገር ሕፃናቱን ጥላ ጠፋች፡፡ አንዳንድ ነርሶች እንደሚሉት ህፃናቱን “የፈለገ ይውሰዳቸው” ስትል ተሰምታለች። የተፈጠረውን ነገር ከእግዜር ቁጣና ካለመታደል ጋር አያይዛዋለች፡፡ ሆስፒታሉ ትሄድበታለች ብሎ ያሰበውን ሥፍራ ሁሉ ጠይቆ አፈላለጋት። አልተገኘችም፡፡
ማዘር ትሬዛ ድርጅት ልጆቹን በወላጅ ምትክ የማሳደግ ኃላፊነቱን ተረከበ፡፡ ስምም አወጣላቸው። የአባታቸውን መጠሪያም የድርጅቱ ስም ወሰደ። አንደኛዋን ማሪያ ትሬዛ ሲላት ሌላዋን ደግሞ ሮዛ ትሬዛ ብሎ ሰየማት፡፡ ብዙውን ጊዜ ተጣብቀው የተወለዱ ህጻናት የመኖር ተስፋቸው ዝቅተኛ መሆኑ ይነገራል። ቀያዮቹና የሚያምሩት ኢትዮጵያውያኑ ማሪያ እና ሮዛ በዚህች ምድር ላይ የመቆየታቸው ዕጣ የሚወሰነው ከፈጠራቸው አምላክ በታች በሐኪሞች እጅ ላይ ሆኗል፡፡
ሳይንስ እንደሚለው ጽንስ መንታ የሚሆነው ከተፀነሰ በኋላ በ7ኛው ቀን ለሁለት ሲከፈል ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ሁለት ተመሳሳይ ፆታ ያላቸው ህፃናት ይፈጠራሉ፡፡ ይህ የመከፈል ሂደት ግን ከ13-16 ቀን ዘግይቶ ሲካሄድ የመክፈል ሂደቱ ሙሉ ለሙሉ ስለማይጠናቀቅ ሕፃናቱ በጎን፣ በፊት ለፊት፣ አለያም በሆነ የሰውነት አካላቸው ተጣብቀው ይወለዳሉ፡፡ በተለይ በሆድ እቃቸውና በጭንቅላታቸው የተጣበቁ ከሆኑና የውስጥ አካል ክፍሎቻቸውን የሚጋሩ ከሆነ ደግሞ ወደፊት በሕይወት የመኖራቸው ዕድል አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይወድቃል። ከአንድ ሺህ ፅንስ አንዱ መንታ የመሆን አጋጣሚ ሲኖረው ተጣብቆ የመወለድ አጋጣሚ ግን ከ1 ሚሊዮን ፅንሰ ከሦስትና አራት አይበልጥም፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ይህን መሰል ወሊድ በ4 ወይም በ5 ዓመት አንዴ የሚከሰት ቢሆንም ጉዳዩ ወደ ሕክምና ለመድረስ ከመቻሉ በፊት የህፃናቱ ሕይወት ያልፋል፡፡
በተከታዮቹ ቀናት ሆስፒታሉ ይህን ክስተት አልፈው እስካሁን በሕይወት የቆዩትን ማሪያ እና ሮዛ በሕክምና ጥበብ እንዲለያዩ ለማድረግ ለውጭ ሀገራት ሆስፒታሎች ጥያቄ ማቅረብ ጀመረ። ጎን ለጎንም ህፃናቱ ጤናቸው ተጠብቆ እንዲቆዩ ጥብቅ እንክብካቤ በማድረግ ለሁለት ሳምንት ያህል በጥሩ ሁኔታ አኖራቸው። የማሪያና የሮዛን ሕይወት ለማትረፍ በቀጣይ ማድረግ ስለሚቻለው ነገር እየታሰበ ባለበት ወቅት ነበር የሚያስፈነጥዝ አጋጣሚ የተፈጠረው፡፡ አሜሪካ ውስጥ የሚገኘውንና ታዋቂውን የጆን ሆፕኪንስ ዩኒቨርስቲ ሕክምና ተቋም ጨምሮ ሦስት ታዋቂ ሆስፒታሎች በነጻ መንትዮቹን ህፃናት ለመለያየት የሚያስችል ቀዶ ሕክምና ለማድረግ ፈቃደኛ መሆናቸውን ገለፁ፡፡ ሳዑዲ አረቢያ የሚገኘው ግዙፍ ሆስፒታልም በተመሳሳይ “ፈቃደኛ ነኝ” አለ፡፡ ይህ ደስታ ግን አልዘለቀም። የሕፃናቱን ጉዳይ የሚከታተለው ቅዱስ ሉቃስ ሆስፒታልም ሆነ ማዘር ትሬዛ ድርጅት ከዚህ ደስታ ሳይወጡ ተስፋቸውን የሚያጨልም ሌላ ነገር መጣ፡፡ የህፃናቱ የመጓጓዣ ወጪ። እነዚህ መንትዮች ወደ አሜሪካ ይሂዱ ከተባለ በተደራጀ የጥብቅ ክትትል ክፍል (ICU)፣ ለዚሁ ተብሎ በተዘጋጁ መሣሪያዎችና የህክምና ቡድን የተሟላ አምቡላንስ አውሮፕላን ያስፈልጋቸዋል። ይህ “በራሪ ሆስፒታል” ዋጋው አይቀመስም። ከ2 እና 3 መቶ ሺህ ዶላር በላይ ይጠይቃል፡፡ የህክምና ወጪውን ሸፍነን በነፃ ቀዶ ህክምናውን እንሰራለን ያሉት ሆስፒታሎችም ሆኑ ቅዱስ ሉቃስና ማዘር ትሬዛ ድርጅት ይህን ወጪ ሊሸፍኑ አይችሉም። አማራጭ ጠፋ፡፡ በዚህ መሃል ደግሞ ሮዛ በሳምባ ምች (Nemonia) በሽታ ተያዘች፡፡
ይህ በሽታ አደገኛ ደረጃ ከመድረሱ በፊት ለማከም ዘመናዊ መሣሪያዎች ያሉትና ለህፃናቱ ቀጣይ ምርመራም የተሻለው ሚዩንግሳንግ ክርስቲያን ሜዲካል ሴንተር ወይም በተለምዶ መጠሪያው ኮሪያ ሆስፒታል ነው። ረቡዕ ነሐሴ 29 ቀን 2005 ዓ.ም ማሪያና ሮዛ ከቅዱስ ሉቃስ ወደኮሪያ ወደዚሁ ማዕከል ተዛወሩ። ለሮዛ የሣንባ ምች ሕክምና እየተደረገላት ጎን ለጎን የልብ ምርመራ (ECG) እና የሳምባና ሆድዕቃ ምርመራ ተካሄደ። የመጓጓዣ ወጪውን ለመሸፈን የሚደረገውም ጥረት አልተቋረጠም። ኢትዮጵያ ውስጥ በሚደረግ ሕክምና የሕፃናቱን ሕይወት ማትረፍ ይቻላል ብሎ ያሠበ ማንም የለም፡፡
በሕክምናው ዓለም ባለው ልምድ ተጣብቀው የተወለዱ ህፃናት በቀዶ ጥገና ለመነጣጠል ብቁ ናቸው የሚባሉት ከ3-6 ወር ሲሞላቸው ነው፡፡ እነማሪያ እስከዚያ በሕይወት ከቆዩ የመጓጓዣ ወጪ ችሎ የሚወስዳቸው አካል ያገኙ ይሆናል፡፡ የኮሪያ ሆስፒታል ኃላፊነት ለጊዜው ህጻናቱ በሕይወት እንዲቆዩ የሚያስችላቸውን ሕክምና እየሰጠ ዕድገታቸውን መጠበቅ ብቻ ነው።
ከቀን ቀን ተስፋ ከሚሠጥ ነገር ይልቅ ውስብስብና ከባድ ችግሮች እየተፈጠሩ ነው፡፡ ሮዛን የሣምባ ምቹ እየጎዳት መጣ፡፡ ከዚህ በከፋ ሁኔታ ደግሞ የደም ዝውውር ሥርዓቷ የተዛባ ሆኖ ተገኘ። በትክክለኛው አፈጣጠር የሮዛ ልብ የቆሸሸውን ኦክሲጂን አልባ ደም በደም ቅዳ (Pulmonary Arthery) አማካኝነት ወደሳምባ ወስዶ ካጣራ በኋላ የተጣራውን ባለኦክስጂን ደም ደግሞ በደም መልስ (Pulminany Vien) አማካኝነት ወደ ልብ መልሶ በዋናው የደም ስር (Aorta) አማካኝነት ወደሰውነት ማሰራጨት ይገባው ነበር። ከዚህ ይልቅ ግን የሮዛ ልብ ደሙን ወደሳምባ ወስዶ ካጣራና ከመለሰ በኋላ ወደሰውነት ከማሰራጨት ይልቅ እንደገና ወደሳምባ ይልከዋል። በዚህ ሳቢያ ሰውነቷ ደም አያገኝም፡፡ ምርመራው ሁለቱ መንትዮች ደም እንደሚጋሩ ያሳያል። ቦታው ግን በየት በኩል እንደሆነ መለየት አልተቻለም።
ይህንን ተዛብቶ የተፈጠረ የደም ማስተላለፍ ሥርዓት ለማስተካከለ ከባድ ቀዶ ሕክምና መደረግ አለበት። ይህ ደግሞ በትንሹ 2 ሳምንት ይፈልጋል፡፡ ይህ ሂደት በኢትዮጵያም ይሁን በየትኛውም ዓለም ቢካሄድ የሮዛ የመኖር ዕድል የመነመነ ነው፡፡ እነዚህን መንትዮች ወደውጭ መላክ ፋይዳ የለውም፡፡ ስለዚህም የሕክምና ቡድን አዋቅሮ በጉዳዩ ላይ ጥልቅ ምርመራ በማድረግ መሆን የሚችለውን ነገር መወሰን የመጨረሻ አማራጭ ሆነ፡፡
በዶክተር ፍሬሁን የሚመራ አራት ከፍተኛ ሐኪሞች ያሉት አንድ ቡድን ተዋቀረ፡፡ የሆስፒታሉ ጠቅላላ ቀዶ ሕክምና ሐኪም ዶክተር ሰለሞን፣ በኢትዮጵያ ብቸኛው የደም ስር ቀዶ ህክምና ባለሙያ አሜሪካዊው ዶክተር ቻንግ፣ የጥቁር አንበሳ የልብና ደረት ቀዶ ህክምና ስፔሻሊስት ዶክተር አበበ እንዲሁም የኮሪያ ሆስፒታል ጠቅላላ ቀዶ ሕክምና ባለሙያ ዶክተር ጆን በጋራ እንደ አንድ ቡድን ተደራጁ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የሆስፒታሉ የህክምና ስነ ምግባር ኮሚቴና ማዘር ትሬዛ በቡድኑ ውስጥ አሉ፡፡ ሕፃናቱ በግልና በጋራ ያላቸው የውስጥ ብልት ምን እንደሆነ፣ የት ጋ እንደተጣበቁና ሌሎችም ውስብስብ ጉዳዮችን ለማወቅ ምርመራ ተጀመረ። የምርመራው ውጤት ደግሞ አስደንጋጭ ነበር።
የማሪያና ሮዛ ሁለት ልቦች ተጣብቀዋል፡፡ አንጀታቸው ተጣብቋል፣ ጉበታቸው ተጣብቋል፣ ሳንባቸው ተጣብቋል፣ ቆሽታቸው ተጣብቋል፣ ሌሎች ጥቃቅን የሰውነት ብልቶቻቸውም ተጣብቀው ነው የተፈጠሩት። ሐኪሞቹ ፈተና ውስጥ ገቡ። በመሳሪያ በተደረገው ምርመራ የታወቀው ይህ ብቻ ይሁን እንጂ ሌሎች ያልታወቁና ለመመርመር አስቸጋሪ የሆኑ ውስብስብ የውስጥ ችግሮችም አሉ፡፡
ሮዛ በመተንፈሻ መሳሪያ እየተረዳች፣ ከያዛት የሳምባ ምች ጋር እየታገለችና የተዛባው የልብ የደም ስርጭት ሥርዓቷ ጫና እያሣደረባት ከሰዓታት ሰዓታት ጤንነቷ ወደ አስጊ ደረጃ እያዘገመ ነው። ሐኪሞቹ ለዚህች ልጅ ጤንነት ይበጃል ያሉትን ሁሉ ጥረት እያደረጉ ነው፡፡ አሁን ውሳኔያቸው የሚፈለግበት ሰዓት ተቃርቧል፡፡
ህፃናቱ እዚህ ሆስፒታል ከገቡ 5 ቀናት ሆኗቸዋል፡፡ የ2005 ዘመን ሊጠናቀቅ የቀሩት ቀናት ሁለት ብቻ ናቸው፡፡ የነዚህ ህፃናት ይህን ዘመን የመሻገር ተስፋም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተመናመነ ነው፡፡ እያንዳንዷ ሰዓት አስጨናቂ ሆናለች፡፡ በኢትዮጵያ የሕክምና ታሪክ ውስጥ አንድ ትልቅ ፈተና ተጋርጧል፡፡ ይህን ፈተና በድል ለመወጣት “ይቻላል” ከሚለው ይልቅ “አይቻልም” የሚለው ሃሳብ ሚዛን እየደፋ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሻለቃ ዳዊት ስለ ትግሉ እና ሽግግሩ ጊዜ ተናገሩ | Hiber Radio with

ሰኞ ጳጉሜን 4 ቀን 2005 ዓ.ም
ማለዳ

የሕክምና ቡድኑ ተደናግጧል፡፡ እነዚህ መንትዮች ቢያንስ ለ3 ወራት በጤንነት ሊቆዩ ቢችሉ ጠንከር ስለሚሉ ኦፕሬሽን ለማድረግ መሞከር የሩቅ ጊዜ ዕቅዱ ነበር፡፡ ነገር ግን የቆንጅዬዋ ሮዛ ጉዳይ የሐኪሞቹን ተስፋ አመንምኖታል፡፡ ግራ በመጋባትና ምን እናድርግ በሚል ስሜት መካከል ተወጥረዋል፡፡ ሰኞ ከሁሉ ቀናት የከበደው ሆነ፡፡ ሮዛ ወደሞት አቅጣጫ እያመራች ነው፡፡ በልቧና በሳምባዋ ላይ ያለው ጉዳት የዚህችን ጨቅላ ሕይወት ሊነጥቅ ግብግብ ገጥሟል። አስጨናቂው ነገር ሮዛ ከሞተች ሁለቱን ሕፃናት በቀዶ ሕክምና በማለያየት ቢያንስ ማሪያን ለማትረፍ የሚደረግ ጥረት አይኖርም፡፡ ምክንያቱም ሮዛ በሞተች በሰዓታት ውስጥ ማሪያ ልትሞት ትችላለች፡፡ በዚህ መካከል ቀዶ ሕክምናውን እናድርግ ቢባል እንኳን አንድ ሕይወት ያላትንና አንድ ሕይወቷ ያለፈን ሕፃን የኦፕራሲዮን ጠረጴዛ ላይ አስተኝቶ ለማለያየት የሚደረገው ቀዶ ሕክምና ራሱ ሮዛን ሊገድላት ስለሚችል ዋጋ አይኖረውም፡፡ ለውሳኔ አስጨናቂ ነገር ተፈጠረ፡፡ ጉዳዩ ወጣቱ ዶክተር ፍሬሁን ላይ ወደቀ። ያለው ምርጫ ሕጻናቱን በቀዶ ሕክምና ለመለያየት አፋጣኝ ውሳኔ ማሳለፍ ወይም “አልችልም” ብሎ ሁለቱም ሲሞቱ መመልከት። ከውሳኔው በፊት ቡድኑ ተሰብስቦ ውይይት ተጀመረ፡፡
ፈረንጆቹ ሐኪሞችና ሌሎችም “ይህን ቀዶ ህክምና ማድረግ ጊዜ ማባከን ነውና ቢቀር ይሻላል” ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያውያን ሐኪሞች ብቃት የተማመነ የውጪ ሀገር ዶክተር የለም፡፡ ‘ከነዚህ ልጆች የሁለቱንም ወይም የአንዷን ሕይወት ማትረፍ የሚቻለው ከኢትዮጵያ ውጪ በሚደረግ ቀዶ ሕክምና ብቻ ነው’ የሚል ድምዳሜ ብቻ ነው የሰፈነው፡፡ የቡድኑ አባላትም ቢሆኑ ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ ውስጥ ተጣብቀው የተወለዱ (Conjoined Twins) ሣይሆን ተቀጥላ አካል ይዘው የተወለዱ (Parasitic Twin) በቀዶ ሕክምና የመለያየት ሥራ መሠራቱን ያውቃሉ፡፡ ይህ ሕክምና የተካሄደው የተጣበቀ እግር፣ ወይም እጅ ወይም ሌላ ግማሽ አካል ይዘው በተወለዱት ላይ እንጂ የተሟላ አካል ይዘው የተፈጠሩ ሕጻናት ላይ አልነበረም። ስለዚህ በሙያው ልምድ ያለው ሐኪም የለም፡፡ ብቸኛው አማራጭ መሞከር ብቻ ነው፡፡
ዶ/ር ፍሬሁን ከመወሰኑ በፊት ከዶክተር ቻግ እና ከዶክተር ሰለሞን ጋር መከረ፡፡ ለውሳኔው የሚረዳውን ሃሳብ አቀረቡለት። የሕፃናት የልብ ስፔሻሊስት የሆነው ዶክተር እንዳለ የሮዛንና የማሪያን የተጣበቀ ልብ በመሳሪያ ካየ በኋላ “ልቦቹ ከላይ ያለው ሽፋናቸው እንጂ ሙሉ በሙሉ የተጣበቁ (Fused) ስላልሆኑ መለያየት ይቻላል” የሚል ማረጋገጫ መስጠቱ ለዶክተር ፍሬሁን ውሳኔ መሠረት ሆኗል፡፡ የልብ ጉዳይ ወሳኝ ነው፡፡ ልቦቹ ሙሉ በሙሉ ተጣብቀው ከሆነ የትም ዓለም ቢሄዱ በሕክምና መትረፍ አይችሉም ነበር፡፡ በቃ! ነገ ማክሰኞ ጷጉሜን 5 ቀን 2005 ማለዳ ቀዶ ሕክምናው ይካሄዳል፡፡ የማይቻል ነው የተባለውን ለማስቻል ተወሰነ፡፡
ቀዶ ሕክምናው በዶ/ር ፍሬሁን መሪነት ከዶ/ር ቻንግ እና ከዶ/ር ሰለሞን ጋር ሊያካሂዱት፣ የሠመመን (Anesthesia) ጉዳይን ስፔሻሊስቱ ዶ/ር ክንፉ ሊከታተሉት፣ ሌሎች አራት ነርሶችና ሐኪሞች በሥራው ላይ ሊሳተፉ፣ ይህ ቡድን ችግር ካጋጠመው ደግሞ በተጠባባቂነት ሁለት የቀዶ ሕክምና ባለሙያዎችና አራት ነርሶች ከምንም ሥራ ነጻ ሆነው እንዲጠባበቁ ሊደረግ ተስማሙ። ሁሉም የቡድኑ አባላት ለነገው ወሳኝ ሥራ ዝግጅት ለማድረግ ተበታተኑ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  በሙስና የተጠረጠሩት የደብረ ጽጌ ቅ/ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን ዋና ጸሐፊ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ዋሉ

* * * * *
ዶ/ር ፍሬሁን ይህን ሐሳብ ይዞ ነው ቤቱ የገባው፡፡ ይህን አስጨናቂ ውሳኔ ይዞ ነው ሌሊቱን ያነጋው፡፡ ቤተሰቡን ተሰናብቶ ሲወጣ ዛሬ ስለሚጠብቀው ፈተና አልተናገረም፡፡ ሆስፒታል የደረሰው በማለዳ ነበር፡፡ ነርሶችና የሕክምና ቡድኑ አባላት በሰፊው ክፍል ውስጥ ተሰባስበዋል። በሆስፒታሉ የሃይማኖት አገልጋዮች ጸሎት ተደርጓል። የሰመመን ስፔሻሊስቱ ዶክተር ክንፉ ወደዶክተር ፍሬሁን መጥቶ የመጨረሻ ውሳኔውን ጠየቀው። “ዶክተር ፍሬሁን! ይቻላል?” አለው። ዶክተር ፍሬሁን መለሰ “ይቻላል!”። ዶክተር ክንፉ ህጻናቱ እንዲመጡ አዘዘ። ማሪያ እና ሮዛን የያዘው ትንሽ አልጋ እየተገፋ ወደ ቀዶ ሕክምና ማድረጊያ ክፍል (Operation Theater) ሲገባ ከማለዳው 2፡30 ሆኗል። ለህጻናቱ ሰመመን ለመስጠት የተደረገው ሥራ 1 ሰዓት ከ30 ደቂቃ ፈጀ። አሁን ለታሪካዊው ቀዶ ሕክምና ዝግጁ ሆነዋል። አስጨናቂው ሰዓት ደረሰ።
ሁሉም የቀዶ ሕክምና ባለሙያዎች አረንጓዴውን ጋዋን ለበሱ። መቀሶች፣ ፋሻዎች፣ መስፌያዎች፣ መድኃኒቶች፣ የመተንፈሻ መሳሪያዎች…ሁሉም ተሟልተዋል፡፡ ሕፃናቱ በኦፕሬሽን ጠረጴዛው ላይ ተኙ፡፡ አርቴፊሻል ትንፋሽ መስጫ፣ የልብ ምት መቆጣጠሪያ፣ ሌሎችም ውስብስብ መሳሪያዎች በትንንሽ አካሎቻቸው ላይ ተገጥመውላቸዋል። በአረንጓዴው ጨርቅ ተሸፍነው ቀዶ ጥገና የሚካሄድበት የተጣበቀ አካላቸው ብቻ ተገልጧል። ሦስቱ ዶክተሮች ጋዋናቸውንና ጓንታቸው አድርገው፣ አንዳች ነገር እንዳይስቱ ዐይናቸውን ተክለው ሥራቸውን ሊጀምሩ ተዘጋጁ። የመጀመሪያውን ቢለዋ ህጻናቱ አካል ላይ ከማሳረፋቸው በፊት ግን ፀሎት አደረጉ፡፡
“ጥበብንና ዕውቀትን የምትሰጥ እግዚአብሔር፣ ለእነዚህ ህፃናት ድሕንነትን አውርድ፡፡ ባንተ ትዕዛዝ ሁሉ ይሁን። ሕይወትን ለነርሱ ስጥ፡፡ በሚፈጠረው ነገር ሁሉ ለሕፃናቱም ለእናታቸውም መፅናናትንና እረፍትን አትንፈጋቸው። ፀሎታችንንም ስማ”
ከረፋዱ 4፡30 ላይ ዶክተር ፍሬሁን የመጀመሪያውን ቢላዋ በሕፃናቱ ገላ ላይ አሳረፈ። መንትዮቹ ከተጣበቁበት የደረታቸው ክፍል የተጀመረው ቀዶ ህክምና ቆዳቸውን፣ ቀጥሎም ሥጋቸውን ከዚያም የደረት አጥንቶቻቸውን እያለፈ ሳንባቸው ላይ ደርሷል። ሳንባቸውን መለያየት ከባድ ሥራ አልነበረም። ወደውስጥ ዘለቀ፡፡ ልባቸው ጋር ደርሷል፡፡ ከባዱ ሥራ እዚህ ላይ ቀለለ፡፡ ዶ/ር እንዳለ እንደተናገረው ሕፃናቱ የየራሳቸው ልብ አላቸው፡፡ ሁለቱም በአግባቡ ይመታሉ። የተያያዙት በላይኛው ሽፋናቸው ብቻ ነበርና ነርቮች እንዳይነኩ ከፍተኛ ጥንቃቄ በማድረግ ለያዩዋቸው፡፡
ከቀኑ ስድስት ሰዓት ሆኗል። የህጻናቱ የልብ ምት መቆጣጠሪያ መሳሪያው ቲክ… ቲክ… ቲክ.. የሚል ድምጹን አላቋረጠም። ትንፋሻቸው ጥሩ ነው፡፡ ቀዶ ሕክምናው ወደ ሆድ እቃ ሲዘልቅ ግን ከባድ ውሳኔ የሚፈልግ ችግር ተከሰተ። ጉበታቸው ተጣብቋል፡፡ የሮዛ ጉበት ትንሽ ሲሆን የማሪያ ትልቅ ነው። የሚሰራውም እሱ ብቻ ነው። በአንድ ጉበት ይጠቀማሉ ማለት ይቀላል፡፡ ይህን ጉበት በማለያየት አንድ ማድረግ ይቻላል፡፡ ለሁለቱም አንዳንድ ጉበት መፍጠር ግን አይቻልም፡፡ ለማን ይሁን? ፈታኝ ጥያቄ ነው፡፡ ሐኪሞቹ ይህን ከመወሰናቸው በፊት ግን በመሳሪያ ምርመራው ላይ ያልታየ ችግር ሮዛ ላይ አገኙ፡፡ የሮዛ የታችኛው የልብ ደም ስር (Inferior Vena Cava) ወጥ ሳይሆን የተቆራረጠ ሆኖ ተገኘ፡፡ ይህ ደግሞ ሮዛ ከማሪያ ከተለየች የመኖር ተስፋዋ እንዲያከትም ሊያደርጋት ይችላል፡፡ አሁን ሐኪሞቹ ሥራቸውን ቀጥለዋል፡፡ ቀዶ ሕክምናው ከተጀመረ 3ኛው ሰዓት ሲቃረብ የሮዛ የልብ ምትና አተነፋፈሷ እየቀነሰ መጣ፡፡ በሕክምናው ቋንቋ የጤናማ ሕፃን በቂ የትንፋሽ መጠን (Saturation) ከ86 በላይ መሆን አለበት፡፡ መሳሪያው የሮዛ ትንፋሽ ከ50 ቀስ በቀስ ወደ 20 እየወረደ መሆኑን አሳየ። በዚህ ቁጥር ውስጥ ለረዥም ደቂቃዎች ከቆየች አዕምሮዋ መሞት ይጀምራል፡፡ የልብ ምቷም ይቀንሳል፡፡ ሐኪሞቹ ስጋታቸው ጨመረ። ከ120-180 መሆን የነበረበት የሮዛ የልብ ምትም እያሽቆለቆለ በ30 እና በ20 ውስጥ ዋለለ፡፡ ሐኪሞቹ በመድኃኒት እርዳታ ሕይወቷ እንዲተርፍ ጥረት ማድረግ ጀመሩ። ከፊት ለፊታቸው ያለው የልብ ምት መጠን ማሳያ መሳሪያ ግራፍ በፍጥነት እያሽቆለቆለና ድምጹም እየዘገየ መጣ። አንድ ጊዜ የማያቋርጥ ድምፅ አሰምቶ ጸጥ አለ…ሮዛ ሞተች፡፡ ጸጥ ያለው ክፍል ከመቀሶችና ከመሳሪያዎች ድምጽ ውጪ በከባድ ዝምታ ተሞላ። ለሁሉም አሳዛኝ አጋጣሚ ነበር፡፡
የሕክምና ቡድኑ አሁን በአንድ ልብ ማሪያን የማትረፍ ሥራ ጀምሯል፡፡ ሮዛ ከሞተች በኋላ የማሪያ ሕይወትም ሊያልፍ ስለሚችል ቀዶ ሕክምናው በፍጥነት መካሄድ አለበት። ከሟች እህቷ መለያየት ይኖባታል፡፡ ሐኪሞቹ የማሪያ የደም ስሮች በቀዶ ጥገናው ሂደት ተቆርጠው በደም መፍሰስ እንዳትሞት ለማድረግ ፈታኝና ውስብስብ ሥራቸውን ቀጠሉ፡፡ የማሪያን አንጀት ከእህቷ ቆርጠው ከነጠሉ በኋላ ቆሽት ላይ ሲደርሱ የደም ስሮቹ ተሳስረው አገኟቸው። ከፍተኛ ጥንቃቄና ጊዜ የወሰደ ነገር ግን የተሳካ የማለያየት ሥራ ሰሩ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለ የሁለቱንም የተጣበቀ አካል በማለያየት ከቀኑ 10፡00 ሲሆን ቀዶ ሕክምናው ተጠናቀቀ። ከዚህ በኋላ ቀሪው ሥራ የተከፈተውን የማሪያን ሆድ ከእህቷ በተገኘ ቆዳ መሸፈንና የመሃሉ አካፋይ የጎደለውን የደረት አጥንቷን አጋጥሞ መስፋቱ ነበር፡፡ ከዝግጅቱ እስከ ሥራው ማጠናቀቂያ በጠቅላላው 9 ሰዓት የፈጀው ቀዶ ሕክምና ተጠናቆ ማሪያ ወደ ጥብቅ ክትትል ዩኒት ተላከች፡፡ ቆንጅዬዋ ሮዛ ደግሞ በክብር ተሸኘች፡፡
ማሪያ በተፈጠረች በ25ኛ ቀኗ ዋና ዋና የተባሉና ከአጥንት እስከ ልብ የዘለቁ ቀዶ ሕክምናዎችን ለማድረግ ተገደደች፡፡ እንኳን ይህቺ ጨቅላ ማንም አዋቂ ከሚችለው በላይ ከባድ ጫና ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ያለው ሥራ ለሚቀጥሉት 48 ሠዓታት ይህች ሕፃን ሕይወቷ እንዳያልፍ ያልተቋረጠ የሕክምና ክትትል ማድረግ ነው፡፡ የዚህን ኃላፊነት የህጻናት ሕክምና ስፔሻሊስቶቹ ዶ/ር ኪም እና ዶ/ር አስቴር ተቀበሉ፡፡ የቀዶ ሕክምና ቡድኑ ፀሎቱ ሰምሯል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሕወሓት መንግስት 5 የደህነንት አባሎቹን ወህኒ ወረወረ * ይህ በስርዓቱ ውስጥ ያለውን መፍረክረክና አለመተማመን ገሃድ ያጋልጣል

ሐሙስ መስከረም 2 ቀን 2006 ዓ.ም
ማሪያ አዲሱን ዓመት አይታለች፡፡ በ48ኛው ሰዓት ሐሙስ ምሳ ሰዓት አካበቢ ያለማሽን እርዳታ መተንፈስ ቻለች፡፡ ሳንባዋንና ልቧ ሥራቸውን ቀጠሉ፡፡ ይህን ዐይነት ቀዶ ሕክምና የተሰራላቸው ሰዎች በተለይ ሕፃናት በአርቴፊሻል መተንፈሻ ከ3-5 ቀን መቆየታቸው የሚጠበቅ ቢሆንም ጨቅላዋ ማሪያ ግን ሞትን ድል ያደረገችበትን ምልክት ገና በሁለተኛ ቀኗ አሳየች፡፡ አርብ ዕለት ደግሞ አንጀቷ በጥሩ ሁኔታ ሥራውን መሥራት እንደሚችል በመረጋገጡ የሚሰጣትን ምግብ መውሰድ እንደምትችል ታመነ፡፡ ይህ ፈጣን ለውጥ የወጣቱን ዶክተርና የሌሎችንም የቀዶ ሕክምና ባለሙያዎች ልፋት ዋጋ እንዳለው ያሳየ ነበር፡፡ ማሪያን ይህንን ቀን ካለፈች በርግጠኝነት ታድጋለች፡፡ ምናልባትም ይህን ከሚሊዮን የአንድና ሁለት ሰው ብቻ የሆነ ታሪክ ለሁሉም ሰው ታወራ ይሆናል፡፡

ቅዳሜ መስከረም 4 ቀን 2006 ዓ.ም

ማለዳ
ወጣቱ ዶ/ር ፍሬሁን ፊቱ በደስታ በርቷል፡፡ እርሱና የሕክምና ቡድኑ አባላት በኢትዮጵያ የሕክምና ታሪክ የመጀመሪያ የሆነውንና አይቻልም የተባለው ፈተና አልፈው ለውጤት በመብቃታቸው እርካታ ተሰምቶታል፡፡ ለአዲስጉዳይ መጽሔት አስተየየቱን ሲሰጥም ይህንኑ ነበር የተናገረው።
“ወጣት ነኝ፡፡ ከዚህ ቀደም ከባድ የተባሉ የቀዶ ሕክምና ሥራዎች ላይ ብሳተፍም እንዲህ ዓይነት ኃላፊነትን የሚጠይቅ ስራ ያጋጥመኛል ብዬ አስቤ አላውቅም፡፡ ውጪ ሀገር ሳለሁ ያየኋቸው ከባድ የተባሉ ቀዶ ሕክምናዎች ኢትዮጵያ ውስጥ መቼ ሊካሄዱ እንደ እንደሚችሉ በማሰብ ያንን ቀን እናፍቅ ነበር፡፡ “ኢትዮጵያውያን አይችሉም” የሚለውን አስተሳሰብ ለመታገልም አንድ አጋጣሚ ይመጣል ብዬ አስብ ነበር፡፡ እነዚህ መንትዮች ወደ አሜሪካ ይሂዱ ሲባል ለነርሱ ደስ ቢለኝም እኛ ባለመቻላችን ወይም ይችላሉ ተብሎ ባለመታሰቡ ግን ቅር ብሎኝ ነበር፡፡ የአጋጣሚ ነገር ሆኖ በኢትዮጵያ ሕክምና ታሪክ የመጀመሪያ ነው ብዬ የማስበውን ቀዶ ሕክምና ኢትዮጵያውያን በጋራ ሰርተነዋል፡፡ ሁላችም ኮርተናል፡፡ ውጤቱ የሁላችንም ነው፡፡ ምንም ነገር ማድረግ እንደምንችል ለሌሎች ማስመስከር ችለናል፡፡ የማሪያን እናት ተገኝታ ልጇን እንደገና ብታይ እመኛለሁ፡፡ ማሪያ ስታደግ የደረት ቅርጿን ለማስተካከል ጥቂት የውበት ቀዶ ሕክምና ያስፈልጋት ይሆናል፡፡ እንደሐኪም መጨረሻውን ሳላይ በእርግጠኝነት መናገር ባልችልም ማሪያ ጤነኛ ልጅ ትሆናለች ብዬ አምናለሁ፡፡ አንድ ቀን ማሪያ ስታድግ ይህን ታሪክ እንነግራታለን፡፡ ክስተቱ ለርሷም ለእኛም ታሪክ ሆኖ ይመዘገባል”
ማሪያ አሁን በሕጻናት ክፍል ተኝታ እያገገመች ነው። ዶ/ር ፍሬሁን አጠገቧ ሆኖ ቁልቁል ሲመለከታት እርካታው ከፊቱ ላይ አልጠፋም ነበር፡፡

(ምንጭ፡ አዲስ ጉዳይ መጽሔት ከአዲስ አበባ)

3 Comments

Comments are closed.

Share