ማንቸስተር ዩናይትድ በእንግሊዝ ነገሰ

ብዙ የተተቸው ቡድን በኦልድ ትራፎርድ ታሪካዊውን ገድል ፈፅሟል
– ‹‹ትልቅ ቦታ የምሰጠው ለመጀመሪያ ዋንጫችን ነው››
– ዘንድሮ ዩናይትድ በማሸነፍ ስነ ልቦናው ብቻ ከተፎካካሪዎቹ ተሽሏል

የቅዳሜ ከሰዓት በኋላውን የአውድ ፓርክ የመጨረሻ ደቂቃዎች ትዕይንት አስታውሱ፡፡ ጨዋታው ሊጠናቀቅ ጥቂት ደቂቃዎች ቀርተውታል፡፡ የስታዲየሙን አንድ ጥግ የሞሉት የማንቸስተር ዩናይትድ ደጋፊዎች ከፍ ባለ ድምፅ ‹‹መርሲሳይዶች ጉዳችሁን እያያችሁ ነው?›› እያሉ ይዘምራሉ፡፡ ዳኛው የባከኑ ሦስት ደቂቀዎችን ጨመሩ፡፡ የደጋፊዎቹ ዜማ ይበልጥ ደምቆ ይሰማ ጀመር፡፡ በዲሚታር ቤርባቾቭ ተቀይሮ የወጣው ሉዊስ ናኒ ደስታውን ለመግለጽ ወደ ሜዳው ጠርዝ ተጠግቶ የመጨረሻውን ፊሽካ ድምፅ በጉጉት ይጠባበቃል፡፡ የማንቸስተር ዩናይትድ ተከላካዮች ኳሷን ተረጋግተው እየተቀባበሉ ነው፡፡ ከብላክበርን አጥቂዎች አንዱ ሊጠጋቸው አልደፈረም፡፡ ሰር አሌክ ፈርጉሰን ተጋጣሚያቸው ባለቀ ሰዓት ጉድ እንዳያደርጋቸው አልፈሩም፡፡ ነገር ግን ሰዓቱ ያለ ወትሮው ሳይንቀረፈፍባቸው አልቀረም፡፡ አዛውንቱ አሰልጣኝ አንድ ጊዜ ዳኛው ፊልዳውድን ቀጥሎ ሰዓታቸውን እያፈራረቁ ሰኮንዶች ተቆጠሩ፡፡ በመጨረሻም የናፈቁትን የፊሽካ ድምፅ አደመጡ፡፡ አምና ጎል ሳያስቆጥሩበት ወጥተው ዋንጫቸውን ለቼልሲ ለማስረከባቸው ሰበብ በሆነው የብላክ በርን ሜዳ ድላቸውን አወጁ፡፡ ደጋፊዎቹ ያዘጋጁት ማንቸስተር ዩናይትድ 19፣ ሊቨርፑል 18 የሚል ፅሑፍ የሚያሳየው ትልቅ ጨርቅ ደምቆ ታየ፡፡
ከጨዋታው በኋላ ብዙ ጊዜ ለጋዜጣው መግለጫ የማይገኙት ፈርጉሰን ፈቃደኛ ሆነው ለጋዜጦቹ ጥያቄ ራሳቸውን አቀረቡ፡፡ ከዓመታት በፊት የሊቨርፑልን ኃያልነት ከስሩ ለመገርሰስ የዛቱበትን ንግግር የሚዲያዎቹ ሰዎች አስታወሷቸው፡፡ የሊቨርፑል እና ማንቸስተር ዩናይትድ የሊግ ዋንጫ ልዩነት 16-7 በነበረበት በ1986 ኦልድትራፎርድ የደረሰ ስኮትላንዳዊ ግን ‹‹የሚጠብቀኝ ትልቁ ስራ ሊቨርፑልን ከታላቅነት ማማው ማውረድ ነው›› ማለታቸውን እርግጠኛ ሆነው አላስታወሱም፡፡ ‹‹እንደዚያ ማለቴን በእርግጠኛነት ማስታወስ አልቻልኩም›› ሲሉ መለሱ፡፡ በእርግጥ ፈርጉሰን እነዚያን ቃላት ተናግረዋል፡፡ ሆኖም የንግግራቸው ትርጉም በተሳሳተ መንገድ እንደተወሰደ ማስታወስ የፈለጉ ይመስላሉ፡፡ ፈርጉሰን በወቅቱ ማለት የፈለጉት ሊቨርፑል በሊጉ ከዚያ በኋላ እንደልቡ እንደማይፈነጭ መግለፅ እንጂ የምን ጊዜም ሪከርዱን ስለመስበር አልነበረም፡፡ ምኞታቸውም ሊቨርፑል በሀያልነቱ የግሉ ያስመሰለውን ሊግ የሌሎችም የፉክክር መድረክ እንደሆነ በጠንካራው ቡድናቸው ማስመስከር ነበር፡፡
የሆነስ ሆነና ሰውየው ለብቻቸው ክለባቸውን በ12 የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫዎች የእንግሊዝ የምን ጊዜም ስኬታማ ክለብ ሊያደርጉት ምን አይነት ስሜት ተፈጥሮባቸው ይሆን? ‹‹ይህ ትልቅ ትርጉም ያለው ድል ነው፡፡ 19ኛውን ዋንጫችንን ማግኘታችን አስደናቂ ውጤት ነው፡፡ ጉዳዩ ሊቨርፑልን የመቅደም ወይም ያለ መቅደም አይደለም፡፡ በሀገሪቱ ታሪክ በርካታ የሊግ ክብሮችን በማግኘት ቀዳሚ መሆን መቻል በራሱ ታላቅ ስኬት ነው፡፡ በኤፍኤ ካፕ ድልም የሚስተካከለን የለም፡፡ ማንቸስተር ዩናይትድ ሊገኝበት የሚገባው ደረጃም ይህ ነው፡፡ ምናልባት አሁን ካለን የተሻለ የአውሮፓ ውድድሮች ስኬት ልናገኝ ይገባን ነበር፡፡ አሁንም ቢሆን ግን ታሪካችንን የምናስተካክልበት እድል አለን፡፡ በሀገር ውስጥ ውጤታማነት ግን ከፍታውን ይዘናል፡፡ እጅግ ደስተኛ የሚያደርገኝም ይህ ነው፡፡›› ይላሉ ፈርጊ፡፡ ከውጤታማው አሰልጣኝ ጋር ቆይቶ 12 የፕሪሚየር ሊግ ክብሮችን የተጎናፀፈው የ37 ዓመቱ ሪያን ጊግስ ሊቨርፑልን የቀደመበት 19ኛ የሊግ ድላቸው በልቡ ምን አይነት ትልቅ ቦታ እንደሚሰጠው ሲጠየቅ ለመልሱ አልዘገየም፡፡ ‹‹ሊቨርፑልን መብለጥ መቻላችን የሚታመን አይደለም፡፡ ሆኖም ከወሰድኳቸው 12 የሊግ ዋንጫዎች ሁሉ በእኔ እምነት ወሳኙ በ1993 ለመጀመሪያ ጊዜ ያሸነፍነው ዋንጫ ነው፡፡ ማንቸስተር ዩናይትድን ለሚያክል ክለብ 26 ዓመታትን ያለ ሊግ ዋንጫ መጠበቅ ረጅም የሚባል ጊዜ ነው፡፡ ስለዚህ የመጀመሪያውን ክብር ለማግኘት ትልቅ ትግል ይጠይቅ ነበር፡፡ የመጀመሪያ ዋንጫ ሁልጊዜም የተለየ ነው፡፡ ለእኔም የተለየ ነበር፡፡ ያደግኩት ታላቁ ሊቨርፑል በ1970 እና 80ዎቹ በእግርኳስ እንግሊዝ እና አውሮፓን ሲቆጣጠር እየተመለከትኩ ነው፡፡ እነሱ የዩናይትድ ቀንደኛ ተቀናቃኝ ቢሆኑም ስኬታቸውን መካድ አይቻልም፡፡ በእውቀቱ የትኛውም ክለብ አይወዳደራቸውም ነበር›› ሲል ለመርሲ ሳይዱ ክለብ ያለውን ክብርም አያይዞ ገልጿል፡፡ ማንቸስተር ዩናይትድ በ1993 የመጀመሪያ የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫውን (በፈርጉሰን ስር) ከማንሳቱ ከአንድ ዓመት በፊት በአሳዛኝ ሁኔታ ከመጨረሻው ጨዋታ ድሉን ለሊድስ ዩናይትዶች አሳልፎ ሰጥቷል፡፡ ፕሪሚየር ሊግ በአዲስ መዋቅር የጀመረውም በዚያን ክረምት ነበር፡፡ ከፕሪሚየር ሊግ ጋር አብሮ የተወለደ የመሰለው የፈርጉሰን ዩናይትድ ከዚያ ወዲህ ባለፉት ዓመታት በውድድር ነግሷል፡፡ በ18 ዓመታት ውስጥ ጣፋጭ ድሎችን ያጣጣመው ዌልሳዊው አማካይም ‹‹የመጀመሪያውን ዋንጫ ስናነሳ ከላያችን ላይ ትልቅ ሸክም የወረደ ያህል እፎይታ አግኝተናል፡፡ ሆኖም በቀጣይ የሚሆነውን በግሌ አላውቅም ነበር፡፡ እነዚህን ዓመታት ሁሉ ወደ ፊት መመልከትም አይጠበቅብኝም፡፡ ሆኖም ስኬትን ትፈልጋለህ፡፡ ምናልባት በዚህ ጊዜ አንድ ሰው መጥቶ በተጨዋችነት ዘመን የሊቨርፑልን ሪከርድ እንደምናልፍ ቢነግረኝ እንደ ቂል ቆጥሬው እስቅበት ነበር፡፡ እስኪ አስቡት፡፡ ክለባችን በወቅቱ ዋንጫውን ሲያነሳ ከ26 ዓመታት በኋላ የመጀመሪያ ነበር፡፡ ታዲያ ተጨማሪ 11 ዋንጫዎች አግኝቶ የሊቨርፑልን ክብር ለመውሰድ ማን ያስባል? ሆኖም ከመጀመሪያው ድላችን በኋላ የነበረን ጫና በመቀነሱ ቀጣዩን ማሸነፍ በንፅፅር ቀለል ያለ ነው፡፡›› ሲል የወርቃማው ዘመቻውን መጀመሪያ የስኬታቸው ቁልፍ ያደርገዋል፡፡
ፈርጉሰን በክለቡ በቆዩባቸው ዓመታት የገነቧቸው የተለያዩ ጠንካራ ቡድኖች አካል የነበረው ጊግስ በግል እና እንደ ቡድን ካገኛቸው ዋንጫዎች ብዛት ተጨዋቹን የተለየ ያደርገዋል፡፡ አሰልጣኙ እስካሁን ከገነቧቸው የዩናይትድ ቡድኖች ውስጥ የትኛው የበለጠ ጠንካራ እንደነበር ለመጠየቅም ጊግስ ተገቢው ሰው ይመስላል፡፡ ሆኖም ጊግስ ለመልሱ ሲበዛ ተጠንቅቆ ‹‹ማነፃፀር ያስቸግራል፡፡ የተለያዩ ቡድኖችን በተለያየ መመዘኛ አወዳድረን ልንከራከር እንችላለን፡፡ እንደ እኔ ግን ስኬታማ የነበሩት ቡድኖቻችን በሙሉ የራሳቸው የሆነ የተለየ ብቃት ነበራቸው፡፡ ከሁሉም ጋር መጫወት መቻሌ ደስተኛ ነኝ›› ይላሉ፡፡
ጊግስ ይህን ይበል እንጂ እንደ ብዙዎች እምነት የዘንድሮው ዩናይትድ በቅርብ ጊዜ በክለብ ማሊያ ከታዩት ቡድኖች ሁሉ በንፅፅር ደካማው መሆኑን የሚከራከሩ አሉ፡፡ እንዲያውም ባለፈው ፌብርዋሪ የዩናይትድን መዳከም የተመለከተው ጋዜጠኛ አሌክሳንደር ኔተር ቶን የፈርጉሰን ቡድን የክርስቲያኖ ሮናልዶ እና ቴቬዝ መልቀቅ ከፈጠረበት ተፅዕኖ ጨርሶ አለመላቀቁን እርግጠኛ ሆኖ ፅፏል፡፡ በእርግጥ ማንቸስተር የዩናይትድ የማታ ማታ 19 ዋንጫውን አንስቷል፡፡ ሆኖም የቡድኑ አቋም አሁንም ያልተዋጠላቸው አሉ፡፡ እነዚህ ወገኖች ዩናይትድ ሻምፒዮን የሆነበትን በንፅፅር ያነሰ ጠቅላላ ነጥብ እና ቡድኑ ከሜዳው ውጪ የነበረውን ደካማ ረከርድ እንደ ማስረጃ ያቀርባሉ፡፡ የዩናይትድን ሻምፒዮንነት ከቼልሲ አርሰናል እና ማንቸስተር ሲቲ ድክመት ጋር ያያይዙታል፡፡ ለዚህም አዲሱ የፈረንጆች ዓመት እስኪገባ ድረስ ከሜዳው ውጪ ከአንድ በላይ ጨዋታ ያላሸነፈው የኦልድትራፎርዱ ክለብ የሊጉ መሪ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡
ፈርጉሰን ግን የዘንድሮው ቡድን ደካማ ነው መባሉ ያስደሰታቸው አይመስሉም፡፡ ቡድኑ ሻምፒዮን የሆነው በተፎካካሪዎቹ ድክመት ነው የመባሉ ነገር አልጣማቸውም፡፡ ‹‹ማንቸስተር ዩናይትድንም ሆነ ፕሪሚየር ሊጉን እንደተዳከመ መናገር ተገቢ አይደለም፡፡ እንዲያውም ውድድሩ ከመቼውም ጊዜ በላይ ለማሸነፍ አስቸጋሪ ሆኗል፡፡ ሊጉን ለመመዘን አጠቃላዩን ሁኔታ መመልከት ይገባል›› ሲሉ በርካታ ነጥቦች የመጣላቸው ምስጢር በሊጉ ጠንካራ ተጋጣሚ ቡድኖች መበራከታቸው እንደሆነ ሊያስረዱ ይሞክራሉ፡፡ ጊግስ በበኩሉ የሚደርስባቸው ትችት እውነተኛውን የቡድናቸው ገፅታ ያላገናዘበ መሆኑን ያምናል፡፡ ‹‹በፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮኖች ነን፡፡ በቻምፒየንስ ሊግ ለፍፃሜ ደርሰናል፡፡ ታዲያ ይህ ቡድን ደካማ የሆነው በምን መመዘኛ ነው?›› ሲል ዩናይትድ እንደምንጊዜውም ኃያል እንደሆነ ይናገራል፡፡
በእርግጥ ሊጉ እስከመጨረሻዎቹ ጥቂት ሳምንታት ድረስ የሶስት ክለቦችን ፉክክር አሳይቶናል፡፡ ሆኖም የአምናው ሻምፒዮን ቼልሲ በውድድሩ ሁለተኛው ዙር የውጤት ቀውስ ውስጥ ነበር፡፡ በ11 ተከታታይ ጨዋታዎች 11 ነጥቦች ብቻ አግኝቶ የነበረው የካርሎ አንቼሎቲ ቡድን በአንድ ወር ከግማሽ ጊዜ ውስጥ ወደ ዋንጫ ፉክክሩ መመለሱ በራሱ ወደ አንድ መደምደሚያ ያንደረድረን ይሆናል፡፡ አርሰናል እንደተለመደው ሁሉ በሊጉ መልካም የሚባል ጉዞ አድርጎ ወደ መጨረሻው ተንኮታኩቷል፡፡
ማን.ቸስተር ዩናይትድ እስከመጨረሻዎቹ ከተፎካከሩት ቼልሲ እና አርሰናል የተለየው የአሸናፊነት ስነ-ልቦናው ነው ማለት ይቻላል፡፡ ቀያይ ሰይጣናቱ ነጥብ ጥለው ሊወጡ በተቃረቡባቸው ጨዋታዎች በፍፁም ጀግንነት እንደሻምፒየን ተፋልመው ውጤታማ ሆነዋል፡፡ የዘንድሮው ዩናይትድ በኖቬምበር ከአስቶንቪላ ጋር 2-2 ሲለያይ ብዙዎች ክለቡ ነጥብ መጣሉን አውርተዋል፡፡ ሆኖም 2-0 ከመመራት ተነስቶ በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ውጤቱን አቻ ያደረገው ዩናይትድ በተከታዩ ሳምንት ብላክ በርንን 7-1 አሸንፎ የሊጉን አናት ተቆናጧል፡፡ በውድድር ዘመኑ ዩናይትድ በዎልቭስ ያልተጠበቀ ሽንፈት እስኪገጥመውም ድረስ የቀጠለው የቡድኑ ያለመሸነፍ ጉዞ ምስጢርም ይኸው የአሸናፊነት ስነ-ልቦናው ነው፡፡ ከዎልቭሱ ጨዋታ በፊት በብላክ ፑል 2-0 እየመሩ 20 ደቂቃዎች ሲቀሯቸው 3 ጎሎች አስቆጥረው 3 ሙሉ ነጥቦችን ወስደዋል፡፡ በእንደዚህ ያሉ ጨዋታዎች ብዙዎቹ ቡድኖች የሚጫወቱት ቢበዛ አቻ ለመውጣት ነው፡፡ ዩናይትድን ለየት የሚያደርገው ሁል ጊዜም የማሸነፍ ረሀቡ ነው፡፡ በአፕሪል ወር ዌስትሀም ላይ ያደረጉትም ተመሳሳይ ነው፡፡ 2-0 እየተመሩ እረፍት የወጡት ዩናይትዶች በሁለተኛው የጨዋታው አጋማሽ 4-2 አሸነፉ፡፡ ይህ ውጤት ለክለቡ እጅግ አስፈላጊ ነበር፡፡ ምክንያቱም ከዚያ በፊት ዩናይትድ ባደረጋቸው ሁለት ተከታታይ ጨዋታዎች በሊቨርፑል እና ቼልሲ ተሸንፏል፡፡ ሆኖም ቡድኑ በሽንፈቶቹ ሳይደናገጥ ወደ አሸናፊነቱ ተመልሷል፡፡ በካርሊንግ ካፕ ፍፃሜ የአርሰናልን የውድድር ዘመን ገፅታ ለቀየሩት በርሚንግ ሀሞች የሚጫወተው የቀድሞው የዩናይትድ ግብ ጠባቂ ቤን ፎስተር የፈርጉሰን ቡድን ለማሸነፍ የተፈጠረ መሆኑን ይናገራል፡፡ ‹‹በብላክፑል 2-0 እየተመሩ እንኳን ጨዋታውን እንደሚያሸንፉ እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ አደገኞች ናቸው፡፡ ስለዚህም ውጤት ሊቀይሩ እንደሚችሉ ሁልጊዜም ትጠብቃለህ፡፡ ፈርጉሰን ይህንን የአሸናፊነት ባህርይ ካልተመለከቱብህ ከጅምሩ አያስፈርሙህም፡፡ ይህንን የተጨዋቾች ስሜት የትም አታገኘውም፡፡ ሌላው ቀርቶ ቼልሲዎች ጋር አታገኘውም፡፡ አርሰናል ኒውካስልን 4-0 ከመራ በኋላ ነጥብ ጥሎ የወጣበትን ጨዋታ ውጤት በዩናይትድ አትመለከተውም፡፡ ሊሆን አይችልማ! ምናልባት ዩናይትድ ጎሎች አክሎበት የጎል ቁጥሩን 6 ወይም 7 ያደርሰው ይሆናል፡፡ እንጂ እንደ አርሰናል አቻ ሊወጣ አይችልም፡፡›› ሲል የፈርጉሰንን ቡድን የተለየ ባህርይ ሊገልፅ ይጥራል፡፡ ፈርጉሰን ምን ጊዜም የሊጉ ክብር የሚሄደው ወጥ አቋም ወደ አበረከተ ቡድን መሆኑን ይናገራል፡፡ የዘንድሮው ቡድናቸው የሚወርድበትን ትችት ያህል ደካማ አለመሆኑን ለማስመስከር ሌላ ማስረጃ ያቀርባሉ፡፡ ማንቸስተር ዩናይትድ ከየትኛውም ተቀናቃኙ የላቀ ጎል ሲያስቆጥር ያሸነፈባቸው ጨዋታዎች ብዛትም ቀዳሚ ያደርገዋል፡፡ ምርጡ ተጨዋቹ ዋይኒ ሩኒ በውድድር ዘመኑ የመጀመሪያ አጋማሽ በጥሩ አቋሙ ላይ ባይገኝለትም የ2007/08 የጥንድ ዋንጫ ታሪኩን ሊደግም ተቃርቧል፡፡ የእንግሊዝ እግርኳስን ንግስና ግን ከወዲሁ ተረክቧል፡፡ ልዑል የነበረው ዩናይትድ አሁን ዘውዱን ጭኗል፡፡
እንደ ብዙዎች እምነት የዩናይትድ የሻምፒዮንነት ምስጢር ተጫዋቹ ከተፎካካሪዎቹ የተሻለ የአዕምሮ ጥንካሬ ይዘው መገኘታቸው ነው፡፡ ሆኖም ቡድኑን ውጤታማ ያደረጉትን ሌሎች ነጥቦች መመልከት እንችላለን፡፡
በኦልድትራፎርድ አልተደፈሩም
ማን.ቸስተር ዩናይትድ በቅርብ ዓመታት ባልታየ መልኩ ከሜዳው ውጪ ለማሸነፍ ተቸግሯል፡፡ አምና ከሜዳው ውጪ ካደረጋቸው 19 ጨዋታዎች 11ዱን ያሸነፈው ቡድን ዘንድሮ እስከ ጃንዋሪ ድረስ ከአንድ የሜዳ ውጪ ድል በላይ አልቀናውም፡፡ ሆኖም በሜዳው የነበረው ውጤት አስደናቂ ሊባል ይችላል፡፡ ዘንድሮ በኦልድትራፎርድ ከዌስትብሮም ጋር አቻ ከመለያየቱ ውጪ ነጥብ አልጣለም፡፡ በሜዳው ሊያገኛቸው የሚችለው 54 ነጥቦች 52ለቱን ሰብስቧል፡፡
የፈርጉሰን ውጤት ረሀብ
በኦልድትራፎርድ ፈርጉሰንን በሙያው የሚረዳቸው አንጋፋው ጋዜጠኛ ዴቪድ ሚክ ሁልጊዜም ከጠዋቱ 1፡30 ሰዓት በካርሊንግተን የልምምድ ማዕከል እንዲገኝ ተነግሮታል፡፡ ሚክ ሁል ጊዜም ወደ ቦታው ሲደርስ አሰልጣኙ ቀድመውት መገኘታቸው ያስገርመዋል፡፡ ‹‹ዛሬ እንኳን ልቅደማቸው ብዬ በጊዜ የደረስኩ ሲመስለኝ እርሳቸው ለግማሽ ሰዓት ያህል ጂምናዚየም ውስጥ እንደቆዩ እረዳለሁ›› ሲል አሰልጣኙ አሁንም ታታሪ መሆናቸውን ገልጿል፡፡ ይህንን የተመለከተ ሰው ፈርጉሰን ከዘጠኝ ዓመታት በፊት ከስራቸው ራሳቸውን ሲያነሱ ነበር መባሉን መቀበል ያስቸግረዋል፡፡ ፈርጉሰን በቅርቡ የአምስት ጨዋታ ቅጣት ቢጣልባቸውም ቡድናቸውን በአግባቡ መርተዋል፡፡
የወጣቶች ውጤታማነት
በክርስቲያኖ ሮናልዶ ተሸፍኖ የቆየው ናኒ በተደጋጋሚ ከመጎዳቱ በስተቀር ወሳኝ ጎሎች እያስቆጠረ ለግቡ የተመቻቹ በርካታ ኳሶች አቀብሏል፡፡ ወጣቱ ብራዚላዊ የመስመር ተከላካይ ራፋኤል ዘንድሮ ልዩ ነበር፡፡ ዘግይቶም ቢሆን ወደ ቡድኑ የተመለሰው መንትያው ፋቢዮም ጥሩ አቋም አሳይቷል፡፡ ክሪስ ስሞሊንግ በአስገራሚ ፍጥነት በቡድኑ የሪዮ ፈርዲናንድን ቀዳዳ ሲሸፍን ተስተውሏል፡፡ ከሁሉም በላይ ሀቪዮር ሄርናንዴዝ አስተዋፅኦ የማይታመን ነበር፡፡ በተጠባባቂ ወንበር ላይ ሆኖ የእንግሊዝን እግርኳስ እንዲለምድ ተብሎ የመጣው ሜክሲኳዊ ለዩናይትድ ሻምፒዮንነት አስፈላጊ ነበር፡፡
አንጋፋዎቹ ተፅዕኖ መቀጠል
ጋሪ ኔቭል ዘንድሮ እግርኳስ መጫወት ይብቃኝ ብሏል፡፡ ፖል ስኮልስም ዘንድሮ በንፅፅር ተዳክሞ ታይቷል፡፡ በአንፃሩ ሪያንጊግስ በመሀል አማካይ መስመር ብስለቱን እየተጠቀመ ቡድኑን ረድቷል፡፡ እንዲያውም በዌስትሀሙ ጨዋታ ለ45 ደቂቃዎች የግራ መስመር ተከላካይ ሆኖ ተጫውቷል፡፡ ጊግስ በመከላከል ላይ ብዙ ማተኮሩ በጎል ማግባቱ ረገድ ብዙ እንዳይሳተፍ አድርጎታል፡፡ ሆኖም ባለፉት 19 ዓመታት በዩናይትድ ማሊያ በየዓመቱ ቢያንስ 1 ጎል የማስቆጠር ሪከርዱ እንደተጠበቀ ነው፡፡
የሩኒ ውዝግብ አልጎዳቸውም
የዩናይትድ ውጤታማነት ሩኒ በውድድር ዘመኑ መጀመሪያ አካባቢ የቡድኑን ጥንካሬ አስመልክቶ የሰጠውን አስተያየት የሞኝ የሚያስመስል ነው፡፡ የማታ ማታ በከፍተኛ ደመወዝ ለአምስት ዓመታት ኮንትራቱን ያራዘመው አጥቂ ለረጅም ጊዜ አቋሙን ለመመለስ ቢቸገርም ቀስ በቀስ የቡድኑ ቁልፍ ሆኗል፡፡ እንደተፈጠረው የቡድኑ ጓደኞቹ ጋር ቅራኔ ውስጥ ያልገባው እንግሊዛዊ ጎል ከማስቆጠሩ በተጨማሪ ለቡድኑ የአጥቂ አማካይነት ሚና ሸፍኖ ሲጫወት ቆይቷል፡፡ ሩኒ በተለያዩ ጨዋታዎች የመስመር ተከላካይም ጭምር እየሆነ የቡድኑ ተጨዋችነቱን አሳይቷል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  Ethiopia names 22 players for Nigerian Encounter
Share