የማለዳ ወግ … ይነጋል ጨለማው … !

ከነብዩ ሲራክ

የጨለመ ቀን ይነጋል ፣ ክፉ ቀን ያልፋል ! የሃገር መሪዎች ለህዝብ ቆመው ትክክለኛ ምርጫ እንኳ አድርገው ስልጣናቸውን ለተተኪው ትውልድ ባያስተላልፉ ሲያረጁና ሲያፈጁ ጥቅማቸውን የሚያስከብርላቸው ተክተውም ቢሆን መሸኘታቸው አይቀሬ ነው! ለህዝብ እና ለሃገር ብሔራዊ ጥቅም ያለተጋ መንግስት በተቀያየረ ቁጥር በዜጎች ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ይህ ነው የማይባል ተጽዕኖን ያሳድራል። ተጽኖ አድራጊነቱ የሚከወነው በዋናነት በመንግስት መሆኑ ባይካድም ለሆዳቸው ያደሩ አጎብጓቢ የአበራካችን ክፋዮች የነዋሪው ውሎ አዳር ላይ የሚያደርሱት ተጽዕኖ እንዲህ በቀላሉ ሊገልጹት የሚችሉት አይደለም! አይቻልምም ! በዘመነ ደርግ ከስርአቱ በላይ አድርባዮች ለስርአቱ ያላቸውን ታማኝነት ለማሳየት ሲሉ ብቻ በገዛ ወገናቸው ላይ ይፈጽሙትን የነበረው ግፍ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው!
ያ ዘመን አከተመ ብለን ትንሽ ሳንተነፍስ ዛሬም በሌላ አደጋ ተዘፍቀናል ። ወደ ትላልቁ ጉዳይ አልገባም ። ዛሬ በ21ኛው ክፍለ ዘመን ዜጎች በዘመናዊ ባርነት ከህግ ማዕቀፍ ውጭ ስለመሸጣቸው እማኝ በሆንኩበት የአረብ ሃገር ኑሮ የራሳችን ዜጎች መብት ይከብር ብሎ መብታችን ለማስከበር ሃላፊነታቸውን ስላማይዋጡ ሃላፊዎች መናገር ሃጢያት ሆኖ ያስወነጅላል ! ” ህገ መንግስት አልተከበረልንም!” ያሉ ሰላማዊ ዜጎች በተሰጣቸው የህግ ማዕቀፍ መሰረት ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግን ተከልክልው እየተመለከትን ነው ። እኔ እሰከማውቀው እና በአደባባይ ሲነገር እንደሰማሁት አንድ መንግስት በስደት ላይ ያሉ ዜጎቹ ስቃይ ይሰማዋል። ግን ስቃዩን ለማስቆም የሚችሉ ተወካዮችን በአረብ ሃገር ከማሰማራት ጀምሮ በሃገር ቤት የሚሰራውን ለእድሜ ያልደረሱ ታዳጊ እህቶቻችን በደላሎች ወደ አረብ ሃገራት እየተጋዙ የሚፈጸመውን ግፍ ተከታትሎ ማስቆም አልቻለም ። መንግስት ያላቻ ጋብቻ አይፈቀድም እያለ በቤተሰብ አማካኝነት የሚመሰረት ትዳርን ህገ ወጥ ነው ብሎ ማገዱ ባይከፋም ትዳር እንዳትመሰርት በእድሜዋ ምክንያት የተከለከለችው ጉብል ወደ አረብ ሃገር ለስራ ብቁ የሚያደርግ እድሜ ቆልላ እዚህ ሳውዲ አግኝቻት አጫውታኛለች ። ብዙዎች አንድ አይነት ባይሆን በለያዩ መንገዶች በሚከወን ሂደት ይሰደዳሉ ። የድልላ ስራው ከሃገር ቤት እሰክ ውጭ ሃገር በስርአቱ ደጋፊዎች የሚመራ በመሆኑ እንቅስቃሴው በግፍ ሲካሔድ ይህም የስደቱን ኑሯችን እየከፋ ለመሔዱ እማኝ ከሆነን መልካም ነው ።
መንግስት በራሱ ሰአት ከፖለቲካ ፍጆታ ላላለፈው ጥቅም የሚያሳየን የከፋ የስደት ኑሮ ይቀየር ዘንድ የሚሰራው ስራ አያበረታታም። የመንግስት ተወካተዮቻች እንኳንስ ችግር ብሶታችን ሰምተው ሊያሰሙ ፣ እንዳንሰማ እንዳናይ እንዳንሰማ ማግለል ይዘዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከፍተኛ ሃላፊዎች በተደፈጋጋሚ ወደ ሳውዲ ቢመጡም ነዋሪውን አያጋኟቸው ። መረጃ ሰበሰብን ብለው የሚሔዱት ፍትሃዊ የመብት ጥበቃ ከማያደርጉት ሃላፊዎች፣ ከፖለቲካ ካደሬዎችና በልማት ስም ከተደራጁ ማህበራት በመሆኑ ለቀጠለው ችግር መፍትሔ ሊያገኙለት አልቻሉም ! ግፍ ቢበዛም አቤት የሚባልበት ቦታ አጥተናል !የሚነገር የሚጻፈውን አልሰማ ላለ መንግስት ደግሞ የዜጎችን መብት ስል ማስከበር ህገ መንግስቱ የሰጠውን መብት መጠቀምና ጥያቄን ማቅረብ ተገቢ ነው። ተቃውሞን በሰላማዊ ሰልፍ ማቀርብ ደግሞ ብቸኛው ተገቢ መንገድ ነው። ይህንም መብት በመንግስት ስለመራቁና እዚያ ለመድረስ መሔድ ያለብንን ጉዞ አርቆ አጥቦታል! ህዝብ መብቱን ለመጠቀም መንገዱ ከጠበበበት ደግሞ አመጻና የከረረ ተቃውሞን በማምጣት ሃገርን ወደ ሁከት ህዝብን ወዳለመረጋጋት ይገፋልና ተገቢ አይደለም ! በጃንሆይ የሆነው በደርግ ፣ በደርግ የነበረው ተጠናክሮና መንገዱን ቀይሮ በኢህአዴግ መንግስት እየተሰራበት ያለው የመብት ገፈፋ ቆሞ ላስተዋለው ያማል! ሰው በነፃ ሃሳቡ ፣ለሃገሩ ይበጃል ያለውን በግልና በቡድን ህጋዊ በሆነ መንገድ ተደራጅቶ ድምጹን ሰላሰማ ዛሬም ይታሰራል ፣ይደበደባል ፣ ይገደላልም ! ይህ ሁሉ አውጥቸ አወረድኩና ቢከፋኝ በማለዳ ወጋወጌ የዘመን ሂደት ፣ የሰው ለሰው ጉድኝት ትዝብቴን ለማዘከር ” የጨለማው ይገፋል ይነጋል ” ስል ስንኝ ቢጤ ቋጥርኩ …. ይህም ይገኝበታል …
ይነጋል …
“ይሁን ያልፋል ! ” ብለን ዝም ብለን በቻልነው
ያንዱ ቤት ሲፈርስ ባያመው ያ ሌላው
የወገኑ እንግልት ዘልቆ ባይሰማው
ግፍና በደሉ እሱን ሰላልነካው
ነግ በኔን ዘንግቶ አይኑን ቢሸፍነው
ጀሮው እየሰማ “አልሰማሁም “ቢለው
አይን አይቶ እንዳላየ ለእይታ ቢያገለው
የዘመን ክፉ አለው ፣ የዘመን ደግ አለው
እንደከፋ አይቀርም፣ ይነጋል ጨለማው !
ከህሊና ፍርጃ ማያስሸሽ መከራው!
ብርሃን ይመጣል ይነጋል ጨለማው!
(ሙሉውን ግጥም ከዚህ ጋር ተያይዟልና ያንብቡት! )
ቸር ያሰማን !
ነቢዩ ሲራክ

ተጨማሪ ያንብቡ:  በማተብዋ ልዳኝ - ወድቃ የተነሳችው - (ከስንሻው ተገኘ)
Share