እያሸበሩ … “አሸባሪ” ፍለጋ … – በነስረዲን ኡስማን

… የኢህአዴግ መንግሥት አክራሪነትን እና ሽብርተኝነትን በመዋጋት ሽፋን ከተከተለው ኢስላምን እና ህዝበ ሙስሊሙን ዒላማ ያደረገ ፖሊሲና ይህን ፖሊሲ ለማስፈፀም ከሚሠራቸው በርካታ ፀረ ኢስላም ስራዎች አንድ ነገር መናገር ይቻላል፡፡ ገዢው ፓርቲ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችን ወደ ሁከትና ብጥብጥ፣ ብሎም ወደ ሽብርተኝነት ለመግፋት አጅግ አድርጎ ይፈልጋል፡፡ ይህ ዝንባሌ በህዝበ ሙስሊሙ ላይ እንዲፈጠር በማድረግም “የዓለም አቀፉ ፀረ ሽብር ጦርነት” አጋርነቱን ማደስ፣ በዚህም ከአሜሪካና ከምዕራብ አውሮፓ አገራት የማያቋርጥ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ እና የዲፕሎማሲ ድጋፎችን ማግኘት ይፈልጋል፡፡ … በአገር ውስጥ ለሚወስዳቸው ዴሞክራሲን የማቀጨጭ፣ ነፃነትን የመገደብ፣ መልካም አስተዳደርን ለማስፈን ያለመቻል ችግሮች፣ በአጠቃላይም በአገሪቱ ውስጥ የሕግ የበላይነት አለመኖርን “በፀረ ሽብር ትግሉ አስገዳጅነት የተፈጠሩ” አስመስሎ ለማቅረብ ይፈልጋል፡፡ የሰብአዊ እና ዴሞክራሲያዊ መብት ጥሰቶች እና የነፃነት ገደቦችን ሁሉ “የህዝብን ሰላም ለመጠበቅ ሲባል በህጋዊ መንገድ የተጣሉ ገደቦች” የማስመሰል ፍላጎት እንዳለው ባለፉት ዓመታት ከወሰዳቸው ፖለቲካዊ እርምጃዎች እና እርምጃዎቹን ተገቢ ለማድረግ ካቀረባቸው ምክንያቶች መገንዘብ ይቻላል፡፡

… ምንም እንኳ ኢህአዴግ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ያነሷቸውን ህገ መንግሥታዊ የሃይማኖት ነፃነት ጥያቄዎች ለማፈን የ“ሽብርተኝነት” አቧራ ለማስነሳት እጅግ ቢደክምም፣ ራሱ መንግሥት ለህጋዊ እና ሰላማዊ የህዝቦች የመብት ጥያቄ ምላሽ እየሰጠ ያለው የ“ሽብርተኝነት” ተግባር በመፈፀም ነው፡፡ በዚህም መሠረት በመጀመርያ የሞከረው፣ “አንድ ግደል፤ አሥር ሺህዎችን አሸብር” የሚለውን የቻይኖች አባባል ተግባራዊ ማድረግ ነበር፡፡ … የካቲት 26፣ 2004 መንግሥት የህዝበ ሙስሊሙን ጥያቄዎች ለማድበስበስ መሞከሩን ተከትሎ፣ ህዝበ ሙስሊሙ ሰላማዊ ትግሉን አጠናክሮ ሲቀጥል፣ መንግሥት አስቀድሞ በሰላማዊነቱ ያወደሰውን ህዝብ አክራሪ እና አሸባሪ እያለ ማብጠልጠል ጀመረ፡፡ የ“አሸባሪነት አቧራን” ማቡነንም የመንግስት መገናኛ ብዙኃን ተቀዳሚ አጀንዳ ሆነ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሳውዲ መንግሥት በዜጎቻችን ላይ እየፈፀመ ያለውን ግፍ በጥብቅ እናወግዛለን!!

… ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር “ሱፊ” እና “ሰለፊ”፣ “ነባሩ” እና “አዲሱ እስልምና” ብለው ከዘባረቁ፣ እንዲሁም “የአል ቃኢዳ ህዋስ ኢትዮጵያ ውስጥ አርሲና ባሌ አካባቢ ተገኝቷል” ካሉ በኋላ፣ የሰውየውን ንግግር ከአምላክ ቃል የበለጠ የሚያምኑት ሎሌዎች፣ ‹‹በጨለማ ቤት ውስጥ የሌለን ጥቁር ድመት ፍለጋ›› ጀመሩ፡፡ እርሳቸው እንደ ዋዛ የተናገሯትን ቃል ይዘውም ህዝብን ለማሸበር ያለመ ግድያቸውን አርሲ ውስጥ በምትገኘው አሳሳ ወረዳ ጀመሩ፡፡ ኢህአዴግ ህዝበ ሙስሊሙ በዚህ ግድያ ተሸብሮ መብቱን የማስከበር ሰላማዊ ትግሉን ያቆማል፣ “አንድ ሲገደል፣ አስር ሺህዎች ይሸበራሉ” ብሎ በእጅጉ ተስፋ አድርጎ ነበር፡፡ … ነገር ግን፣ በተግባር የሆነው የዚያ ተቃራኒ ነው፡፡ ሰላማዊው ትግል ሌሎች መቶ ሺህዎችን አሰለፈ፡፡ ከዚያም የኢህአዴግ ሎሌዎች አዲስ አበባ እና ደሴ ላይ አያሌ ሙስሊሞችን መስጂድ ድረስ ገብተው ደበደቡ፣ አያሌዎችንም ወስደው አሰሩ፤ ለጠላት በማይሰነዘር የጭካኔ በትር ቀጠቀጡ፣ የአሸዋ ኮረት ላይ በእንብርክክ እያስኬዱ አሰቃዩ፤ … ግና ሰላማዊ ትግሉ ከመቆም ይልቅ ሌሎች መቶ ሺህዎችን ከሩቅ ተመልካችነት ወደ ንቁ ተሳታፊነት ጠራ፡፡ … ነገር ግን ኢህአዴጎች አሁንም እርም አላሉም፡፡ ደቡብ ወሎ፣ ገርባ ላይ ሌሎች አራት ሰላማዊ ሙስሊሞችን ገድለው፣ በብዙዎች ላይ የአካል ጉዳት አደረሱ፡፡ … በዚህም ጊዜ “ለዲናችን እንሞታለን!” የህዝበ ሙስሊሙ መፈክር ሆነና መብትን የማስከበር ሰላማዊ ትግሉ ይበልጥ ተፋፍሞና ተጋግሞ ቀጠለ፡፡ …

ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ኢህአዴጎች ሊገባቸው በማይችል ጠንካራ የአንድነት ገመድ ተሳስረዋል — “የአላህን የአንድነት ገመድ” አጥብቀው ይዘዋል፡፡ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር “ነባሩ” የሚል ማዕረግ የሰጡት አህባሽ ይህንን የአንድነት ገመድ ለመበጠስ ቅንጣት ታህል አቅም የለውም፡፡ በወንጀለኛ የፌደራል ፖሊሶች የሚተኮሱ ጥይቶችና ከብረት የተሰሩ የግፈኛ በትሮች ህዝበ ሙስሊሙን ለበለጠ ሰላማዊ ትግልና መስዋዕትነት ያዘጋጁታል እንጂ ከቶውኑም ከትግሉ አያሸሹትም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአማራ ምሁር ነኝ ያልክ ሁሉ የውስጡም የውጩም ቁማር ይግባህ

በህገ መንግሥት ለተረጋገጠው የሃይማኖት ነፃነታችን መከበር እስከመጨረሻው በሰላማዊ መንገድ ብቻ እንድንታገል በአላህ ስም ቃል ያስገቡን ፍፁም ሰላማዊና ቅን መሪዎቻችን በወህኒ ቤት የሚያሳልፏት እያንዳንዷ ደቂቃ፣ በአላህ ፈቃድ የጽናታችን መሠረት ይበልጥ የሚደድርባት እንጂ ከቶውኑም ከሰላማዊ ትግላችን የምንንሸራተትባት አትሆንም፡፡ በአላህ (ሱብሃነሁ ወተዓላ) ፈቃድ መቼም ይሁን መቼ፣ እናንተ በምትሹት የሁከት መንገድ ላይ እኛን አታገኙንም፡፡ እናንተ በምትሹት የሁከት መንገድ ላይ በመገኘት ታላቅ መስዋዕትነት እየከፈሉ በሚገኙት ቅን መሪዎቻችን ላይ ክህደትን አንፈጽምም፡፡ ይህንን መቼም አናደርገውም፡፡ ይህ ቃላችን ነው፡፡ በየትኛውም የአገሪቱ ክፍል የሚነሳ ሁከት በእናንተ እና በእናንተ ብቻ የሚለኮስ እንደሆነ ድፍን ዓለም እስኪያውቅ ድረስ ፍፁም ሰላማዊ ከሆነው የመብት ትግላችን አንዲት ጋት አናፈገፍግም፡፡

ሦስት ግልጽ ጥያቄዎችን በፊርማችን ውክልና በሰጠናቸው የተከበሩ ዜጎች (ሽማግሌዎች) አማካይነት አቅርበንላችኋል፡፡ ከኢትዮጵያዊ ወግና ልማድ ፈጽሞ ባፈነገጠ ነውረኝነት የእኛን የሚሊዮኖቹን ወኪሎች ለወህኒ ስትዳርጉ ደግሞ “ተወካዮቻችን ይፈቱ” አራተኛው ጥያቄያችን ሆኗል፡፡

ሰላማዊው ትግላችን የሚያበቃው እነዚህ ጥያቄዎቻችን ከፖለቲካዊ አሻጥር እና ድራማ በራቀ መንፈስ ተገቢ ምላሽ ሲያገኙ ብቻ ነው፡፡ ላነሳናቸው ግልጽ ጥያቄዎች ተገቢ ምላሽ በመስጠት ፈንታ ህጋዊ ውክልና ሰጥተን ወደ እናንተ የላክናቸውን ቅን መሪዎቻችንን በወህኒ ማሰቃየታችሁ ሁላችንም ራሳችንን ለመስዋዕትነት እንድናዘጋጅ ከማድረግ ውጪ ለእናንተ ምንም አላተረፈላችሁም፡፡ ህዝብን በብረት ቆመጥ ከመደብደብም አንዳችም ትርፍ አታገኙም፡፡ … ለህዝብ ጥያቄ ተገቢ ምላሽ መስጠት ሊያስከብራችሁ የሚችለውን ያህል፣ በጠብመንዣ በመመካት የንፁኃንን ደም ማፍሰስ በህዝብ ለመተፋት ይዳርጋችኋል፤ እስካሁን ካልተተፋታችሁ ማለቴ ነው! … እየተጓዛችሁበት ያለው መንገድ የትም አያደርስም፡፡ እኛ እንደሆንን እስካሁን የህይወት መስዋዕትነት ከከፈሉት የአርሲ፣ የገርባ እና የሐረር ወንድሞቻችን የበለጠ ነፍስ የለንም፡፡ ስለ ሃይማኖት ነፃነታችን ስንል ባነሳነው የመብት ጥያቄ ሳቢያ ከህጋዊ ወኪሎቻችን ጀምሮ በየክፍለ ሃገሩ በእስር ከሚማቅቁት አባቶቻችን እና ወንድሞቻችን የላቀ ስጋም የለንም፡፡ ለህጋዊ፣ ፍትኃዊ እና ሰላማዊ ጥያቄያችን ምላሻችሁ በግፍ ላይ ግፍ፣ በወንጀል ላይ ወንጀል መደራረብ ከሆነ … ዝለቁበት፡፡ እኛም እስትንፋሳችን እስካለች ድረስ ሰላማዊ ትግላችንን ይበልጥ አጠናክረን እንቀጥላለን፡፡ ለምናምንበት ዓላማ እስከ መጨረሻው እስትንፋሳችን በሰላማዊ መንገድ መታገል እንጂ ድላችንን ማየት አያስጨንቀንም፡፡ አላህ ያደለው የድሉን ፍሬ ያያል፡፡ እንዲሁም አላህ ያደለው ሰማዕት (ሸሂድ) ይሆናል፡፡ በአላህ ፈቃድ ሁላችንም ለሃይማኖት ነፃነታችን መከበር እስከ መጨረሻው በሰላማዊ መንገድ እንታገላችኋለን፡፡ እስከዚያው ድረስ በግፍ ላይ ግፍ፣ በወንጀል ላይ ወንጀል ታነባብራላችሁ እንጂ፣ ሐቅን ይዞ በፍፁም ሰላማዊ መንገድ የሚታገላችሁን የኢትዮጵያ ሙስሊም ኢንሻአላህ አታሸንፉትም፡፡ አላሁ አክበር፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  እግዚኦታችን አልሰምር እያለን የተቸገርነው ለምንድን ነው? - ጠገናው ጎሹ

2 Comments

  1. weyanea meleya meleketun madreg yalebet NEB sayho XEJE be BRELEA be21 keflezemen endezih aynet DOMA amerar menoru betam yasaferal TAXBO CHEKA

  2. Muslemu ygedlachw sewoche yakatelchwe bet kerstaynoch gen aytyhem enatem ketelu egnem entbkalen keza blay ymettlut ke mengset sayhon kegna gare nwe

Comments are closed.

Share