(ሰበር ዜና) ቋሚ ሲኖዶሱ ፓትርያርኩ አስተዳደር ነክ ውሳኔዎችን ብቻቸውን እንዳይሰጡ የውሳኔ ሃሳብ አቀረበ

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎች በተቃውሞ ላይ(ዘ-ሐበሻ) ቋሚ ሲኖዶሱ ሳይሰበሰብ፣ የተማሪዎቹ ጥያቄ በአግባቡ ሳይመለስና ሳይጠና ከአቡነ ጢሞጢዎስ ጋር ባላቸው ጥብቅ ወዳጅነት የተነሳ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ እስከ መስከረም ድረስ እንዲዘጋ ፓትርያርኩ አቡነ ማቲያስ ወስነዋል በሚል ቋሚው ቅዱስ ሲኖዶስ ተቃውሞውን ማሰማቱን ለዘ-ሐበሻ የደረሰው መረጃ አመለከተ። ከአዲስ አበባ ለዘ-ሐበሻ ሾልከው የመጡት የቤተክህነት መረጃዎች እንዳመለከቱት የቋሚው ቅዱስ ሲኖዶስ አባላት አስቸኳይ ጉባኤ እንዲጠራ አድርገዋል።
ጉባኤው መቼ እንደሚደረግ የዘ-ሐበሻ የቤተክህነት ምንጮች ያልደረሱበት ቢሆኖም በቅርብ ቀናት ውስጥ እንደሚደረግ ግን ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። የቋሚ ቅዱስ ሲኖዶሱ አባላት ባወጡት የውሳኔ ሃሳብ መሰረት ፓትርያርኩ ቡራኬ ከመስጠት በቀርቭ አስተዳደራዊ የሆኑ ውሳኔዎችን ብቻቸውን እንዳይሰጡ ይከለክላል። ይህ አዲስ የውሳኔ ሃሳብ እንደሚለው ፓትርያርኩ አስተዳደራዊ ውሳኔዎችን ሲሰጡ በቅድሚያ ከቋሚው ቅዱስ ሲኖዶስ ጋር እንዲነጋገሩበትና በጋራ እንዲወሰን ያዛል። ይህ ፓትራይርኩ በአስተዳደራዊ ውሳኔዎች ላይ ስህተት እንዳይፈጽሙ ወይም የሚደርስባቸውን ወቀሳም ይቀንሳል በሚል የቀረበው የውሳኔ ሃሳብ በተጠራው ጉባኤ ላይ ከጸደቀ ሕግ ሆኖ እንደሚያገለግል የዘ-ሀበሻ የቤተክህነት ምንጮች አጋልጠዋል።
በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የተነሳው የተማሪዎች ተቃውሞ እስካሁን እልባት አላገኘም። ዘ-ሐበሻ አሁንም ጉዳዩን ተከታትላ መረጃውን ለሕዝብ ታደርሳለች።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ጠ/ሚ አብይ አህመድ በዛሬው እለት ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ መግለጫ ሰጡ
Share