Health: በኢስላም ማህፀንን ማከራየትና መከራየት እንዴት ይታያል? – ዳኢ መንሱር ሁሴን ይነግሩናል

ዳኢ መንሱር ሁሴን ስለ ማህፀን ማከራየት ከኢስላም አስተምህሮ አንፃር እንደሚከተለው አብራርተውልናል፡፡

ምስጋና ለአሏህ (ሱ.ወ) የተገባ ነው፡፡ ሶላትና ሰላም በአሏህ መልዕክተኛ በሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ) ላይ ይስፈን፡፡
ወደ ዋናው ርዕሳችን ከመግባታችን በፊት እንደ ኢስላም አስተምህሮ የሰው ልጆች የተፈጠሩባቸውን አራት መንገዶች እንመልከት፡፡

የመጀመሪያው መነሻችን የሆኑት የአባታችን አደም (ዐ.ሰ) አፈጣጠር ሲሆን፣ እርሳቸውም ያለ እናትና አባት በአሏኅ ችሎታና ጥበብ ከአፈር መፈጠራቸው ነው፡፡ በመቀጠልም እናታችን ህዋ ደግሞ ያለ ሴት ከአባታችን አደም ጎን ተፈጠሩ፡፡ በሶስተኛ የምናገኘው የነቢዩሏህ ዒሳ (ዐ.ሰ) ከእናት ብቻ ያለ አባት በአሏህ (ሱ.ወ) የ‹‹ሁን›› ቃል የተወለዱበት ተአምራዊ አፈጣጠር ነው፡፡ በመጨረሻ የምናገኘው ብዙሃኑ የአደም ልጆች ከእናትና አባት የተወለድን የምንራባበት መንገድ ነው፡፡
የሰው ልጆች ምድር ላይ የተገኘንባቸውን መንገዶች ካየን፣ በርዕሳችን ስላነሳነው ልጅ ምናልባትም ከሶስት ወላጆች እንዲገኝ ‹‹ሰለጠንኩ›› የምትለው ዓለም ስላመቻቸችው፣ ‹‹የማህፀን ኪራይ›› ኢስላም የሚለውን ትንሽ እንበላችሁ፡፡
እንደሚታወቀው ይህ ጉዳይ፣ በቀደሙት ጊዜያቶች የማይታወቅና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ተጀምሮ ዓለም ላይ እየተስፋፋ ያለ ነገር ነው፡፡ ከዚህ በፊት ስላልነበረ ቀደምት የኢስላም ምሁራን በጉዳዩ ላይ የተናገሩት ነገር የለም፡፡ በተጨማሪም ታዋቂ የሙስሊሙ ማህበረሰብ መሪዎች (የመዝሃብ ባለቤቶች) የነበሩ፣ ይህን ጉዳይ በኢስላም መፈቀዱን ወይም አለመፈቀዱን የዘገቡትም የተናገሩትም ነገር የለም፡፡

እዚህ ላይ ልብ ልንል የሚገባን ነገር ቢኖር፣ የሙስሊሙ የመዝሃብ መሪዎች ከቁርአን እና ከሐዲስ (የነብዩ ሙሐሙድ አስተምህሮ) ባገኙት ትንተና ሰጥተዋል፡፡ ይህ አይነቱ ትንታኔ ደግሞ ከቁርአን እና ከሐዲስ ቀጥሎ ሙስሊሙ ማህበረሰብ ዘንድ ትልቅ ቦታ አለው፡፡ ሕይወቱንም እዚያ ላይ ባገኘው ሕግ ነው የሚመራው፡፡
ለዚህም ነው ከላይ በጉዳዩ ላይ ከነርሱ የተገኘ ማብራሪያ አለ? ወይስ የለም የሚለውን ለማስቀመጥ የሞከርነው፡፡ እነሱ የሰጡት ትንታኔ የለም ማለት ግን ኢስላም ስለዚህ ጉዳይ የሚሰጠው ብያኔ የለም ማለት አይደለም፡፡ አሏህ (ሱ.ወ) ከቁርአኑ ላይ እንዲህ ብሏል፡-
‹‹በመጽሐፉ (በቁርአን) ውስጥ ምንም (ስለምንም) ነገር (ሳንገልፅ) አልተውንም›› (አል አንአም 38) በሌላ ምዕራፍ ላይም፣ ‹‹ዕውቀቱ ከሌላችሁ የዕውቀት ባለቤቶችን ጠይቁ›› (አል አንቢያእ 7)
ይህ ማለት፣ የትኛውም አዲስ ነገር ቢፈጠር የሚፈጠረው ነገር ጠቅለል ብሎ በተቀመጠው የአሏኅ (ሱ.ወ) ቃል (ቁርአን) እና የመልዕክተኛው ንግግር (ሐዲስ) ሕግ ስር በጊዜው በሚኖሩ ምሁሮች ጥልቅ እይታ እና ግንዛቤ በሚኖሩ ምሁሮች ጥልቅ እይታ እና ግንዛቤ መሰረት ተገቢ የሆነ ትንተና እና ብያኔ ይሰጥበታል፡፡ ከላይ እንደተጠቀሰው፣ ይህ ጉዳይ መጤ ከመሆኑም ጋር አንዳንድ ሰዎች ስለ ጉዳዩ ሰፊ ጥናት ሳያደርጉ፣ በደፈናው ችግር እንደሌለውና ለሰዎች ጥሩ የሕይወት መቀጠያ ዘዴ አድርገው ይገልፁታል፡፡ ነገር ግን ይህ አመለካከት እንደማያዋጣና ጉዳዩን ትኩረት ሰጥተን ልናየው እንደሚገባ በዚህ ጽሑፍ ለመጠቆም እንሞክራለን፡፡
ማህፀንን ስለማከራየትም ሆነ መከራየት አሁን ላይ ያሉ ሙስሊም ምሁራ የሰጡትን ትንታኔ እና ብያኔ ከማየታችን በፊት አላህ (ሱ.ወ) ስለ ሀፍረተ ገላችን ምን እንደተናገረ አጠር ባለ መልኩ እንመልከት፡፡
አንደኛ፡- ‹‹(አማኞች) እነዚያ ብልቶቻቸውን (ከሐራም) የሚጠብቁት…›› (አል ሙእሚኑን፤ 5-6)
ከአንቀፁ እንደምንረዳው፣ አላህ (ሱ.ወ) አንድ ወንድ በሸሪዓዊ መንገድ ከተፈቀደችለት ሴት ውጭ የሚያደርገውን የግብረ ሥጋ ግንኙነት እርም አድርጓል፡፡
ሁለተኛ፡- አሏህ (ሱ.ወ) የሰውን ልጆች ዘራቸውን እና ልጆቻቸውን እንዲጠብቁ አደራ ብሏል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ቃርያን የመመገብ የጤና ጥቅሞች በጥቂቱ (በዶ/ር ሆነሊያት ኤፍሬም)

ሀፍረተ ገላችንን እና ክብራችንን እንዴት መጠበቅ እንዳለብን በአጭሩ ይህን ካልን፣ ወደ ዋናው ርዕሰ ገዳይ ስንገባ ማህፀን ማከራየት ካለምንም የሐሳብ ልዩነት በኢስላም ክልክል (ሐራም) ነው ይሉናል- ሙስሊም በኢስላም ክልክል (ሐራም) ነው ይሉናል- ሙስሊም ምሁራኑ፡፡ ለዚህም የሚከተሉትን ምክንያቶች ያቀርባሉ፡፡

1. የሚወለደው ልጅ የእናት፣ የአባት ብሎም የዘር እውቅናን ሙሉ በሙሉ ይህ ነው ለማለት ብዥታ ውስጥ ይከተላል፡፡ ይህ ብዥታ በኪራይዋ እናት እና በዋናዋ እናት መካከል ወደ ፀብ ይወስዳል፡፡ የሚወለደው ልጅ ከሁለቱ እናቶች የአንዷ እንደሆነ እርግጠኛ ብንሆንም፣ በእርግጠኝነት የዚህች ነው ብሎ መወሰን ግን አንችልም፡፡ ከሳይንሱም ጋር ተያይዞ በዘርፉ ሰፊ ጥናት ያደረጉት ዶክተሮችና ፕሮፌሰሮች ስለ ችግሩ ብዙ የሚሉት ስላለ ያንን ፈልጎ መረዳት ከእኛ የሚጠበቅ ይሆናል፡፡ ስለዚህ እንደ ኢስላም ህብረተሰቡ ይህን እንዲርቀው ይመከራል፡፡

2. ይህን ጉዳይ ከወንዱ ፍትወት እንዲሁም ከሴቷ እንቁላል ለመውሰድ ሂደቱ የእሷንም የሱንም ሀፍረተ ገላ ማየት ይጠይቃል፡፡ በተጨማሪም የኪራይዋ እናት ሀፍረተ ገላን ማየት ግድ ይላል፡፡ ይህ ደግሞ ከላይ ከተጠቀሰው የኢስላም አስተምህሮ ጋር ይጋጫል፡፡ የሌላን ወገን ሀፍረተ ገላን ማየት ክልክል ስለሆነ (ባል የሚስትን ሚስት የባልን ሐፍረተ ገላ ማየት ሲቀር)

ይህን በተመለከተ አሏህ (ሱ.ወ) እንዲህ ይላል፡- ‹‹ለአማኝ ወንዶች እይታቸውን እንዲቆጣጠሩና ብልቶቻቸውንም እንዲጠብቁ ንገራቸው›› (አን ኑር 30)
ይህም አንዱ የሌላውን ሀፍረተ ገላ አይመልከት፡፡ ለዚያም እይታውን ወደ ታች ይመልስ፣ የራሱንም ሀፍረተ ገላ ይሸፍን ማለት ነው፡፡ ከፊል ሙስሊም ምሑራን በጣም ለከፋ ችግር ጥንቃቄ በተሞላበት መልኩ፣ (ሴት ከሆነች አባቷ፣ ባሏ፣ ለአቅመ አዳም የደረሰ ወንድሟ ወይም ልጇ ባሉበት) መታየት እንደሚቻል ብይን ይሰጣሉ፡፡
ይህ አይነቱ ጥንቃቄ ያስፈለገውም፣ ሰይጣን የሰው ልጆች ከአምላካቸው ጋር ያላቸውን ግንኙነት በማቋረጥ የራሱ ግብረ አበሮች እንዳያደርጋቸው በማሰብ ነው፡፡ ተቃራኒ ፆታዎች ከተፈጥሮ መሳሳቡ ጋር የሰይጣን ጉትጎታ ሲጨምር፣ ህገ ወጥ የሆኑ መነካካትና መተያየት ወደ ዝሙት እንዳያመራቸው ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  Health: መጥፎ የአፍ ጠረንን ለመካከል ወይም ለመቀነስ 5 ቀላል ዘዴዎች

3. የማህፀን ኪራይ የምዕራቡ ዓለም ‹‹ስልጣኔ›› የፈጠረው ግኝት ነው፡፡ በተለይ ከሃይማኖት ህግጋት አንፃር ስልጣኔቸው ደግሞ በከፊል ሰይጣኔ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ኢስላም ከሳይንስና ቴክኖሎጂ ጋር ሰፊ ግንኙነት ቢኖረውም ሰዎች ከተፈጠሩለት አሏህን የማምለክና ለትዕዛዙ እጅ የመስጠት አላማ ጋር የሚያጋጭን የሳይንስና ቴክኖሎጂ ውጤት አያስተናግድም፡፡

ጠቅለል ባለ መልኩ፣ በስልጣኔ ስም ሁሉንም መከተል ሳይሆን ጥሩና መጥፎ ጎጂና ጠቃሚውን ለይተን ልንጠቀምበት እንደሚገባ ኢስላም ያስተምራል፡፡
ኢስላም እንደ እምነት፣ ለስነ ምግባርና ባህሪ በጥቅሉ ለመልካም ማህበራዊ እሴቶች ትልቅ ዋጋ ይሰጣል፡፡ በተቃራኒው ምዕራቡ ዓለም ደግሞ ለዚህ ጉዳይ ትኩረት ሲሰጥ አይታይም ይላሉ ምሁራኑ፡፡ ስለ ማህፀን ኪራይ ክልክልነት ለማስረዳት ከተነሱት ምክንያቶች፣ ማህበረሰባዊ ቀውሶችን ስለሚያስከትል ሸሪዓዊ (ኢስላማዊ ሕግ) መነሻ የለውም የሚል ነው፡፡ ይልቁንም ማህፀን የሴቷ ሀፍረተ ገላ ስለሆነ ለሕጋዊ ባሏ እንጂ ህጋዊ ባሏ ያልሆነ ወንድ ፍትወት ተቀብላ ልታሳድግበት አይፈቀድላትም፤ ሸሪዓ አምርሮ ይቃወመዋል፡፡

እንደ ኢስላም አንድ ወንድ ያላገባትን ሴት ባይተዋር ለሆነ እርግዝና የመጠቀም መብት የለውም፡፡ በሌላ አገላለፅ አንዲት ሴት ማህፀኗን ላላገባት ወንድ ስታከራይ ሀፍረተ ገላዋን በጋብቻ ላልተሳሰራት ወንድ እየፈቀደች ነው፡፡ እርሷም ለእርሱ እርሱም ለእርሷ ስለማይፈቀዱ ሙሉ ዝሙት ይሆናል ባይባልም ተግባሩ ግን ሙሉ በሙሉ ሐራም ነው፡፡
የእርሱን ፍትወት በእርሷ ውስጥ እንዲያሳድግ ከማድረጉም በላይ፣ ፅንሱ የሚመገበውና የሚያድገው በማህፀን ውስጥ ስለሆነ በጎም ሆነ መጥፎ ተፅዕኖ የሚያርፍበት ከኪራይዋ እናቱ ነው፡፡ ስለሆነም ይህቺ ሴት የጎጂ ልማዶች (መቃም፣ ማጨስ፣ አልኮል መጠጣት ወዘተ…) ተጠቂ ብትሆን ፅንሱ ከጅምሩ ገና ለአደጋ ተጋላጭ ሊሆን ይችላል፡፡ በዚህ ሂደት ላይ ጽንሱን የሚከታተለው ዶክተር፣ ፅንሱ ላይ የአካል ጉዳት ይታያልና የወሊድ ጊዜሽ ከመድረሱ በፊት በቀዶ ጥገና ወጥቶ ጽንሱ መታከም አለበት ቢላት ፈቃደኛ ትሆናለች? የእኔ ለማትለው የሰው ልጅ ትክክለኛዋ እናቱ ብትሆን፣ ልታደርገው የምትችለውን የራሷን ሕይወት ቤዛ የማድረግ ጥያቄ ትቀበላለች?

እዚህ ላይ ሌላ ሳንጠቅስ የማናልፈው ሐሳብ ቢኖር፣ በሕጋዊ ባልና ሚስቶች መካከል በተፈጠረ አንዳች ውስጣዊ ችግር ምክንያት፣ ሚስቲቱ መፀነስ ካልቻለች በሕክምና ድጋፍ የባሏን ፍትወትና የራሷን እንቁላል ውጭ ላይ አሳድጎ ፅንሱን ወደ ራሷ ማህፀን አስገብተው ቢወልዱ የራሳቸው እስከሆነ ድረስ ችግር እንደሌለው ሙስሊም ምሑራን ይገልፃሉ፡፡
4. በእርግዝና ወቅት ያልተጠበቁ እንደ ስኳር፣ የደም ግፊት ያሉ ከባባድ ህመሞች የሚገጥሟቸው ሴቶች አሉ፡፡ እነኚህ በሽታዎች በአፋጣኝ ህክምና ካላገኙ የነፍሰ ጡሯን ህይወት ሊቀጥፉ ይችላሉ፡፡ በተጨማሪም ፅንሱን ለመጠበቅ (ለማዳን) ቀዶ ህክምና (ኦፕራሲዮን) የግድ ሊሆን ይችላል፡፡ ይሁን ኃላፊነትስ የሚወጣው ማን ነው? ይህቺው
የኪራይ እናት ወይስ የእንቁላሏ ባለቤት?

ተጨማሪ ያንብቡ:  Health: 10 የእንቅልፍ ፀሮችና መፍትሄያቸው

ከዚህ ሂደት ጋር ተያይዘው የተለያዩ እንግዳ ነገሮችም ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ እነዚህን የባህል፣ የስነ ልቦና እና ሌሎች ማህበራዊ ቀውሶች እንዴት ነው የምንፈታቸው? ኃላፊነቱን ለየትኛይቱ እናት እንስጣት?
ከዚህ በመነሳት አንድ ድምዳሜ ላይ እንደርሳለን፡፡ ይኸውም ፅሱ በዚያችው በእውነተኛ እናቱ ማህፀን አሏህ (ሱ.ወ) እንደፈቀደለት ይኑር፡፡ እናቱም ጽንሱን የመጠበቅና የመንከባከብና በአሏህ ፈቃድ ጊዜው ሲደርስም የመውለድ ሰብአዊ፣ ሃይማኖታዊና ህጋዊ ግዴታ ይኖርባታል፡፡
‹‹ማህጸን መከራየት ሞግዚት እንደመቅጠር ነው›› የሚሉ አንዳንድ ወገኖች አሉ፡፡ ፍየል ወዲያ… እንዲሉ፣ ይህ ጤነኛ አዕምሮ ሊቀበለው የማይችል ሐሳብ ነው፡፡ አንድን የተወለደ ልጅ ሞግዚት ብትንከባከበው፣ ጡቷን ብታጠባውና ብታሳድገው ልጁ በኪራይ ማህፀን እንደሚያድገው ፅንስ ያለ ተፅዕኖ አይገጥመውም፡፡ ከሞግዚቷ ጋር አለመግባባት ቢፈጠር ወይም በሆነ ምክንያት ጡት ማጥባት ብትከለክለው (ብታቆም)፣ ልጁ በቀላሉ ወደ ወላጅ እናቱ ተመልሶ አስፈላጊውን እንክብካቤ ማግኘት ይችላል፡፡ ህይወቱም ያለምንም እንከን መቀጠል ትችላለች፡፡

5. የማህፀን ኪራይ፣ በትዳር ህይወት ውስጥ በባልና ሚስት መካከል ሌላ ሶስተኛ ሰው ጣልቃ እንዲገባ ሁኔታዎችን ያመቻቻል፡፡ ባል ወደ ኪራይ እናት የሚሳብበት ክፍተት ይፈጠራል፡፡ ይኸው መጤ ፍልስፍና በምዕራቡ ዓለም ውስጥ ብዙ ቀውሶችን እያመጣ ይገኛል፡፡ አንድ ክስተት እንደ አብነት ብናነሳ፡፡ እንግሊዝ ሀገር ውስጥ ዋናዋ እናት ለኪራይዋ እናት ለመክፈል የተስማማችውን 20 ሺ ፓውንድ የማህፀን ኪራይ ጊዜው ደርሶ ልጇ ከተወለደላት በኋላ አልከፍልም በማለት ጭቅጭቅ አስነስታ ነበር፡፡ የኪራይዋ እናትም ‹‹ብሩን ካላመጣሽ ልጁ የእኔ ነው፣ እውቅና አልሰጥሽ›› ብላ ክስ እንደመሰረተችባት ተሰምቷል፡፡ ይህ ወረርሽኝ በእኛ ሀገር ደረጃ ደግሞ ከዚህ የከፋ ችግሮችን ይዞ እንደማይመጣ ምን ያህል እርግጠኞች ነን? ስለዚህ ልብ ያለው ልብ ይበል ነው ነገሩ፡፡

የወንድ ዘር (ስፐርም) ልገሳ

ስለማህፀን ኪራይ ካነሳን ዘንዳ፣ ጉዳዩ ተቀራራቢነት ስላለው የወንድ ዘር (ስፐርም) ልገሳን በተመለከተ ትንሽ ማለት ወደድን፡፡ እርስዎ እስካሁን ከሰሟቸው ልገሳዎች ‹‹የደም፣ የልብ፣ የኩላሊት፣ የዓይን ልገሳ ወዘተ…›› ባለፈ ወንዶች ፍትወታቸውን በመለገስ ላይ ናቸው፡፡ በዚህ ሂደት ደግሞ አንድ ‹‹ቸር›› የሆነ ወንድ፣ በዚህ ልገሳ ከተሰማራ ስለማንነታቸውና ስለዚህች ምድር ዕጣ ፈንታቸው የማይጨነቅላቸውን ጭራሹንም የማያውቃቸውን የትየለሌ ልጆች ሊያፈራ እንደሚችል መገመት አያዳግትም፡፡
ይህ የማስተዋል አቅሙ ላልከዳው ሰው፣ እጅግ ከባድና ዘግናኝ በመሆኑ ለመስማት እንኳን የሚከብድ ጉዳይ ነው፡፡ ኢስላም በተለይ ወንድ እንደ አባት ለልጆቹ፣ የምድራዊም ሆነ ሰማያዊ ዓለም ሁለንተናዊ ዕጣ ፈንታቸው የሚበጃቸውን የማመላከት፣ የመንከባከብና መሰል ኃላፊነቶች አስረክቦታል፡፡ ወንዱ የአባትነት ሚናውን ለማይወጣበት ይህ አይነት የዘር (ስፐርም) ልገሳ ክልክል ነው፡፡

Share