“ ድንጋይ ቢቆሉት አይሆንም ቆሎ ”

ይድነቃቸው ከበደ

(ይድነቃቸው)

ሉቃ ም.14ከቁ.15-24 “በእግዚአብሔርመንግስት እንጀራ የሚበላ ብፁዕ ነው አለው፡፡እርሱም ግን አንድ ሰው ታለቅ እራት አዘጋጅቶ ብዙዎችን ጠራ፡፡በእራትም ሰዓት አሁን ተዘጋጅቷልና ኑ እንዲላቸው ባሪያውን ላከ ሁላቸውም በአንድነት ያማካኙ ጀመር ይላል፡፡” የሚገርመው የነዚህ ሰዎች ምክንያት ተራና የውሸት ምክንያት መሆኑ ነው “ ፊተኛው መሬት ገዝቻለው ወጥቼ ላየው በግድ ያስፈልገኛል” አለ፡፡ሰው መሬትን መርምሮ የሚያየው ከመግዛቱ በፊት እንጂ ከገዛ በኋላ ነው ? ሁለተኛውም “አምስት ጥማድ በሬዎችን ገዝቼአለው ልፈትናቸው እሄዳለሁ”አለ፡፡በሬን የሚገዛ ሰው በሬውን የሚፈትነው ቀንበር መሸከም መቻሉን አለመቻሉን አይቶ ማረጋገጥ ያለበት ከመግዛቱ በፊት ነው ወይስ በኋላ? በተጠቀሰው መጽሐፍ ቅዱስ ምዕራፍ ላይ ታሪኩ በሰፊ ይገኛል፡፡ ምክንያተኛ ሰው ሌላው ቀርቶ እግዚአብሔር ሲጠራው ይቸገራል፡፡

ምክንያት ለሰው ልጅ ለየትኛውም እንቅስቃሴ አስፈላጊ ከመሆኑም ባሻገር ተፈላጊም ጭምር ነው፡፡ምክንያት አያስፈልግም ከሚል መደምደሚያ የሚያደርስ የማናቸውም ሰው ክርክር ዉሃ የማይቋጥር ጉንጭ አልፋ ሙግትነው፡፡ለማድረግ ወይም ላለማድረግ የቀረበው አመክንዮ ተገቢ ነው ወይስ አይደለም? ለማለት ምክንያታዊ አስተሳሰብን መሠረት በማድረግ መሞገት፣ ተመራጭ አሳብን ለማቅርበ እድል ይሰጣል፡፡

በመሆኑም የተለያዩ ምክንያቶችን በማቅረብ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ውህደት፣ቅንጅት እና ትብብር በተጠና መልኩ ከተከናወነ ውጤት አለው ተብሎ እንደሚነገረው ሁሉ እራስን ከማታለል እና ድክመትን በሌላው ከመሸፈን ያለፈ ፋይዳ አይኖረውም የሚልአቋም እንዳለም የሚታወቅ ሃቅ ነው፡፡የየትኛውም ወገን ክርክር “ለሃገር የቱ ይጠቅማል?” ከሆነ ፣ምክንያቱ እጅግ በጣም ጠቃሚ ነው ብሎ ለመቀበል አዳጋች አይሆንም፡፡ ነገር ግን ክርክሩ ከነምክንያቱ “ለፓርቲዬ የቱ ይጠቅማል ከሆነ?” ችግሩ የሚጀምረው ከዚህ ነው፡፡ እንዲህ አይነቱ ክርክር ምክንያት አልባ ከመሆኑ ባለፈ የስብህና ዝቅጠትም ይሆናል ፡፡የዚህ ጹሑፍ ዋና ዓላማ እነዚህን ሁለት ምክንያቶችን መነሻ በማድረግ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ውህደት፣ቅንጅት እና ትብብር በመጠኑ ለመዳሰስ ነው፡፡

ምርጫ 97 በኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ስርአት ውስጥ የሩሱን አዎንታዊ እና አሉታዊ አሻራዎች ጥሎ ያለፈ የ10 ዓመት የቅርብ ጊዜ ትውስታችን ነው፡፡በወቅቱ የአራት ፓርቲዎች ስብጥር የፈጠረው ቅንጅ ለጠላትም ለወዳጅም የሁሉ ጊዜ የቤት ስራሰጥቶ ያለፈ ነው፡፡ይህን ለማለት የሚያስደፍረው ከምርጫ 97 በኋላ እስከ ምርጫ 2002 አዲስ የተቋቋሙት እንዲሁም ነባሮቹ አካሄዳቸው አንዱ ሌላውን በሴራ ፖለቲካ ውጦ ከማስቀረት የዘለለ አደባባይ ተይዞ የተወጣ አንዳችም ቁሙ ነገር አልታየም፡፡ህረተሰብም በምርጫ ሰበብ ከደረሰበት የልብ ስብራት አገግሞ ስለ አገር እና ፖለቲካ ለማሰብ እና ለመተግበር የነበረው ዝጉጁነት እጅግ በጣም አናሳ የነበረበት ወቅት ነው፡፡በአንጻሩ ገዥው ኢሕአዴግ (የወያኔ) መንግስት በሁሉ መልኩ ራሱን በይበልጥ በአምባገነናዊ ስርአት በማደራጀት በእኩይ ተግባሩ የተጠመደበት የሞት ሽርተ ትግል ለማድረግ ተጠቅሞበታል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኦሕዴድ መንታ መንገድ - አገሬ አዲስ

ምርጫ2002 እንደ ምርጫ 97 በፖለቲካ ይዘቱም ሆነ ዓይነቱ ፍፁም የተለየ ለይምሰል የተደረገ አገር አቀፍ የምርጫ ሠሌዳ መረሀ-ግብር ለመሸፈን የተካሄደ ምርጫ ነው፡፡ይህ ምርጫ ውጤት እንደማይኖረው ከበቂ ምክንያት ጋር በማስደገፍ ምርጫው ከመካሄዱ በፊት ይሞግቱ የነበሩ ሰዎች ስለመኖራቸው ስንቶቻችን እናስታውስ ይሆን ? ፡፡ በተለይ አንድነት ፓርቲ የመርህ እና የህግ ጥሰት በመፈፀሙ ከፓርቲው አባላት ከግማሽ በላይ የሚሆነው በፕ/ር መስፍን ወልደ ማርያም ይመራ የነበረው “የመርህ ይከበር” ስብስብ ምርጫ 2002 ፓርቲዎች በተለይ አንድነት ወደ ምርጫው ከመግባቱ በፊት ሊያጤናቸው የሚገባ ነጥቦች እንዳሉ በማስገንዘብ በውይይት ለመርታት ሙከራ አድርጓል፡፡በወቅቱ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የሂደቱን ክሽፈት ለማፋጠን የያኔው አንድነት ፓርቲየአንበሳውን ድርሻ በፍቃደኝነት ወስዷአል፡፡

በወቅቱ ምርጫው ከመካሄዱ በፊት ውጤቱ የተተነበየለት ምርጫ 2002 ኢሕአዴግ (ወያኔ) ይህ ቀረ የማይባል የአፈና ሃይሉን ተጠቅሞ የፓርላማ መቀመጫ ጠቅልሎ በማግኘት ሲንፏለልበት ለማየት ግድ ሆኗአል፡፡ በምርጫ 2002 እድሜቻው ለመምረጥ ከደረሱ ኢትዮጵያዊያን መካከል 33%ኢሕአዴግ(ወያኔን) የመርጡ ሲሆን ፡፡የእያንዳንዱ ተቃዋሚ ፓርቲ ማለትም አንድነት፣መኢአድ፣ኢዴፓ እና ሌሎችም በምርጫው የተሳተፉ በድምሩ ያገኙት ድምፅ 15% ነው፡፡ በአጠቃላይ 48 % የሚሆኑት በምርጫው በመሳተፍ ለሚፈልጉት ፓርቲ ድምፅ የሰጠ ናቸው፡፡ነጉሩን ይበልጥ አስገራሚ የሚያደርገው የተቀሩት 52% የሚሆኑት ድምፃቸውን ለማንም አልሰጡም፡፡ በሌላ አገላለፅ በምርጫው ከተሳተፈው ይልቅ ያልተሳተፈው ይበልጣል ማለት ነው፡፡ይህ ደግሞ በገዥው መንግስት እንዲሁም በተቃዋሚዎች 52% የሚሆኑ መራጮች ተስፋም እምነትም አልነበራቸውም ማለት ነው፡፡ ይህ ሒሳባዊ ቀመር ከመርጫ ቦርድ የተገኘ መረጃ ሲሆንመረጃውየቁጥር ልዩነት አለው ቢባል እንኳን መሰረታዊ ሃቁን የሚያስቀይር አይደለም፡፡ በመሆኑም መረጃውን መሠረት በማድረግ እንዲሁም የወቅቱን ነባራዊ ሁኔታከግምት በማስገባት ምርጫ 2002 ቅድመ ምርጫ ፣የምርጫ ወቅት እና ከምርጫ በኋለ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ፣የገዥው መንግስ እንዲሁም የህብረተሰብ ተሳትፎ በተለይ የነጻ ሚዲያ አስታዎጾ በጥቅል እና በተናጥል በመመልከት ምርጫው “ቅርጫ” ስለመሆኑ ማመላከቻ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሚኒሶታ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤ/ክ ለሰላምና ለአንድነት ከቆሙ ምእመናንን የተላለፈ ማብራሪያ

ከላይ በስሱ ለማየት የተመከረው ሁለት አገር-አቀፍ ምርጫ ከፊት ለፊት እየጠበቅን ላለው ምርጫ 2007 ለተቃዋሚ ፓርቲዎች በገዥው መንግሰት የፖለቲካ ንድፈ-ሃሳብ ሠነድ እንዳለ የሚነግረን ነገር ይኖረዋል፡፡ይህን መነሻ በማድረግ በመጪው ምርጫ 2007 የገዥው መንግስት ባሪያ የሆኑትን በስመ ተቃዋሚ ተመዝግበው ከአሳዳሪያቸው ቀለብ የሚሰፈርላቸውን ወደ ጎን በመተው ፡፡ እውነተኛ ተቃዋሚ ነን የሚሉየኢሕአዴግ (ወያኔ) ንቅዘትና በዘር ከፋፍለህ ግዛው ፖሊስ የሚቃወሙ እንዲሁም ዴሞክራሳዊት ኢትዮጵያ ለመገንባት ቁርጠኝነቱ አለን የሚሉ ፓርቲዎች ወሣኝ ትግል ሊደረግበት የሚገባውወቅት ነው፡፡

ይህን ትግል በተልካሻ ምክንያት ውጤት አልባ እንዳይሆን የፖለቲካ ሊቃን ብቻ ሳይሆን ስለ አገሪ ጉዳይ ያገባኛል የሚሉ ሁሉ ሊመክሩበት፣ውሳኔ ሊሰጡበት እና ተግባራዊ ሊያደርጉት የሚገባ ታላቅ ስራ ነው፡፡በተለይ የዓላማ አንድነት ያላቸው የተቃዋሚ ፓርቲዎች በመጪው 2007 አገር-አቀፍ ምርጫ የሞት ሽረት ሠላማዊ ትግል የሚያደርጎበት ነው፡፡ በእርግጠኝነት ከወዲኹ መገመት እንደሚቻለው ምርጫ 2007 በአገራች እየታየ ያለው ሰላማዊ ትግል ተስፋ ሰጪ የሚሆንበት ወይም ተስፋ የሚጨልምበት ታሪካዊ ወቀት ነው፡፡ታሪክ መስራት ደግሞበተቃዋሚ ፓርቲዎች እጅ የሚወድቅ ሃላፊነት ነው! ይህ አገራዊ ሃላፊነት ከቂም እና ከጥላቻ ፣ከተሳሳተ ሂሣባዊ ቀመር፣ከአገር በላይ ለፓርቲ ማድላትእንዲሁም ከእራስ ወዳድነትና ከስልጣን ጥማትእራስን በመግታት ትውልድ ተሻጋሪ የሆነ ታሪክ በመስራት የአገራችን ዕጣ ፈንታ የሚወሰንበት የምርጫ መጨረሻ መጀመሪያ ነው፡፡ በአርግጥ ይህ ሃላፊነት የፓርቲዎች ብቻ ሣይሆን ለውጥ ፈላጊ የሆነ የማንኛውም ኢትዮጵያዊ ሃላፊነት ጭምር ነው፡፡

የዚህ ጽሑፍ ዋና ማጠንጠኛ እውነተኛ ተቃዋሚዎች እና የዓላማ አንድነት ባላቸው ፓርቲዎች መካከል ሊተባበሩ ወይም ሊቀናጁ ከተቻለ ውህደት ሊፈጥሩ እንደሚገባ ለማመላከት ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ አንድነት እና መኢአድ ቅድመ ውህደት መፈፀማቸው እጅግ በጣም አስደሳች ከመሆኑ ባለፍ ለሌሎችም ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ከፈፀሙትም ቅድመ ውህደት ወደዋናው ውህደት የሚያደርጉት ጉዞ የተሳካ እንዲሆን ከመመኘት ባለፈ ለውህደቱ አስታዎፆኦ ሊያበረክት የሚችል ማናቸውም ነገሮች መተግበር ጥቅም እንጂ ጉዳት የለውም፡፡ሰማያዊ ፓርቲ በባለፈው ሳምንታት የብሔራዊ ምክር ቤት ስብሰባ ጥልቀት ያለው ውይይት በማካሄድ ፓርቲው ከመቼው ጊዚ በላይ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር በትብብር ለመሥራት መዘጋጀቱ መግለጹ ይበል የሚያስብል መልካም ጅማሮ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሰላም ትግሉ በኢትዮጵያ (ክፍል ፩) - አንዱዓለም ተፈራ

በመሆኑም እውነተኛ ተቃዋሚ ፓርቲ ነን የሚሉና በህብረተሰብ ተቀባይነት ያላቸው ፓርቲዎች በሙሉ፤ ደግመው ደጋግመው እልህ አስጨራሽ ሂደቱን ተከትለው ሊተባበሩ ወይም ሊቀናጁ ከተቻለ ውህደት ሊፈጥሩ ይገባቸዋል፡፡ይህን የሚያደርጉት ተባባሩ ወይም ተሰባበሩ የሚባለውን ለመሸሽ ወይም ለመጋፈጥ ሳይሆን እያንዳንዱ የፖለቲካ ፓርቲ በጥልቀት እራሱን በመፈተሸ ጠንካራና ደካማ ጎኑን በመለየት ከሚዲያ ፍጆታ ባለፈ መሬት የያዝ ስራ ምን ሰራው ?ምንስ ይቀረኛል ?በማለት ጉድለተ የሚሞላበት ስኬት ለሌላው የሚያስተላልፉበት የትብብር፣የቅንጅት እና የውህደት ጊዜው አሁን ነው!!! የማይካድ ሃቅ ቢኖር የፓርቲዎች ትብብር፣ ቅንጅት እና ውህደት መካከል አጋፋሪዎች መኖራቸው ነው፡፡እነዚህን በጥንቃቄ በመለየት እና በማስረዳት ካልተቻለም በመነጠል አሸናፊ ለመሆን ትጋትን የሚጠይቅ የጎን ለጎን ስራ ያስፈልጋል፡፡በይበልጥ ደግሞ ትብብር፣ቅንጅት እና ውህደት ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ለዚህ ጽሑፍ በመግቢያነት የተጠቀሰው ዓይነት ወንዝ የማያሻግርተልካሻ ምክንያቶችን በመደርደር ለሰላማዊ ትግሉ እንቅፋት ላለመሆን እራስን መጠበቅ የተሻለ ነው፡፡

በመጨረሻም የዚህ ጽሑፍ ማጠቃለያ የሚሆነውበባለፈው ምርጫ 2002 ክስተትን በማስታወስ ነው፡፡ እሱም ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ በተወዳደሩበት አካባቢ 2ኛ ሆነው ነው የተሸነፉት 1ኛ የወጣው የወያኔ ተላላኪ የበለጣቸው 130 ድምፅ ነው፡፡በዚያው አካባቢ መኢአድ ወክለው የተወዳደረው ከ400 በላይ ድምፅ አግኘተው ነበር፡፡ከዚህ የበለጥ ስለትብብር፣ቅንጅት እና ውህደት ምን ጥሩ ማሳያ ይኖራል በማለት መደምደም ባይቻልም እንደግባት ለመጠቀም ግን የተሻለ ነው፡፡በመሆኑም እነዚህን እና መስል ሃቆችን ግምት ውስጥ በማስገባት የተቃዋሚ ፓርቲዎች ጉዞ  “ ድንጋይ ቢቆሉት አይሆንም ቆሎ ” ከመባል እና ተተፍቶ ከመጣል እራስን ማዳን ምንኛ መታደል ነው፡፡

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!

1 Comment

Comments are closed.

Share