ካሁን ቀደም በነፃ ከተለቀቁት ሙስሊሞች ውስጥ 2ቱ እንደገና እንዲከላከሉ ተወሰነ

“ትናንት በተካሄደ ሌላ ችሎት ካሁን ቀደም በነጻ ከተለቀቁት ሙስሊሞች ሁለቱ እንዲከላከሉ ተወስኖባቸዋል” ሲል ድምጻችን ይሰማ ዘገበ።

እንደ ድምጻችን ይሰማ ዘገባ ከሆነ ከትናንት የቀጠለው ችሎት ዛሬ ማክሰኞም ምስክሮችን መስማቱን ቀጥሏል፡፡ በትናንትናው እለት በጠዋቱና በከሰአቱ ችሎት ተማሪ አቡበከር መሀመድ ምስክርነቱን መስጠቱ ይታወሳል፡፡ በአወሊያ ተቃውሞ አነሳስ ዙሪያም የነበረውን ነገር ቀድመውት እንደነበሩት መስካሪዎች በትክክል አስቀምጧል፡፡ በተለይም ተማሪዎች ገና ተቃውሟቸውን ማሰማት ሲጀምሩ መጅሊስ ቢሮ ጠርተው ያነጋገሯቸው አቶ አህመዲን አብዱላሂ ጨሎ ግድ የለሽነታቸውን ሲገልጹ ‹‹እንኳን እናንተ ይቅርና አዲስ አበባ ህዝብ በሙሉ ጨርቁን ጥሎ ቢያብድ ግድ አይሰጠንም›› ማለታቸውና 3 አመት ተምረው ሊመረቁ 3 ወር የቀራቸውን ተማሪዎች ከማባረር እስኪመረቁ እንዲጠብቁ ሲለምኗቸው ‹‹እንኳን 3 ወር ቀርቶ 1 ቀን እንኳ ቢቀራችሁ አትመረቁም›› ብለው መመለሳቸው ለሰሚው ሁሉ የሚያሳዝን ሆኖ ነበር፡፡

ተማሪዎች የተቃወሙት በወቅቱ የነበረውን የአህባሽን አስተሳሰብ አስገድዶ የመጫን እርምጃ መሆኑን በዝርዝር የገለጸው ተማሪ አቡበከር አቶ አህመዲን በግልጽ ‹‹የእኛን አስተሳሰብ አህባሽን ካልተቀበላችሁ አብረን አንቀጥልም›› ብለው በዚሁ ስብሰባ ላይ ቁርጡን እንደነገሯቸው አስረድቷል፡፡ የካሪኩለሙ መቀየር ዓላማም ይኸው የአህባሽ አስተሳሰብ ጠመቃ መሆኑን የተረዱትም በዚህ ምክንያት መሆኑን ገልጿል፡፡ በተለይም ተማሪው ለጥያቄው መልስ በሚፈልግበት እና ቁጣውን በሚገልጽበት ወቅት የመጅሊሱ ጸሀፊ አቶ አልሙሀመድ ሲራጅ ‹‹እናንተ ምንም አያገባችሁም! ምንም አታመጡም! አርፋችሁ ተቀመጡ!›› ማለታቸውና ተማሪዎች ላይ አብረዋቸው ከመጡት አቶ ተስፋዬ ዲንቃ ጋር ማፌዛቸው ተቃውሞውን ማቀጣጠሉን ተናግሯል፡፡ ተማሪ አቡበከር ከሰዓት በዋለው ችሎትም ከዓቃቤ ህግ ለቀረቡለት መስቀለኛ ጥያቄዎች በጥሩ ሁኔታ መልስ ሰጥቷል፡፡

በተያያዘ ዜና በታህሳስ 23 በነጻ እንዲለቀቁ ከተወሰነላቸው 10 ሙስሊሞች መካከል አራቱ ላይ በአቃቤ ህግ የቀረበው ይግባኝ ተቀባይነት አግኝቶ ሁለቱ ላይ ‹‹ይከላከሉ›› የሚል ብይን ተሰጥቷል፡፡ ነጻ ተብለው ከተፈቱ በኋላም ፍርድ ቤት ሲያመላልሳቸው ከከረመ በኋላ የይከላከሉ ብይን የሰጠባቸው ሁለት የቀድሞ ታሳሪዎች ወንድም አሊ መኪ እና ሐጂ ዐብዱረህማን ዩሱፍ ሲሆኑ ከቀሪዎቹ ታሳሪዎቻችን በተለየ ችሎት ጉዳያቸው ሊታይ እንደሚችልም ተገምቷል ሲል ድምጻችን ይሰማ ዘገባውን ቋጭቷል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በቼክ ሪፐብሊክ በተደረገ የማራቶን ውድድር ድል ቀናቸው
Share