የፕሪሚየር ሊግ ክለቦች የገቢ እድገት እየቀነሰ ነው

የቴክኖሎጂ ዕድገት የፕሪሚየር ሊጉ ፈተና ሆኗል
– የፕሪሚየር ሊጉ 2 ቢሊዮን ፓውንድ አስገብቷል

ከሳምንታት በፊት ዴሎይቴ የአውሮፓ ክለቦችን የገቢ ደረጃ ይፋ አድርጓል፡፡ እንደተለመደው ከ20ዎቹ ክለቦች የሰባቱን ቦታ ፕሪሚየር ሊግ ወስዶታል፡፡ መሪዎቹ ግን የታወቁት ስፔን ሀያላን ናቸው- ሪያል ማድሪድ እና ባርሴሎና፡፡ በደረጃ ሰንጠረዡ ቀድሞ ከሚታወቁት ማንቸስተር ዩናይትድ፣ አርሰናል፣ ቼልሲ፣ ሊቨርፑል፣ ማንቸስተር ሲቲ እና ቶተንሃም በተጨማሪ አስቶን ቪላም በእንግድነት ተቀላቅሏል፡፡ በክለቦች ድምር ገቢ ሲወዳደር ፕሪሚየር ሊጉ 2 ቢሊዮን ፓውንድ፣ ቡንደስሊጋው 1.4 ቢሊዮን ፓውንድ እና ላሊጋው እንዲሁም ሴሪአ በተመሳሳይ 1.3 ቢሊዮን ፓውንድ አስመዘግበዋል፡፡ ሆኖም በንፁህ ትርፍ ሲለካ ቡንደስሊጋው የበላይ ነው፡፡ ዴሎይቴ ባለሙያዎች የ2010-11 ግምታቸውን ሲያስቀምጡ ዘንድሮ የሚፈረመው የፕሪሚየር ሊግ ቴሌቪዝን መብት አጠቃላይ ገቢውን 2.2 ቢሊዮን ፓውንድ ያደርስለታል፡፡ የዚህን ገቢ 60 በመቶ የሚቋደሱት ደግሞ ስድስት ክለቦች (ዩናይትድ፣ አርሰናል፣ ቼልሲ፣ ሊርፑል፣ ማንቸስተር ሲቲ እና ቶተንሃም) ናቸው፡፡
በ2009-2010 የተጠቀሱት ስድስት ክለቦች ገቢ በ5 በመቶ አድጎላቸዋል፡፡ ይህ መልካም ቢሆንም ከ56 ሚሊዮን ፓውንድ ውስጥ 2/3ኛው ገቢ የተገኘው በአንድ ክለብ መሆኑ ያስገርማል፡፡ ማንቸስተር ሲቲ ከመካከለኛው ምስራቅ የንግድ አጋሮቹ ጋር የፈጠረው ግንኙነት ገቢውን በእጅጉ አሳድጎታል፡፡ ከዚህ አንፃር የሊጉ አራት ሀያላን ገቢያቸው ብዙም እንዳላደገ መናገር ይቻላል፡፡ ከ2004 ጀምሮ የክለቦቹ ገቢ በ77 በመቶ (500 ሚሊዮን ፓውንድ ቢጨምርም ባለፉት ሶስት ዓመታት ተመሳሳይ እድገት አላሳየም፡፡ ይሁን እንጂ የቴሌቪዥን ገቢ የሊጉ ዋነኛ የገቢ ምንጭ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ ሆኖም የጨዋታ ዕለት ገቢ፣ የቴሌቪዥን ገቢ እና የኮሜርሺያል ገቢዎችን ማነፃፀር እንችላለን፡፡
የጨዋታ ዕለት ገቢ
በዚህ የገቢ ምንጭ ክለቦች የሚያገኙት ገንዘብ በቲኬት ዋጋ፣ በሜዳቸው በሚያደርጉት ጨዋታ ብዛት፣ በተመልካች ብዛት፣ ከፍተኛ ዋጋ በሚከፍሉ ተመልካቾች ስብጥር እና ወደ አዲስ ስታዲየም ከመዛወር እድላቸው ጋር ይያያዛል፡፡ ማንቸስተር ዩናይትድ እና አርሰናል ከጨዋታ ዕለት ገቢ በተናጥል በዓመት እስከ 100 ሚሊዮን ፓውንድ ያገኛሉ፡፡ አምና ግን የስድስቱ የእንግሊዝ ክለቦች የጨዋታ ዕለት ገቢ ቀንሷል፡፡ የቀነሰበትን መጠን ስንመለከት ቼልሲ 10 በመቶ፣ ማንቸስተር ዩናይትድ 8 በመቶ፣ ቶተንሃም 7 በመቶ እና አርሰናል 6 በመቶ የጨዋታ ዕለት ገቢያቸው ወርዷል፡፡ ሊቨርፑል ከሌሎቹ በተለየ ገቢውን አስጠብቆ ዘልቋል፡፡ የጨዋታ ዕለት ገቢ ከ2007 አንስቶ ሲጨምር አለመታየቱ የአሁኑን መቀነስ አስገራሚ እንዳይሆን ያደርገዋል፡፡ ክለቦች ይህንን የተለየ ገቢ ለማሳደግ የቲኬት ዋጋ መጨመር፣ በሜዳ በርካታ ጨዋታ ማድረግ፣ የደጋፊን ቁጥር ማሳደግ፣ የተመልካቾችን (የከፍተኛ ክፍያ) ስብጥር ከፍ ማድረግ እና ስታዲየም መገንባት እንደ አማራጭ ሊታዩ ይችላል፡፡ ሆኖም የተጠቀሱት አማራጮች ሁሉ የራሳቸው የሆነ ፈተና ያለባቸው እና ለመተግበር የሚያስቸግሩ ናቸው፡፡ የቲኬት ዋጋ ጭማሪ ከወዲሁ አብዛኛውን ደጋፊ ምሬት ውስጥ አስገብቷል፡፡ በሜዳ በርካታ ጨዋታ ለማድረግ ቡድኑ በሁሉም ውድድሮች ረጅም ርቀት ሊያደርግ ይገባል፡፡ አዲስ ስታዲየም ማስገንባትም እጅግ ከባድ ስራ ነው፡፡ ስለዚህ የክለቦች የጨዋታ ዕለት ገቢ ከዚህ በላይ እንደሚጨምር መጠበቅ ያስቸግራል፡፡
ቴሌቪዥን
የእንግሊዝ እግር ኳስ የቴሌቪዥን ገቢ አዲስ መብቶች በተፈረሙ ቁጥር ሲያድግ ቆይቷል፡፡ ለመጨረሻ ጊዜ በተፈረመው የ2008 የሶስት ዓመት ውል ገቢው 45 በመቶ ዕድገት አሳይቶ ነበር፡፡ የዘንድሮውም አዲስ የቴሌቪዥን ውል ገቢውን እንደሚያሳድገው ይታመናል፡፡ ሆኖም ይህ የገቢ እድገት በዚህ ላይቀጥል እንደሚችል የሚጠራጠሩ እየበረከቱ መጥተዋል፡፡ ለምሳሌ የሀገር ውስጥ የቴሌቪዥን መብት (የቀጥታ ጨዋታ ስርጭት እና ሀይላይት) ግዢ ገቢ ዕድገቱ የመጨረሻው ላይ የደረሰ መስሏል፡፡ ሆኖም የውጪ ሀገር ስርጭት መብት ክፍያ እያደገ ነው፡፡ ለምሳሌ በሩቅ ምስራቅ እና ሰሜን አፍሪካ የስርጭት መብት የገዛው አቡዳቢ ስፖርትስ ለመብቱ ክፍያ 200 ሚሊዮን ፓውንድ አውጥቷል፡፡ ይህ ከዚህ ቀደም ሾውታይም አረቢያ ከከፈለው 80 ሚሊዮን ፓውንድ ወደ ሶስት እጥፍ የቀረበ ነው፡፡ በሌሎች የዓለማችን ክፍሎች መብቱን የተሸጠበት ዋጋም አስገራሚ ዕድገት ማሳየት ቀጥሏል፡፡
ሆኖም የፍላጎቱ እና የክፍያውን መጨመር ያህል ተያይዘው የሚነሱ ሁለት ችግሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ የእስያ አካባቢ ተመልካቾች እንዲመቻቸው ሲባል በእንግሊዝ ምሳ ሰዓት የሚጀምሩ ጨዋታዎች ይበዛሉ፡፡ ሌላኛው ስጋት የውጪ ሀገራቱ የስርጭት ገበያ እንደ ሀገር ውስጡ የመጨረሻ ዕድገቱ ላይ እንዳይደርስ ነው፡፡ እንዲህም ሆኖ የፕሪሚየር ሊግ የቴሌቪዥን መብት ከሌሎቹ ሊጎች በእጅጉ የላቀ ነው፡፡ በየዓመቱ የሚመዘግበው 1.1 ቢሊዮን ፓውንድ ከሴሪ አ (760 ሚሊዮን ፓውንድ)፣ የፈረንሳይ ሊግ (560 ሚሊዮን ፓውንድ) ላ ሊጋ (500 ሚሊዮን ፓውንድ) እና ቡንደስሊጋው (340 ሚሊዮን ፓውንድ) እጅግ ይበልጣል፡፡ የሊጎቹ ዋነኛ ልዩነት የውጪ ሀገራት የቴሌቪዥን መብት ሽያጫቸው ነው፡፡ በዚህ ረገድ ፕሪሚየር ሊጉ በዓመት 480 ሚሊዮን ፓውንድ ሲያጋብስ ላ ሊጋ 130 ሚሊዮን ፓውንድ እና ቡንደስሊጋ 35 ሚሊዮን ፓውንድ ያገኛሉ፡፡
የፕሪሚየር ሊጉ የቴሌቪዥን መብት ዋጋ ክፍፍል ከሌሎቹ ሊጎች አንፃር ፍትሃዊ ነው፡፡ ለምሳሌ በ2009/10 ማንቸስተር ዩናይትድ 53 ሚሊዮን ፓውንድ በማግኘት ከፍተኛውን ድርሻ ሲወስድ በሊጉ የመጨረሻ ደረጃ ይዞ የጨረሰው ፖርትስመዝ 32 ሚሊዮን ፓውንድ ደርሶታል፡፡ ይህ ልዩነት ከክለቦቹ የደረጃ ርቀት አንፃር ብዙ የሚባል አይደለም፡፡ በአንፃሩ በላሊጋው ባርሴሎና እና ሪያል ማድሪድ በተናጥል 117 ሚሊዮን ፓውንድ ሲሰበስቡ የመጨረሻው ክለብ 10 ሚሊዮን ፓውንድ ብቻ ደርሶታል፡፡ ፕሪሚየር ሊግ ከሌሎቹ ሊጎች ከፍተኛ የቴሌቪዥን ገቢ የማግኘቱ ምስጢር የውጪ ሀገሮች ስርጭት መብት ገቢው ነው፡፡ ይህ ደግሞ አደጋው ብዙ ነው፡፡ ለምሳሌ የፕሪሚየር ሊጉ ከዋክብት ተጨዋቾች ወደ ላሊጋው ወይም ሌሎች ሊጎች ቢጓዙ በውጪ ሀገራት የሚገኙ ተመልካቾች ፍላጎታቸው ሊቀየር ይችላል፡፡ ሌላኛው የፕሪሚየር ሊግ ስጋት የስርጭት ቴክኖሎጂ ለውጥ ነው፡፡ በኢንተርኔት ጨዋታዎችን ህጋዊ ባልሆነ መንገድ በቀጥታ የሚያስተላልፉ አካላት እየበረከቱ ነው፡፡ እነዚህን ህገወጥ በህግ የማስቀጣቱ ሂደት ቀላል ስራ አይደለም፡፡ የቪዲዮ ቴክኖሎጂ የሬዲዮ ስርጭት ገቢን እንደቀነሰ ሁሉ ለወደፊቱ በሚመጡ የተሻሉ የስርጭት መንገዶች ክለቦች የስርጭት ገቢያቸው ሊጎዳባቸው ይችላል፡፡ ከዚህም ሌላ ከጊዜ ወደ ጊዜ ተመልካቾቻቸው ቀስ በቀስ እየቀነሰባቸው ያሉት ክለቦች ለወደፊቱ የስታዲየሞቻቸውን መልካም ድባብ ለመመለስ የቲኬት ዋጋቸውን እንዲቀንሱ ይገደዱ ይሆናል፡፡
ኮሜርሺያል
በአጠቃላይ ሲታይ የፕሪሚየር ሊጉ የኮሜርሺያል ገቢ እየወደቀ መምጣቱን ማስተዋል ይቻላል፡፡ ሆኖም አምና ስድስት የሚደርሱ የእንግሊዝ ክለቦች በዘርፉ ገቢያቸውን አሳድገዋል፡፡ ከፍተኛው ገቢ የተመዘገበው በአስገራሚ ሁኔታ የኮሜርሺያል ገቢውን በ159 ፐርሰንት ካሳደገው ማንቸስተር ሲቲ ነው፡፡ ለኢስትላንዱ ክለብ የገቢ ዕድገት በመካከለኛው ምስራቅ አጋሮቹ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ማንቸስተር ዩናይትድም Turkish Airlines, Berfair, DHL, Thomas Cook, Singha, Ebson ከሚባሉ ኩባንያዎች ጋር በፈጠረው የንግድ አጋርነት ስምምነት የኮሜርሺያል ገቢው ከፍ ብሏል፡፡ በዚህ ረገድ የተጎዱት ከደረጃቸው ጋር የሚመጣጠን ገቢ አያገኝም የሚባሉት አርሰናል እና ሊቨርፑል ናቸው፡፡ በርካታዎቹ የአውሮፓ ክለቦች በማሊያ ላይ ስፖንሰር በትጥቅ አምራች ተቋማት ኮንትራት፣ በስታዲም ስያሜ መብት እና በመሳሰሉት ገቢዎቻቸውን አሳድገዋል፡፡
የስፖንሰር ድርጅቶች በስታዲየም በርካታ ተመልካች የሚኖረውን እና ጨዋታዎቹ በበርካታ ሀገራት በቀላሉ የሚተላለፉለትን የጀርመን ቡንደስሊጋ ይመርጣሉ፡፡ ለምሳሌ ሼልክ ከኮሜርሽያል ገቢ የሚያገኘው ዓመታዊ 66 ሚሊዮን ፓውንድ ከማንቸስተር ዩናይትድ በስተቀር ሁሉንም የእንግሊዝ ክለቦች ያስከነዳል፡፡ ዩናይትድ በተመሳሳይ ዘርፍ የሚያገኘው 81 ሚሊዮን ፓውንድ ግን ባየር ሙኒክ ከሚሰበስበው 144 ሚሊዮን ግን አይነፃፀርም፡፡ ይህ ልዩነት የእንግሊዞች ክለቦች ከፍተኛ ክፍያ የሚያስገኙ የማሊያ ስፖንሰሮች እንዲያፈላልጉ አበረታቷቸዋል፡፡ በዓመታት ከcartsberg 7.5 ሚሊዮን ፓውንድ ዓመታዊ ክፍያ ሲያገኝ የኖረው ሊቨርፑል ከአዲስ ስፖንሰሩ standard chartered 12.5 ሚሊዮን ፓውንድ ይቀበላል፡፡ በቀድሞው ስፖንሰሩ AIG 14 ሚሊዮን ፓውንድ ይከፈለው የነበረው ዩናይትድ ከ Aon በ6 ሚሊዮን ፓውንድ የተሻለ ክፍያ ያገኝ ጀምሯል፡፡ ቼልሲ ከsumsung ጋር ባደረገው ድርድር ዓመታዊ ክፍያው በ4 ሚሊዮን ፓውንድ አድጎለት 14 ሚሊዮን ፓውንድ ደርሷል፡፡ ከMansion 8.5 ሚሊዮን ፓውንድ ይከፈለው የነበረው ቶተንሃምም ከጥንዶቹ አዲስ ስፖንሰሮቹ Autonomy እና Investec 12.5 ሚሊዮን ፓውንድ ያጋብሳል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አብዛኞቹ ክለቦች የትጥቅ አቅራቢ ስፖንሰሮቻቸው ጋር የተሻለ የሚባል ውል ፈፅመዋል፡፡
የክለቦችን አጠቃላይ የገቢ ዕድገት አስፈላጊነት በሁለት አቅጣጫ ልንመለከተው እንችላለን፡፡ በመጀመሪያ የእንግሊዝ ክለቦች ከአውሮፓ ተቀናቃኞቻቸው ጋር ተፎካክረው የዓለም ምርጡ ተጨዋቾችን በተሻለ የዝውውር ሂሳብ እና ደመወዝ ለማግኘት ጥሩ የገንዘብ አቅም ያስፈልጋቸዋል፡፡ የታዳጊ ማዕከሎቻቸው በይበልጥ ውጤታማ እንዲሆኑም ከፍተኛ ኢንቨስትመንት ይፈልጋሉ፡፡ ሆኖም የደመወዝ እና የዝውውር ወጪዎች ማደግ የአውሮፓ እግርኳስ ማህበር ያስቀመጠውን 70 ፐርሰንት የደመወዝ ገቢ ንፃሬ ይጋፋል፡፡ የአውሮፓ እግርኳስ ማህበር በቅርቡ ይፋ ያደረገው መረጃ እንደሚያረጋግጠው በ53 ፐርሰንት (11.7 ቢሊዮን ዩሮ አድጓል፤ አስገራሚ ነገር ግን ወጪያቸው በ9.3 ፐርሰንት መጨመሩ ነው፡፡ ኪሳራቸውም በሁለት እጥፍ ጨምሮ 1.2 ቢሊዮን ዩሮ ደርሷል፡፡
ስለዚህ የአውሮፓ እግርኳስ ማህበርን ደንብ ላለመጣስ ክለቦቹ ገቢያቸውን እግርኳሳዊ በሆኑ መስኮች ማሳደግ ይኖርባቸዋል፡፡ በዴሎይቴ መረጃዎች እንደሚታየው የፕሪሚየር ሊጉ ክለቦች አሁንም ከሌሎቹ ሊጎች ተወካዮች በተሻለ የወደፊቱን ፈተና ሊወጡ ይችላሉ፡፡ በአሁኑ የዓለም ኢኮኖሚ እግርኳስ ታማኝ ‹‹ደንበኞች›› ያሉት መሆኑ እድለኛ ያደርገዋል፡፡ እግርኳስን የሚያፈቅሩ ሰዎች የሚወዱትን ክለብ ለመከታተል በስታዲየም መገኘት፣ የቴሌቪዝን ስርጭት ክፍያ መፈፀም እና የክለባቸውን ቁሳቁስ መግዛት አላቆሙም፡፡ የክለብ ባለቤቶችን እየጠሉም (የማንቸስተር ዩናይትድ ደጋፊዎች መልካም ምሳሌ ናቸው) በክለቡ ላይ ገንዘባቸውን ያወጣሉ፡፡ ሆኖም ክለቦች በቴሌቪዥን ክፍያ ሳይዘናጉ የኮሜርሽያል እና ሌሎች ገቢዎቻቸውን እንዳያሳድጉ የሚገደዱበት በርካታ ምክንያት አለ፡፡ ክለቦቹ ለዚህ የሚሆኑ አማራጮች ሲፈልጉ ጊዜው እየሄደባቸው ይመስላል፡፡ ክፉው ቀን እንደተፈራው በቶሎ ከመጣ ክለቦች ወጪዎቻቸውን እንዴት እንደሚሸፍኑ መመልከት ያጓጓል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ፋሲል 1 ወልዋሎ 0
Share