May 11, 2011
47 mins read

‹ትራንስፎርሜሽን እና ቦንድ› ፈተና ውስጥ ያሉ ሁለቱ የኢትዮጵያ እንግዶች

ከእውነቱ በለጠ
ብቸኛው የህዝብ ተወካይ የሆኑት አቶ ግርማ ሰይፉ ‹‹ህዝቡ ቃሪያ እና ብርቱካን የመሳሰሉትን አጥቶ ትራንስፎርሜሽንና ቦንድ የሚባሉ ቃላቶችን የማኘኩ ነገር ምስጢሩ ምንድን ነው?›› በማለት ለአቶ መለስ ጥያቄ ቢያቀርቡላቸው፣ የአቶ መለስ መልስ ያው የታወቀውና የተቀመመ እንደሚሆን ይገመታል፡፡ ‹‹ዕድገታችን ያመጣው ጉዳይ ነው፤ ህዝብ አይደግ አንልም፤ ለዚህም አንሰራም፡፡ ስለዚህ ህዝብ ተገቢ አመራር ያልነበረው በመሆኑ ቃሪያ እና ብርቱካን ይበላ፣ ባይሆኑም ያይ የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ግን ልማታዊ መንግስታችን በሰጠው ብልህ አመራር ህዝቡ ቃሪያ እና ብርቱካንን ልክ እንደ ድህነቱ ታሪክ አድርጓቸዋል፤ በምትኩም ትራንስፎርሜሽንና ቦንድ ከሚባሉ ዘመናዊ ቃላቶች ጋር እየተዋወቀ ነው፡፡
ይሄም አገራችን መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ተርታ ለመቀላቀል ዋዜማው ላይ የቆመች መሆኑን ያመላክታል›› የሚል ትንታኔ በሚሰጡበት ጊዜ፤ በዓመት 33 ሚሊዮን ብር እየከፈልን የምንቀልበው ፓርላማ የተለመደውን ሳቁን ይዘረግፋል፡፡ ዘንድሮ መቼም ፓርላማ የተለመደውን ሳቁን ይዘረግፋል፡፡ ዘንድሮ መቼም ፓርላማ ካልሆነ የሚስቅ ህዝብ የለም፡፡ ኮሜዲ ቴአትር የሚታይባቸው ቴአትር ቤቶች እንኳን እንዲህ አይሳቅም፡፡ የሆነ ሆኖ ፓርላማም ሳቁን ካልዘረገፈ የሚዘረገፍ ቃሪያና ብርቱካን የለንም፡፡
የቃሪያ እና የብርቱካን ነገር ከተነሳ ሥጋንም እንጨምርና በየዓመቱ ፓርላማ በመንቀልብበት 33 ሚሊዮን ብር፤ ከአርባ ሰባት ሺህ ኩንታል በላይ ብርቱካን ወይም ከ66 ሺህ ኩንታል በላይ ቃሪያ፤ አምርተንና አቅርበን የኢትዮጵያን ህዝብ ለመመገብ እንችላለን፡፡ ህዝባችን ፍላጎቱ ሥጋም ከሆነ በዚሁ ብር ከ7 ሺህ በላይ የደለቡ ሠንጋዎችን ለህዝቡ አቅርበን አምሮቱን ልንቆርጥለት እንችላለን፡፡
በሌላም መልኩ ለአራት የፓርላማ ዘመን ተቀምጠው ለዋሉ እና ወደ ፊትም ተቀምጠው ለሚውሉ የፓርላማ አባላት አገሪቱ የምትከፍለውን 7 ቢሊዮን ብር ለመቆጠብ ብትችል ኖሮ አባይን ለመገደብ 73 ቢሊዮን ብር ብቻ በጎደለን ነበር፡፡
ሀሳቤ አገሪቱ ፓርላማ አያስፈልጋትም በማለት ጭራሽ ለአምባገነኖች የተመቸች ትሁን ለማለት አይደለም፡፡ ፓርላማው የፓርላማ ተግባር የማያከናውን ከሆነ እና ‹‹ተቀምጦ ዋይ›› የፓርላማ አባላትም ምን ሰራችሁ ተብለው፤ በሰማይ ቤት ነፍሳቸው እንድትጠየቅ ከምናደርጋቸው፤ ገንዘቡም ቢቆጠብ፤ እነሱም ከገሃነም ቢተርፉ ለማለት ነው፡፡ የፓርላማ አባላቱ የነፍስ ነገር በጣም አሳሳቢ ነው፡፡ ነፍስ ሰማይ ቤት ስትደርሰ ቀድሞ የሚቀርብላት ጥያቄ በመሬት እያለሽ ምን ሰራሽ? የሚለው ነው፡፡ መቼም የፓርላማ አባላቱ ነፍስ ‹‹ሰዎች ሲዛትባቸው፤ ተቀምጬ እስቅ ነበር›› የምትል ከሆነ ክፉ እሳት ይጠብቃታል፡፡
ፓርላማ በእርግጥ ከህዝቡ ውስጥ ተመርጦ በህዝብ የተመሰረተና ለህዝብ የሚሰራ ሲሆን መድኃኒትነቱ የታወቀ ነው፡፡ ነገር ግን የእኛ ፓርላማ በየት በየት ቀዳዳ ሾልከው የገቡ ሰዎች የበዙበት ለመሆኑ ተጠራጣሪ የለም፡፡ አንድ ጤና ጣቢያ ለአንድ ቀን ቢዘጋ አንድ ብርቅዬ እናት ትሞታለች፤ አንድ ትምህርት ቤት ለአንድ ቀን ቢዘጋ ብዙ ልጆች ከዕድሜአቸው በአንድ ቀን ይቀንሳሉ፤ አንድ ታክሲ ለአንድ ቀን ብትበላሽ ከ400 የማያንሱ ሰዎች የትራንስፖርት አገልግሎት ያጣሉ፤ አንድ ገበሬ ታሞ አንድ ቀን ቢተኛ አገሪቱ ልታገኝ የምትችለውን አንድ ፍሬ በቆሎም ቢሆን ታጣለች፡፡ እንዲያው ፓርላማው ለድፍን 5 ዓመት ቢዘጋ ምን እንሆናለን? ምንም ነው መልሴ፡፡ በበኩሌ ምንም አንሆንም ነው የምለው፡፡ የአቶ መለስ ትዕዛዝ እንደሆነ እጅ ስላልተቆጠረለት ትዕዛዝ ከመሆን፤ የአቶ መለስ ቁጣም በሳቅ ስላልታጀበ፤ አስፈሪ ቁጣ ከመሆን የሚከለክለው ምንም ነገር አይኖርም፡፡ የአቶ መለስ ትዕዛዝ ፓርላማ ኖረ አልኖረ፤ ከፍ ዝቅ ሊል የሚችልበት ሁኔታ የለም፡፡ በፓርላማው አቶ መለስን ‹‹አልበዛም እንዴ? አሁንማ ይብቃ እንጂ›› የሚል የለም፡፡ የማን አገልጋይ እየሆነ ይታወቃል፡፡ አገልጋይ ቁጥሩ፤ መቶም ሆነ አምስት መቶ ጌታውን እረፍ አላበዛኸውም እንዴ? ለማለት አይችልም፡፡ ጌታ ጌታ ነው፤ አገልጋይም አገልጋይ ነው፡፡ የአገልጋዮች ትልቁ ድክመት ደግሞ በአንዴ ማገልገል መረረን አይሉም፡፡ በጣም የመረረው በተናጠል መረረኝ በሚልበት ሰዓት መራራ መቅመስ የቻለው ምላሱ ይቆረጥለትና በቦታው መረረኝን የማያውቅ ምላስ ያለው ሌላ አገልጋይ ይተካል፡፡ እንዲህ እየሆነ የአገልጋዮች ቁጥር ሳይጎል ጌታቸውን ያገለግላሉ፡፡ የዘንድሮዎች አገልጋዮች ለመጽናኛ ይሆናቸው ዘንድ ‹‹ክቡር›› የሚባል ቅጽል ተጨምሮላቸዋል፡፡ ማናችንም ብንሆን ሰዎች እስከ ሆንን ድረስ የሚያስከብር ስራ ሳንሰራ ክቡር መባላችን በውስጣችን የሚነፈርቅ የህሊና ቁስል መተው የማይቀር ነገር ነው፡፡ ነገሩ ሁሉ በህሊና እየቆሰሉ በልብ፤ በስም ብቻ መከበር እንደ ማለት ነው፡፡
ትራንስፎርሜሽን የመጀመሪያው የኢትዮጵያ እንግዳ
የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ በደንብ ሳይታሰብበት የተዘጋጀ መሆኑን፤ ከራሱ ከስሙ ብቻ መረዳት ይቻላል፡፡ ምክንያቱም እቅዱ በደንብ ቢታሰብበት ኖሮ ከዚህ በተሻለ ገላጭነት ያለው ስም መስጠት ይቻል ነበር፡፡ በተለይም የስሙ አንደኛው አካል አማርኛ፤ ሁለተኛው አካል ደግሞ እንግሊዝኛ መሆኑ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን የሚለውን እቅድ ነጭና ጥቁር የፊት ቀለም ያለው አንድ ሰው የማየትን ያክል ያልለተመደና የሚያደናግር አድርጎታል፡፡ የእቅዱን ስም ሌላው ሰው ቀርቶ፤ የእቅዱ ፈጣሪ የሆኑት አቶ መለስ እንኳን የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱን የስር ነቀል ለውጥ እቅድ ሲሉ ተሰምቷል፡፡ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ማለት እና የስር ነቀል ለውጥ እቅድ ማለት ለእኔ እቅድ አይነት መልዕክት አይነግሩኝም፡፡
በእርግጥ አሁን ዓለም አንድ መንደር ሆናለች በተባለበት ጊዜ የቋንቋዎች መወራረስ የማይቀር ቢሆንም ባዕድ ቋንቋ እንዳለ ከመውሰዳችን በፊት ግን የአገር ቤት አቻውን ለማግኘት ጥረት ማድረግ ነበረብን፡፡ ጃፓኖች መውሰድና የራስ ማድረግ (Copying and Assimilation) የሚል ስልት የሚከተሉ ሲሆን፤ ሱፐር ማርኬት (super market) የሚለውን ባዕድ ቃል ‹‹ሱፐር ማርኬት›› ወይም ‹‹ትልቁ ማርኬት›› አይሉትም፡፡ አሳጥረው ‹‹ሱፓ›› ይሉታል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ ቴሌቪዥን የሚባለውን ‹‹ቴሌቢ››፣ ስቶር የሚለውን ደግሞ ‹‹ዲፓቶ›› ይላሉ፡፡ ይህ አይነቱ የመውሰድና የራስ የማድረግ ስልት ቃላትን በማዳቀል የሚፈጠረውን የተዳቀለ ስሜት ያስወግዳል፡፡ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን የሚለው ቃል፤ የተዳቀለ ስሜት የሚፈጥር በመሆኑ በዕቅዱ ላይ የዝግጅትና የቁርጠኝነት ችግሮች እንደነበሩ ያሳያል፡፡
መንግስት ከ2003-2007 ዓ.ም ድረስ ያለውን የ5 ዓመት እቅድ ዝግጅት አስመልክቶ የገንዘብ እና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ለባለበጀት መ/ቤቶች፣ ስለ 5 ዓመቱ እቅድ በመጋቢት ወር 2002 ዓ.ም ማብራሪያ ሲሰጥ፤ እቅዱን የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ ብሎ አልጠራውም ነበር፡፡ እንዲያውም ከ2003-2007 ዓ.ም የሚኖረው የ5 ዓመት እቅድ በይዘቱ ካለፈው የ5 ዓመት እቅድ አጠናክሮ መቀጠል እንደሆነ አስረድተው ነበር፡፡
በመሆኑም የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ የታቀደውና ስያሜውም የተሰጠው መረጃ፤ ተሰብስቦ ጥናቶች ተደርገው ባለሙያዎችና ህዝብ ተወያይተውበት የዕቅዱ ግብዓቶች መኖራቸው ተፈትሾ ሳይሆን ከ2002 ምርጫ በኋላ እንዲያው በግድየለሽነት በይድረስ ይድረስ የተዘጋጀ እንደሆነ ከተግባሩ ለመረዳት ይቻላል፡፡ ለዚህ አንዱ ማመላከቻ እቅዱ ታትሞ የተሰራጨበት ጊዜ ነው፡፡ እቅዱ የ5 ዓመት እቅድ እንደ መሆኑ መጠን 2003 ዓ.ም የእቅዱ ማሳተሚያ እና ማስታወቂያ ሳይሆን የእቅዱ መተግበሪያ ጊዜ መሆን ነበረበት፡፡
ለምሳሌ ጃፓኖች በ2005 ያደረጉትን ሰፊ የመዋቅር ለውጥ በፓርላማ አፅድቀው፣ አሳትመውና ሂደቱን የሚከታተል አካል ሰይመው ከመተግበሪያው ጊዜው 3 ዓመት ቀድመው በ2002 ለህዝብ አሰራጭተዋል፡፡ እንግዲህ ኃላፊነት ያለበት መንግሥት እንዲህ በቂ ዝግጅት አድርጎ፤ ከህዝብ ለሚገኝ አስተያየትም በቂ ጊዜ ወስዶ የዝግጅትና የትግበራ ጊዜውን ለይቶ ይሰራል እንጂ የዝግጅትንና የትግበራ ጊዜን እያቀላቀሉ ፈጽሙልን ሲባል ዝግጅት ላይ ነን የሚሉ፤ ዝግጅት ላይ ናቸው ሲባሉ ፈፀምን፤ አጠናቀቅን ምን አድርጉ ትሉናላችሁ? የሚሉ ህዝቡን የሚንቁ፣ ለህሊናና ለህዝብ ተጠያቂ ያልሆኑ አምባገነኖች ብቻ ናቸው፡፡ በፕሮፓጋንዳ እንደ ተካበደለትና እንደ ተወራለት ያለ ‹‹የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ›› እቅድ ለማቀድና ለማከናወን የ3 ወሳኝ ነገሮችን መሟላት ይጠይቃል፡፡ እነሱም የዳበረና ስር የሰደደ የአሰራር ስርዓት፤ የተፈጥሮ ሀብትና የካፒታል ክምችት፤ እንዲሁም የሰለጠነ የሰው ሀብት ናቸው፡፡
1. የዳብረና ስር የሰደደ የአሰራር ስርዓት
የአሰራር ስርዓት ምን እንደሆነ ለማወቅ እኛ ሰዎች ራሳችንን ማየት በቂ ነው፡፡ በሰዎች ውስጥ ፍፁም የረቀቁና እርስ በርሳቸው የተደጋገፉ ተግባራቸውን ወለም ዘለም ሳይሉ የሚያከናውኑ ስርዓቶች አሉ፡፡ ጥቂቶችን ለመዘርዘር ያክል የመመገቢያ ስርዓታችን /Digestive system/ የስሜት ስርዓታችን /Nervous System/፣ የመራቢያ ስርዓታችን /Reproductive system/፣ የደም ዝውውር ስርዓታችን ወዘተ… ናቸው፡፡ እነዚህ ስርዓቶች በውስጣቸው እንዲሁም አንዱ ስርዓት ከሌላው ስርዓት ጋር ያለው ግንኙነት ካልተስተካከለ የሚከተለውን ነገር እናውቀዋለን፡፡ አቶ ሞት አሁን ጊዜው የእኔ ነው በማለት በደስታ ይፈነጫል፡፡ የስርዓቱ ጉለት ካልተስተካከለም አቶ ሞት ሰለባውን ይዞ ለመሄድ ከልካይ የለውም፡፡
አንዲት አገር ስር ነቀል የህብረተሰብ ለውጥ የሚያመጣ እቅድ ተግባራዊ አደርጋለሁ ከማለቷ በፊት አስቀድመው የነበሩ እና መሬት የወጉ የአሰራር ስርዓቶች መኖራቸውን መፈተሽና አስተማማኝነታቸውን ማረጋገጥ ይኖርባታል፡፡ እነዚህ የአሰራር ስርዓቶች የምንላቸው ለምሳሌ የአመራረት፣ የትምህርት፣ የቁጠባ፣ የስራ ፈጠራ፣ የክትትልና ግምገማ፣ የመረጃ ልውውጥ፣ የጥናትና ምርምር፣ ትራንስፖርትና ኮሙኒኬሽን፣ የሀብት አጠቃቀም፣ የፍትህ፣ የዳኝነት፣ ሌሎችም ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ አገሪቱ ባለፉት ሃያ ዓመታት ተዋጣልኝ የምትለው ምንም አይነት የአሰራር ስርዓት የላትም፡፡ እንዲያውም አንዱን ስትይዝ ሌላውን ስትጥል እንዲሁ ስታገላብጥ የኖረች ምንም አይነት ስርዓትም ሆነ ስነ-ስርዓት የሌላት አገር ሆናለች፡፡ የዳብረ እና መሬት የያዘ የአሰራር ስርዓት አለ ከተባለ እሱ በኢህአዴግ ሻንጣ ወይም በአቶ መለስ ኪስ ውስጥ ብቻ የሚገኝ ባለመሆኑ ሁላችንም መኖሩን አይተን ለመመስከር እንችል ነበር፡፡ ነገር ግን የሌለ ነገር ስለማይታይ እኛም አይተን አለ ለማለት አልቻልንም፤ አለ የሚሉም ካሉ እነሱ ውሸት ልማድ ሆኖባቸው እንጂ፤ አሳዩኝ ለሚል ማሳየት አይችሉም፡፡
ከመመገቢያ ስርዓቱ ውስጥ ጉሮሮው ለተቀደደ ሰው እርጎ ብናጠጣው እርጎው ወደ ውጪ ወደ ደረቱ ይፈሳል እንጂ፤ ወደ ውስጥ ወደ ሆድ ዕቃው ገብቶ ሰውዬውን ለመጥቀም አይችልም፡፡ የአንድ እጁ የስሜት ህዋስ የተጎዳ ሰው እጁን ከማገዶ ጋር ቀላቅሎ እሳት ውስጥ ቢቆሰቁሰው የሚነደው ፍልጥ ይሁን የእሱ እጅ ለመረዳት አይችልም፡፡ በመሆኑም ሙስና ስር በሰደደበት አገር፤ የልማት እቅድ መያዝና ለእቅዱ ማስፈፀሚያ የሚሆነውን ገንዘብም በግብር፤ በመዋጮ፣ በቦንድ ሽያጭ፣ በእርዳታና በብድር በማግኘት ስራ ላይ ማዋል በተቀደደ ጉሮሮ እርጎ እንደ ማንቆርቆር ነው፡፡ የክትትልና ግምገማ፣ የነፃ መረጃ፣ የተጠያቂነትና ኃላፊነት ስርዓት በሌለበት አገር ገንዘብ አውጥቶ በልማት ስራ ላይ ማዋል ማለት እጅን እሳት ውስጥ ቆስቁሶ እንደ መሞቅ ማለት ነው፡፡
በመሆኑም ለእቅዱ መሰረት የሆኑት ስር የሰደዱና መሬት ወጉ የአሰራር ስርዓቶች ሳይኖሩ ከዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ በሚገኙ ውጤቶች ህዝቡ መካከለኛ ገቢ ያለው ህዝብ እሆናለሁ ብሎ ማሰብ፤ መካከለኛ ገቢ ያለው ሰው ለመሆኑም መመኘት፤ ስህተቶችን በወቅቱ አለማረም ይሆናል፡፡ እንዲያውም ጉሮሮው እንደ ተቀደደው ሰው፣ እጁ እሳት ውስጥ እንደተማገደ ሰው፣ በፍጥነት ወደ ሞት እየገሰገሰ መሆኑን መረዳት አለበት፡፡ ከሞት ለማምለጥ የሚቻለው ደግሞ እርጎ እየተበደሩም እየለመኑም ወደ ተቀደደው ጉሮሮ በማንቆርቀር ሳይሆን የተቀደደውን ጉሮሮ በማከምና የተሟላ የመመገቢያ ስርዓት በመፍጠር ብቻ ነው፡፡
የዳበረ እና ስር የሰደደ የአሰራር ስርዓት የሚለውን ነገር በደንብ ተገንዝበነው ማለፍ ይገባናል፡፡ መቼም ጃፓን የሚለው ቃል ‹‹ቦንድ›› ቦንድ አለን አትበሉኝ እንጂ፤ ጃፓኖች በጣም የዳብረ እና ስር የሰደደ የባቡር ኔትዎርክ ስርዓት አላቸው፡፡ እንደ መገኛው ጊዜ /Frequency of availability/ እና እንደ ፌርማታው እርዝመት /Distance Jumped/ ሎካል /local/፣ ሰሚ ኤክስፕረስ /Semi-Express/ ኤክስፕረስ /Express/፣ ራፒድ /Rapid/፣ እና ሺጅካንሴን /Bullet train/ የሚባሉ የባቡር አይነቶች አሏቸው፡፡ በግሉ አጥርና ሃዲድ በመላዋ ጃፓን ከሚፈረጥጠው የምድር ላይ ተተኳሽ ሺንካንሴም በስተቀር ሌሎች የባቡር አይነቶች በአንድ ሃዲድ ይጠቀማሉ፡፡ ጃፓኖች ከ30-50 ዓመት በሆነው የባቡር የአገልግሎት ዘመናቸው አንድ ባቡር አንድ ቀን የመድረሻ ሰዓቱን ሳይጠብቅ በመድረሱ ይህ ቀን በባቡር አገልግሎት ታሪካቸው ፍፁም የሚገርም ቀን ተደርጎ ተመዝግቧል፡፡ በእኛ ሀገር ሰዓት አሳልፎ መገኘት የተለመደ እንጂ፣ ይህን ያህል ነውር ሆኖ እና ጉድ ተብሎ ታሪክ አይመዘገብለትም፡፡ ሎካል የሚባለው ባቡር በቆሙበት ፌርማታ በየ3 ደቂቃው የሚመጣልዎት ሲሆን ወደ ውስጥ ሲገቡም እንደ አየሩ ሁኔታ በክረምት የሚሞቁት እሳት፣ በበጋ ደግሞ የሚቀዘቅዙበት ንፋስ ተዘጋጅቶ ይጠብቅዎታል፡፡ እያንዳንዱን መንደር ሲደርሱበት ስሙ በድምፅ ማጉያ ይነገርዎታል፡፡ ቅድሚያ ለሚገባቸው /Priority/ የሚሉ መቀመጫዎችን ያገኛሉ፡፡ እነዚህ ቅድሚያ ለሚገባቸው የተባሉ መቀመጫዎች እዚህ እኛ አገር የገዥው መደብ ሹማምንቶች ብቻ የሚቀመጡባቸው መቀመጫዎች እንደ ማለት አይደለም፡፡ ጃፓን አገር ሹም የተሾመው ሊቀመጥ ሳይሆን ሊሰራ ነው፡፡ ጃፓን አገር የተሾመ ሰው ክብርን በገነት እና በትውልድ ሂደት የሚጠብቅ እንጂ ዛሬ ክቡር በሉኝ፤ አንቱ በሉኝ እያለ የልማት ጊዜውን አያጠፋም፡፡ ሰሞኑን አላዩም ጠቅላይ ሚኒስትራቸውን? በክራባት ታንቀው ወንበር ላይ ተዘፍርቀው ንግግር ሲያደርጉ አይታችኋል? ፊታቸውን ቅጭም አድርገውና በጃኬት ተሸክፈው ጃፓን መቼም አትወድቅም፤ ሁላችንም አደጋው የደረሰባችሁ በሙሉ ትካሳላችሁ፤ ትነሳላችሁም ብለው የጀግና ስራ ሲሰሩ አላዩም? የጃፓን ጠ/ሚኒስትር ናኦቶ ካን የደረሰው አደጋ በጣም ቀላል ነው፤ ድንቢጥም አይጥም አትሁኑ ብለው በህዝባቸው ላይ ጭካኔ አላሳዩም፡፡ ጠ/ሚኒስትሩ ለአገሬ የሚሆን የትኛውም አቅም በእጄ ቢኖርም ዓለም ግን በዚህ በመከራዬ ጊዜ ሊረዳኝ ይገባል ብለው የአደጋውን ደረጃ ራሳቸው እየተከታተሉት ለዓለም ያሳውቁ ነበር፡፡
ለማንኛውም ኧረ ለመሆኑ እነዚያ ቅድሚያ የሚገባቸው የተባሉ መቀመጫዎች የማን መቀመጫዎች ናቸው? እነዚያ መቀመጫዎች ጌታዬ የአካል ጉዳተኞች፣ የነፍስ ጡር ሴቶች፣ እና የህፃናት መቀመጫዎች ናቸው፡፡ ጌታዬ በዚህ አገር በጃፓን ንጉሱም እንኳን ቢሆኑ የህፃናትን፣ የአረጋውያንን እና የነፍስ ጡር ሴቶችን ያክል ሊከበሩ ከቶ አይታሰብም፡፡ እነዚህ መቀመጫዎች የቱንም ያክል ባዶ ቢሆኑ ከእነዚሁ ከተከበሩት ሰዎች በቀር ሌላ ምንም ሊቀመጥበት አይችልም፡፡ በእርግጥ ቢቀመጡበት ፖሊስ መጥቶ እንደማይዝዎት አረጋግጫለሁ፡፡ ግን በእነዚያ መቀመጫዎች በመቀመጥዎ በፖሊስ አይታሰሩ እንጂ የአገር መሳቂያ ይሆናሉ፡፡
እርስዎ ግን እዚህ አዲስ አበባ በስንት ህፃናት ራስ ላይ ወጥተው ታክሲ ይዘዋል፤ ስንት ነፍሰ ጡር ሴቶች ገፍትረው እርስዎ በጊዜ ቤትዎ ገብተዋል፤ ስንት አረጋውያንን ገፍትረው ኪሳቸውንም ፈትሸው ዝም ተብለዋል፡፡ በጃፓን ግን ይሄ ሁሉ ተደርጎ ቀርቶ በእነሱ መቀመጫ ላይ ተቀምጠው ቢገኙ እንኳን የአገር መሳቂያ ይሆናሉ፡፡
ታዲያ የዳበረና ስር የሰደደ የአሰራር ስርዓት ማለት ይህ አይነት አይደለም ይላሉ? ካሉ እባክዎት ለጋዜጣው አዘጋጅ ይላኩለትና እንማርበት፡፡
2. የተፈጥሮ ሀብት እና የካፒታል ክምችት
የገዢው መደብ አባላት እንደመሰኩሩት ያለ ዕድገት እና ለውጥ ለማምጣት በጣም የተከማቹ የተፈጥሮ ሀብቶች ማግኘት የግድ ይላል፡፡ እነዚህም ሀብቶች በጣም የበለፀጉና የውጭ ኢንቨስትመንትንና ቴክኖሎጂን ለመሳብ የሚችሉ ሰፊ የስራ እና የገበያ ዕድል መፍጠር የሚችሉ፤ የአገሩን ህዝብ ከድህነት የሚያወጡና የሚያነቃቁ እንደ ነዳጅ፣ አልማዝ፣ መዳብ፣ ወርቅ እና ሌሎች የከርሰ ምድር ማዕድኖች መገኘት አለባቸው፡፡ የዐረብ አገሮች ምንም እንኳን አደጉ ከሚባሉት አገሮች ተርታ ለመመደብ ብዙ ቢቀራቸውም፤ ከአገራቸው ዜጎች አልፈው በሚሊዮን ለሚቆጠሩ የሌላ አገር ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር የቻሉት በዚህ እውነታ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ከማዕድን ሀብት ሳይሆን ከእርሻ እና ከውሃ ሀብቷ ለዕድገቷ እና ለለውጧ የሚሆን ዕድል ያላት ቢሆንም፣ በዚህ በኩል ያለው ዕድል ኢህአዴግ ሞቶ እስከሚቀበር ድረስ ጥቅም ላይ የማይውል ሆኖ ስለተቆለፈበት አገሪቱ ልማቷን ለማፋጠንና ህዝቧን ለመመገብ የሚያስችል ምንም አይነት የተፈጥሮ ሀብት አላት ለማለት አይቻልም፡፡ በከርሰ ምድር ተከማችቶ ሊወጣ ከተዘጋጀ ሀብት በተጨማሪ በደህና ቀን ያስቀመጡት የተቆጠበ እና የተከማቸ ሀብትም ለልማት መነሻ ይሆናል፤ ችግርም ሲያጋጥም ያከማቹትን ካፒታል አውጥቶ መጠቀም ይቻላል፡፡ አሜሪካ እና ጃፓን ያደረጉት ይሄንን ነው፡፡ በደህናው ጊዜ ያከማቹትን ድልብ ሀብት ለችግራቸው ሲያውሉ አይተናል፡፡
ኢህአዴግ ግን በ20 ዓመት ግባት ዘመኑ ያስመዘገበውን ዕድገት ሰላቢ ያሹልክበት፣ ሙሰኛ ይንጠቀው አልታወቅም፡፡ ከተመጽዋቹ ህዝብ ምጽዋት በመሰብሰብ ላይ ይገኛል፡፡ እንዲህም ሆኖ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ታቅዷል፤ አፈፃፀሙም በተፈለገው ልክ እየሄደ መሆኑም አይጥ ለድንቢጥ መመስከር ሳያስፈልጋት በአውራው ተረጋግጧል፡፡
3. የሰለጠነ የሰው ሀብት
ይሄ ነው የሚባል የተፈጥሮ ሀብት ሳይኖራት በሰለጠነ የሰው ሀብቷ ብቻ የስልጣኔ ማማ የወጣቶች መሆኗ የሚነገርላት ልዕለ ሃያል አገር ጃፓን ነች፡፡ የጃፓን የዕድገት ምስጢር የሰለጠነ የሰው ሀብቷ መሆኑን ለማወቅ ዓለም አቀፍ ተመራማሪ መሆን አይጠይቅም፡፡ ያለመታደል ሆነና ተምረን እንዳልተማረ ሰው መሰልጠን አልታቸለንም እንጂ፤ የጃፓን የዕድገት መሰረቱ የሰለጠነ የሰው ኃይል መሆኑን ገና ከ9ኛ ክፍል የጂኦግራፊ ትምህርታች ለመረዳት ችለን ነበር፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያዊ እንደ አቅሙ በትምህርቱ ለመግፋት የሚከፍለውን ያህል ዋጋ የከፈለው የሰለጠነ ሰው ለመሆንና የሰለጠነ አገር ለመፍጠር ነበር፡፡ ታዲያ ምን ያደርጋል ‹‹አርሶ መራብና ተኩሶ መሳት ልብ ይለበልባል እንደ እግር እሳት›› እንደሚሉት የኢህአዴግ የፕሮፖጋንዳ ማራገፊያ ጎተራ ሆነን፤ ተምሮ ዋሾዎች ሆነን፡፡ ይህች አገር ለስልጣኔ ይህን ያህል መስዋዕትነት ከፍላ ሌላው ሌላው ቢቀር እንኳን እውነት የሚነገርባት፤ ስነ ምግባር የሚታይባት አገር መሆን አልቻለችም፡፡
ስልጣኔ ማለት ዘመናዊ ጃኬት አጥልቆ፤ በክረባት ታንቆ፤ ወዛም ፊትና ቦርጭ አምቦርጭጮ፣ ቂጥ አደላድሎ G+3 ህንፃ በመገንባት ብቻ ስልጡን ነኝ ማለት ቆጥ ላይ የተንጠለጠለ ዶሮ መሆን ነው፡፡ እውነትን እና ፍትህን ሳይፈልጉ ቦርጭ ማንቦርጨጭና ዳሌ መደልደል የማይቆረጥ ሥጋ መሸከም ነው፡፡ እውነትን እና ስነ-ምግባርን የዕለት ከዕለት መመሪያ ሳያደርጉ ክራባት ማንጠልጠል ያው መታነቅ ነው፡፡
የስልጣኔ መጀመሪያው እውነትና ስነ-ምግባር ነው፡፡ ከዚያም ልዩ ልዩ ጥበቦችን መቅሰምና ለራስና ለወገን ጥቅም መዋል ይቻላል፡፡ እውነት በማይሰማበት አገር ከፍተኛ በጀትና የሰው ሀይል ተመድቦ ውሸት በሚበረታታበት አገር፣ እውነት በኢትዮጵያ ሰማይ እንዳያልፍ መሬቱ እና ሰማዩ በታጠረበት አገር የሰለጠነ ሰው እንዴት ማግኘት ይቻላል? እንዴትስ ህዝብን እንዲሰለጥንና እንዲለወጥ የሚያደርግ እቅድ ማቀድና መተግበርስ ይቻላል? እቅድ እኮ ተጨባጭ የሰዎች እንቅስቃሴ ውጤት እንጂ በታምር የሚገመጥ ዳቦ አይደለም፡፡ የሰለጠነ ሰው ይፈልጋል፡፡
ለዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ ቋሚ ምሰሶ /strategic pillars/ የሆኑት የዳብረ የአሰራር ስርዓት፣ የተፈጥሮ ሀብትና የካፒታል ክምችት እንዲሁም የሰለጠነ የሰው ኃይል በሌሉበት ውጤት በመጠበቅ በቻለ በልተን ለማደር እንችላለን ማለት የለብንም፡፡ በእቅዱና በአፈፃፀሙ ላይ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ በልተን የማደራችንን ነገር አስተማማኝ ማድረግ ይኖርብናል፡፡ ካድሬዎቹ እንደሚነግሩን ከዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ የሚገኘውን ፍሬ ለመብላት ትላልቅ ቅርንጫፎችን በማዘጋጀት ብቻ የምንወሰን ከሆነ አቶ ሞት ወደ ሌላ አገር ሳይሆን ወደ እኛ አገር በፍጥነት እየገሰገሰ መሆኑን ቁልጭ አድርገን ልናየው ይገባል፡፡
ቦንድ 2ኛው የኢትዮጵያ እንግዳ
የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱን መተግበር፣ የማቀዱንና ትራንስፎርሜሽን፣ ትራንስፎርሜሽን አያሉ የመደለቁን ያክል ቀላል ባለመሆኑ ሌላ እንግዳ ወደ አገር ውስጥ ማስገባት የግድ ሆነ፡፡ ይሄም ቦንድ የሚሉት ነው፡፡ ቦንድ እንደ ትራንስፎርሜሽን ሁሉ የአገር ቤት አቻው ሳይፈለግለት ኢትዮጵያዊ የሆነ እንግዳ ቃል ነው፡፡ አላማውም የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱን ለማስፈፀም የሚሆን ገንዘብ ከህዝቡ ለማስገኘት የታሰበ ሳይሆን አይቀርም፡፡ እንደ ተባለውም የቦንድ ግዢውን የጋለ ለማድረግ አንድ ዘዴ መፈለግ ነበረበት፣ ተፈለገም፣ ተገኘም፣ አባይ ሊገደብ ነው ተባለ፡፡ ሌለው ሁሉ ዘርፈ ብዙ ስራ ተትቶ ስራው ሁሉ ‹‹አባይና ቦንድ›› ሆነ፡፡ ቦንድ በፈጠረው ግለት ምክንያትም በደንብ ሳይታሰብበት የሚሌኒየም ግድብ የተባለው የህዳሴ ግድብ ተባለ፡፡ ምንም ሳይጠና በ10 ዓመት ያልቃል የተባለው ግድብም በ6 ዓመት ያልቃል ተባለ፡፡
ኢህአዴግ የሚናገራቸውና የሚያደርጋቸው ነገሮች ለህዝብ ሁሌም የማይገጣጠሙ በመሆኑ አባይን ለመገደብ የሚያስፈልገውን ገንዘብ በቦንድ ሽያጭ የማግኘቱ ነገር አጠራጣሪ ሆኗል፡፡ የአባይ መገደብ በማንም ዘንድ ተቃውሞ የማይፈጥር ቢሆንም በኢህኤግ የአያያዝ ችግር ምክንያት ህዝቡ ግራ ተጋብቷል፡፡ ህዝቡ የአባይ ግድብን ይፋ ማድረግ ያስፈለገው ታህሳስ 28 ቀን 2003 ዓ.ም የተገለፀውን የዋጋ ተመን ቅሌት ለማረሳሳት እና ሰልፍ ሳይወጣበት ቀድሞ ለመውጣት እና ምንም ገንዘብ ሳይያዝ የታቀደውን የትራንስፎርሜሽን እቅዱን ለሃፍረት መመለሻ ያህል ለማከናወን ተጨማሪ ገንዘብ ለማግኘት ነው እንጂ አባይን ለመገደብ አይደለም የሚል መላምት ላይ የደረሰ ይመስለኛል፡፡ ይሄ እንግዲህ የእኔ የግል አስተያየቴ ነው፡፡ በእርግጥ መላምቴ እውነትነት አለው፡፡ ምክንያቱም መንግስት ከአፍሪካ ልማት ባንክ በተገኘ ብዙ ሚሊዮን ዶላር ብድር ከባህር ዳር ከተማ 40 ኪሎ ሜርት ላይ በሚገኘው በጀት፤ ሜዳ ላይ የተሰራውን የቆቃ ወንዝ ግድብን አጠናቆ፤ ጥቅም ላይ ሳያውል ሌላ ግድብ ጀመርኩ ማለቱ እንዲሁም አቶ መለስ ከአንዴም ሁለቴ እንዲያውም ለ3ኛ ጊዜ የአዲስ አበባ ከተማ የትራንስፖርት አገልግሎት ይስተካከላል እመኑኝ ብለው ተናግረው እስካሁን ተግባራዊ ሳያደርጉ፤ የዋጋ ንረቱም ይወርዳል እንዲያውም ለህዝቡ በቂ ዘይት ገዝተናል ብለው እስካሁን ዘይት ማቅረብ ሳይችሉ፤ የዋጋ ቅናሽ ቀርቶ በተጠራው ዋጋም እንኳን ሸቀጦች እንዲገኙ ማድረግ ተስኗቸው በረሃ ወርደው አባይን ይገድባሉ ብሎ ለማመን ከባድ በመሆኑ ነው፡፡ ትንሹን መስራት ያልቻለ ትልቁን መስራት አይችልም የሚለው ቀላልና ግልጽ ማወዳደሪያ ስለሆነ መስጋቱ ጨለምተኝነት አይደለም፡፡ እነዚህ ሁሉ ውዥንብሮች ህዝቡ ቦንድ በመግዛት የግድቡን መገደብ እውን የማድረግ አቅሙን ሊያዳክም ይችላል፡፡ በመሆኑም ትራንስፎርሜሽንም ሆነ ቦንድ ሁለቱ የኢትዮጵያ እንግዶች ወደ አገር ውስጥ የገቡበትን አላማ አሳክተው አሁን በካድሬዎች እንደሚደሱት በህዝቡ ዘንድ ተቀባይነት የሚኖራቸው እንግዶች የመሆናቸው ነገር አጠራጣሪ ይመስለኛል፡፡ ሁለቱም የራሳቸው የሆነ ፈተና አለባቸው፡፡
የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ ለምን ታቀደ
እስካሁን ካለው የእቅዱ አያያዝና አፈፃፀም አኳያ ሲታይ እቅዱ የታቀደው በእቅዱ የተያዙትን ግቦች ለህዝብ ለማበርከት ሳይሆን እንዲህ አይነት ነገር ኢህአዴግ የተለመደውን ባህሪውን የሚያሳይበት ሆኗል፡፡ ከራሱ ከኢህአዴግ መነጠል የማይቻለው የኢህአዴግ መሰረታዊ (Intrinsic) ባህሪ ለዛሬ ብቻ መኖር የሚለው የድርጅቱ ባህሪ ነው፡፡ ኢህአዴግ ነገ ሌላ ቀን ነው፤ ዋናው ነገር ዛሬን ማለፍ ነው የሚል ድርጅት ነው፡፡ እያንዳንዷን ቀን በዚህ መልክ ማለፍ እንጂ ዛሬ ላይ ሆኖ ነገን፤ መጪውን ወር፣ መጪውን ዓመት ለመመልከት የሚችል ድርጅት አይደለም፡፡ በዚህ ባህሪው ድርጅቱ በጭራሽ በህዝብ ዘንድ አመኔታ እንዲያጣና እንዲያውም ፀባዩ ምን እንደሆነ የማይታወቅ ድርጅት አድርጎታል፡፡ እንዲያው ሩቅ ሳንሄድ፤ አሁን ባለንበት ሰዓት ድርጅቱ ‹‹አባይ ይገደባል›› ሲል፤ እምነት የተጣለበት ድርጅት ቢሆን ኖሮ ህዝብ ‹‹አዎ አባይ ይገደባል›› ማለት ነበረበት፡፡ ሆኖም ግን ህዝቡ አባይ ይገደባል የተባለው ለምን አላማ ነው? በማለት በሊቃውንት ደረጃ የማይደረግ ምርምር በመመርመር ላይ ይገኛል፡፡
እንደ እኔ እምነት ኢህአዴግ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱን ለማቀድና ይፋ ለማድረግ የተገደደው፤ ከ2002 ምርጫ ጋር በተያያዘ በዚያም በዚህም የሚፈነዱ ቀዳዳዎችን ለመለሰን ነው፡፡ ከዚህ አኳያ እቅዱ የድርጅቱን ስለታዊ ግብ አሟልቷል፡፡ ምክንያቱም ሌላው ቀርቶ የአዲስ አበባ ህዝብ እንኳን እፎይ ባቡር መጣልኝ፤ ታክሲ ደህና ሰንብት ብሏልና፡፡ ውጤቱ ግን ባቡር ቀርቶበት ለታክሲ የሚከፍለውን ገንዘብም የቦንድ ግዢና መዋጮ በሚል ምክንያት እየተመናመነበት ነው፡፡ እናም የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ የልማት እቅድ ሳይሆን የማስቀየሻ እቅድ ነው ብዬ ነው የማስበው፡፡ አሁን ግን በላዩ ላይ ከፍተኛ የማስቀየስ አቅም ያለው የአባይ ግድብ በመምጣቱ እቅዱን እንደ እናት ጡት መርሳት ተችሏል፡፡
እቅዱ ሊስተካከል አይችልምን?
አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ እቅድ በዝግጅት ጊዜም ሆነ በትግበራ ወቅት ሊስተካከል የሚችል ቢሆንም፤ በኢህአዴግ ግትር አቋም ምክንያት እቅዱ በሚፈለገው መልክ አልተስተካከለም፡፡ አቶ መለስ እቅዱን እንዲያስተካክሉ ሲጠየቁ ‹‹የወሎ እረኛ›› አትሁኑ ነው ያሉት፡፡ አቶ መለስ አልገባቸውም እንጂ የወሎ እረኛ የታከተው (የደበረው) ነገሩ እንደማይሆን ሆኖበት ነው፡፡ የማይሆን ነገር ያታክታል (ይደብራል)፡፡ ዛሬ ይኸው አቶ መለስም ትራንስፎርሜሽን ታከታቸው፤ በአባይ ግድብ አንዴ ሚሌኒየም አንዴ ህዳሴ እያሉን ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ብዙ የታከተው ነገር አለ፡፡ ለምን ቢባል ኢህአዴግ የያዛቸው አብዛኛዎቹ ነገሮች የማይሆኑና መሆን ያለመቻላቸውም የተረጋገጠ በመሆኑ ነው፡፡ ኢህአዴግ የህዝብ ምክርና አስተያት አይቀበልም፡፡ ‹‹ወደብ መብታችን ነው›› ሲባል፤ ‹‹ወደብ ሸቀጥ ነው›› ይላል፡፡ ‹‹ሻዕቢያ ጠላት ነው መመታት አለበት›› ሲባል፣ ‹‹የዘላለም ጠላት ከሞት ያድናል፤ መረጃ አቅም ነው›› ይላል፡፡ በሌላም በኩል ‹‹ዲያስፖራው የልማት ገንዘብ ማዋጣት አለበት›› ብሎ ስብሰባ ይጠራል፤ የተጠራው ሰው ሲመጣ ‹‹ለምን መጣችሁ?›› ይላል፡፡ የኢህአዴግ ልዑክም እውቀት ገንዘብና ነፃነት ባለው ዲያስፖራ ተዋርዶ በፊት በር መውጣት ሲገባው በኋላ በር ይወጣል፡፡ ኢህአዴግ አገሪቱ ከዲያስፖራው ይገኝ የነበረውን ገንዘብና እውቀት እንዳታገኝ ምክንያት በመሆኑ ተጠያቂ ሊሆን ይገባል፡፡
የእቅዱ ዘመን 20 በመቶ ምንም አይነት ስራ ሳይሰራ ያለፈ እንደ መሆኑ መጠን፣ በቀሪዎቹ 4 ዓመታት የእቅዱ ዘመን እዚያም እዚህም የተበቱኑ የእቅዱን ክፍሎች በማሰባሰብ ከሁሉም በላይ ለዴሞክራሲ እና ለመልካም አስተዳደር ግንባታ ትኩረት ሰጥቶ ህዝቡ በተደጋጋሚ ለሚያነሳቸው የዴሞክራሲና የመልካም አስተዳደር እንዲሁም የህግ የበላይነት ጥያቄዎች ምላሽ መስጠት የግድ ይላል፡፡µ

Previous Story

The trails keeping Ethiopia's distance runners in sprint condition

Next Story

Itching the unitching (Yalbeluten Makek)

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop