February 18, 2024
13 mins read

የካቲት ሄደ የካቲት መጣ – አንዱ ዓለም ተፈራ

3000

ሐሙስ የካቲት ፯ ቀን ፳ ፻ ፲ ፮ ዓ. ም. (2/15/2024)

በመካከሉ ሐምሳ የካቲቶች አለፉ! ይሄም የካቲት ሊያልፍ ነው!

ዛሬ፤ ሃምሳ ዓመታት ወደ ኋላ ዞሬ የነበርኩበትን ስቃኝ፤ የተመኘሁትና የተከተለው ምን ያህል የተራራቀ መሆኑን ስነዘብ፤ ወይ ጉድ! እላለሁ። በሕልሜም ቢሆን አገራችን እንዲህ ባለ ሁኔታ ውስጥ ትማቅቃለች የሚል ግምት አልነበረኝም። ያን ጊዜ፤ ኢትዮጵያ ለምን ከሠለጠኑት አገራት ወደ ኋላ ቀረች! የሚል የአገር ወዳድ ስሜት ሁሉን ነገር መመልከቻ መነፅሬ ነበር። በተማሪነቴ ከዩኒቨርሲቲ ተማሪ ጓደኞቼ ጋር አብሬ ወዲያ ወዲህ ስል፣ በመምህርነቴ በሸዋ ክፍለ አገር በመናገሻ አውራጃ፣ አቃቂ መለስተኛ ትምህርት ቤት መምህራንን ወክዬ ስድስት ኪሎ ከነበረው የመምህራን ማኅበር ጽሕፈት ቤታችን ስመላለስ፣ በሕቡዕ በሚንቀሳቀሰው የጥናት ቡድናችን ስሯሯጥ፤ ኢትዮጵያ አዲስ ምዕራፍ ቀድዳ ወደ ሥልጣኔ ስትጓዝ ብቻ ነበር የሚታየኝ። ያን ጊዜ ተማሪዎችና ለውጥ ፈላጊው ወገን  ጥያቄዎቻችን ምን ነበሩ? ምኞታችን ምን ነበር? ከዚያ እስካሁን እኒህ ጥያቄዎቻችን እና ምኞታችን ምን አጋጠማቸው? ይህ ነው የዚህ ጽሑፍ ትኩረት።

ዛሬ ዐማራነት ወንጀል ሆኖ፤ ዐማራዎች በያሉበት እየታደኑ የሚገደሉበት እውነታ ወቅቱን ገዝቷል። ዛሬ አገሪቱ በትውልድ ዞግ አጥሮች ተከፋፍላ፤ አንዱ ሌላውን በጥርጣሬ፣ በቅናትና በጠላትነት የሚመለከትበት ሀቅ በአገሪቱ ሰፍኗል። ዛሬ ጉራጌው በኦሮሞ ገዥዎች እንቅልፍ አጥቶ፤ ነገ ምን እንደሚከተል ሳያውቀው ውሎ የሚያድርበት እውነታ ጠርንቆ ይዞታል። ዛሬ አብይ አሕመድ ጠቅላይ ሚኒስትር፣ ከዶክተሮች የበለጠ ሕክምና አዋቂ፣ ከሃይማኖት መሪዎች በላይ የሃይማኖት ሊቅ፣ ከኢኮኖሚስቶች ሁሉ በላይ ስለ አገሪቱ የምጣኔ ሀብት ሁኔታ አስሊ፣ ከነጋዴዎች በላይ ነጋዴ፤ ከለማኞች በላይ ለማኝ፤ አልፎ ተርፎም ከፈጣሪ በላይ ፈጣሪ አድርጎ ራሱን ሰይሟል! ወይ ጉድ! ጉድም እኮ  ልክ አለው!!!

መቼም በሺ ዘጠኝ መቶ ስድሳ ስድስት ዓመተ ምህረት ተቀምጦ፤ በሁለት ሺ አስራ ስድስት ዓመተ ምህረት የሚሆነውን በርግጠኝነት የሚያናግር፤ ምንም ዓይነት ተዓምር አልነበረም። ዛሬም በሁለት ሺ ስድሳ ስድስት ምን እንደሚሆን የሚነግረን ተዓምር የለም። በተማሪነቴ እንደ ተማሪዎች፣ በመምህርነቴ እንደ መምህር፣ በለውጥ ፈላጊነቴ ደግሞ እንደ ታጋይ የጣርኩት፤ ለዚህ አልነበረም። በመካከል መንግሥቱ ኃይለማርያም፣ መለስ ዜናዊና አብይ አሕመድ ገቡና፤ በግላቸው አገሪቱን አንቀሳቃሽ ሆነው፤ የኋሊት ነዷት። ላለንበት ሀቅ ተጠያቂዎቹ እኒህ ናቸው። በአገር መውደድና በወገን ፍቅር የተንገበገብን ተማሪዎች፤ በዚያ ጊዜ ሊኖረን የሚችለውን ዕድል ሁሉ ትተን፤ ለወገን ስንል ሕይወታችን ሠጥተናል። የሰው ልጅ መብት ይከበር ዘንድ፣ የያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲያዊ መብቶች መከበር በተግባር ይውል ዘንድ፣ በወንዶችና በሴቶች መካከል የነበረው የፆታ እኩልነት ይከበር ዘንድ፣ የድሃ ልጅ ትምህርት ያገኝ ዘንድ፣ ከከታማ ውጪ የሚኖረው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሕክምና ያገኝ ዘንድ፣ መሬት ለሚያርሰው ይሆን ዘንድ፣ አድልዖና ሙስና ይጠፉ ዘንድ፣ ባደባባይ ሰልፍ ወጥተን፣ በፖሊስ ተሳደድን! በተለይ ከክፍለ አገራት የመጣን ተማሪዎች የምንበላው ሳይኖረን ከግቢ ተባረን መግቢያ እንድናጣ ተደርገን! መሪዎቻችን ታሰረው! ያን ሁሉ ስንከፍል፤ በተዓምር ያገራችን “የውጪ ጠላቶች መሳሪያ” ተባልን። በሃያና የሃያዎቹ መጀመሪያ የነበርን ተማሪዎች፤ የአገር ድህነትን ለመቋቋም፣ የአገራችን ኋላ ቀርነትን ለማስወገድ፣ የተራበውን ለመታደግ፤ የራሳችንን የወደፊት ዕድል ዘጋን። የዕለት ምግባችንን ለወሎ ረሃብተኞች እንዲሠጥ አደረግን። አዲስ አበባን ከቁሻሻዋ ለማላቀቅ ሶስት ቀናት ዘመትን። ያ ነው አሁንም አእምሮዬ ውስጥ ያለው። በርግጥ ዛሬም የኢትዮጵያ ሕዝብ የመንግሥት ጢሰኛ ነው! ዛሬም ዴሞክራሲያዊ መብቱ ተገፎ ነው ያለው። ዛሬማ ብሶ ታሪኩና ማንነቱ ተሰርዞ፤ እንደ መንጋ፤ ትግሬ ነህ – ትግሬ በሙሉ እንደ አንድ ትግሬ ብቻ ስለሚስብ፤ አንተም እንደ ትግሬ አስብ፣ ኦሮሞ ነህ –  ኦሮሞ በሙሉ እንደ አንድ ኦሮሞ ብቻ ስለሚስብ፤ አንተም እንደ ኦሮሞ ብቻ አስብ፣ ዐማራ ነህ –  ዐማራ በሙሉ እንደ አንድ ዐማራ ብቻ ስለሚስብ፤ አንተም እንደ ዐማራ ብቻ አስብ፣ እንደ ሶማሊ፣ እንደ ከምባታ፣ እንደ ሃድያ፣ እንደ አፋር፣ እንደ ጋምቤላ፣ እንደ ጉራጌ፣ እንደ አደሬ፣ እንደ አዲስ አበቤ፣ አስብ ተባለ። ለመሆኑ አንዱ ዐማራ አገሩንና የአገሩን ፖለቲካ በሚመለከት፤ ከአንዱ አፋር ምን የተለዬ አሳብ አለው? ሁለት የተለያዩ ኦሮሞ ግለሰቦች፤ ከአንድ ጉራጌ የበለጠ የሚያተሳስራቸው የፖለቲካ አመለካከት አለ? አኙዋኩንስ? በአጥር የተከለሉ፣ የተለያዬ ቋንቋና መንግሥታዊ ስርዓት ያላቸው አድርጎ መግዛቱ ማንን ለመጥቀም ነው?

ይሄ በትውልድ ማንነት ላይ በተመሠረተ የፖለቲካ አገሪቱን የመግዛት አካሄድ፤ ልዩነትን ምርኩዝ አድርጎ ሥልጣን ለመያዝና ለመግዛት የተደረገ ስሌት ነው። ለሰላሳ ዓመታት ባገራችን ነግሦ ስለቆዬ፤ ዘለዓለማዊና ምን ጊዜም ያለ ተደርጎ ሊታሰብ ይችላል። ነገር ግን አገር አፍራሽ ብቻ ሳይሆንል ሕዝብ አጨራራሽ ነው። ይሄም ያልፋል! ከሃምሳ ዓመታት በኋላ፤ ያኔም እንዲሁ አገራችን ከነበረችበት የበለጠ ዘቅጣ እንድትገኝ አልፈልግም። በሥልጣን ላይ ያለ ትክክለኛ ያልሆነ መሪ፤ የሚያስበው ራሱን ዘለዓለማዊ መሪ አድርጎ ማኖር ብቻ ነው። መንግሥቱ ኃይለ ማርያም፤ እሱ ዘለዓለማዊ መሪ ሆኖ እንዲኖር ነበር ሌት ተቀን የሚያውጠነጥነው። መለስ ዜናዊም! ብቻ መልስስ እስከ ዕለተ ሞቱ ነግሧል! ይሄኛው ደግሞ በጥንቁልና የመጣሁ ነኝ! እያለን ነው። በራሱ የማይተማመን መሪ፤ ከሱ በፊት የነበረውንም ሆነ ከሱ በኋላ የሚከተለውን ይጠላል። ሁሉ ነገር በሱ ተጀምሮ በሱ የሚያልቅ አድርጎ ትርክት ይፈጥራል። የትግሬዎች ነፃ አውጪ ግንባር በሥልጣን ላይ ሲወጣ፤ ኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት ለመጀመሪያ ጊዜ አገኘች አለን! የነበረውን ጨርሶ መካድና አልነበረም ማለት፤ የትግራይ ሕዝብ ነፃ አውጪ ግንባርን ፈጣሪ ያደርጋልና! ስላሁኑማ ከኔ የበለጠ አንባቢ ስለሚያውቁ፤ ምን እላለሁ!

ዛሬም መሬት ለአራሹ አልተሠጠም። ዛሬም ሹም ማለት አድራጊ ፈጣሪ ማለት ነው። ዛሬማ፤ እዚህ አትሄድም! በዚህ አታልፍም! እየተባለ ሕዝቡ ባለበት ታጉሯል። ዛሬ መሪው አውቅልሃለሁ! አንቺ ዝም በይ! አንተ ዝም በል! ሆኗል አገዛዙ። በትውልድ ማንነትህና በብልፅግና ብቻ ነው መደራጀት ያለብህ! አለዚያ ትታሰራለህ< ትገረፋለህ፣ ሀብትህ ይነጠቃል፣ ጻደዳለህ፣ ትገደላለህ! ተብሏል ሕዝቡ። የፈረደበት ዐማራ፤ ዐማራነቱ ወንጀል ሆኖ፤ በየተገኘበት እየታደነ ነው። ለምን? ብሎ ለሚጠይቀኝ፤ ከጠንቋይ ቤት ስላላደግሁ፤ አላወቅም! ነው መልሴ። እናቴም ስታሳድገኝ፤ ተማር እንጂ ጠንቋይ ይሆናለህ አላለችኝም።

በኢትዮጵያ የተከሰተ ለውጥ ቢኖር፤ ትልልቅ ሕንጻዎች በየቦታው ተገትረዋል፣ ጥቂት ከገዢዎቹ ጋር የተገናኙ ቢሊየነሮች ብቅ ብለዋል፣ የአንድ ወገን መሆን የሚጠቅምበት፣ የሌላ ወገን መሆን የሚጎዳበት እውነታ ነግሧል። ተጠቂው ዐማራ፤ አሁንስ በቃኝ ብሎ ተነስቷል! የራሴን የነገ ዕጣ ራሴ እወስናለሁ ብሎ አምጿል። ሕዝብ ምን ጊዜም አቸናፊ ነውና፤ ዐማራ ያቸንፋል። የኢትዮጵያ ሕዝብ ነቅቷል። የኢትዮጵያ ሕዝብ፤ መከፋፈሉ ለገዢዎች አመቺ ከመሆን በስተቀር፤ ለሕዝቡ እንደማይጠቅም ስለተረዳ፤ ፋኖን የኔ ብሏል። ፋኖ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃ አውጪ ሠራዊት ነው። አብሮ የመሰለፊያ ሰዓቱ አሁን ነው። ከአካባቢ ጥበቃ ተነስቶ፤ ወደ ሻለቃ፣ ብርጌድና አሁን ወደ ዕዝ የተመነደገው የፋኖ አገር አዳኝ ጦር፤ በየትኛውም ቦታ በር እያንኳኳ ነው። ለምን ዘገዬ እንጂ፤ ለምን ቸኮለ የሚል ማንም የለም። ፋኖ፤ እየመጣ ነው! መብትህን ለማስከበርና ባገርህ ለመኖር የፈለግህ ሁሉ ካሁኑ ተባበር! ይህ ትግል የሁላችንም ነው። ሌላ ዓምሳ ዓመታት መኖር ባልችልም፤ ይህ ሁኔታ ሀቅ ሆን  ያኔ ብቅ እንዲል አልፈልግም።

 

 

5 Comments

  1. ልክ ብለሃል ወዳጄ። ያ ሁሉ እልፎች ህይወታቸውን ያጡበት፤ ቤተሰብ የበተኑበት፤ በበረሃ የተንከራተቱበት፤ በእስርና በግርፋት የማቀቁበት፤ ቁስላቸው ሳይደርቅ ዳግም በጨካኞች የተቀጠቀጡበት፤ አልፎ ተርፎም ከእነ ቁስላቸው የተረሸኑበት ያ የመሬት ላራሹና ሌሎችም የመብት ጥያቄዎች ዛሬ ላይ ቆም ብሎ ለተመለከተው ቢላሽ ነው። ግን ይህም ያም ወደፊት ሊሆን ያለውም ክፉና በጎ ነገር ” A Time Victim” የጊዜ ቁስል ውጤት ነው። ጊዜ ያቆስላል፤ ይፈውሳል፤ ያፈርሳል፡ ይጠግናል። ለንጉሱ ጋቢና ነጠላውን አንጥፎ ያጨበጨበው ደርግ በዚህም በዚያም ወሬ አናፍቶ ከሥልጣን ሲያወርዳቸው ” ሌባ ሌባ” በማለት ነበር የጨፈረው። ለመንግስቱ ታላቅ ጭብጨባና ሆታ በማድረግ ቆራጡ መሪያችን ይሉ የነበሩት ዛሬ በረንዳ ላይ አዳሪዎችና ተሰዳጆች ናቸው። ወያኔ የሃገር መሪ ሆኖ ኤርትራ የምትባል ሃገር አለች እወቁልን እያለ ሲማጠን ዳግም ወያኔና ሻቢያ ይፋለማሉ ብሎ ያሰበ የለም። ግን ሌባ ሲካፈል እንጂ ሲሰርቅ አይጣላምና በኢትዮጵያ ሃብት ባድሜን አሳበው ተላለቁ። የሰው ደም እንዲህ ነው ይጣራል። ይጮሃል፤ እንቅልፍ አያስተኛም፡ ቀኑ ሲደርስም ይወስዳል።
    ታዲያ ከግፈኛው የወያኔ የዘርና የአፓርታይድ አገዛዝ ነጻ ወጣን በማለት ለጠ/ሚር አብይ በጊዜው የሰገድ አሁን በሚያዪትና በሚሰሙት ምን ይሰማቸው ይሆን? ተሸወድን፤ ተታለልን ወይስ ሌላ የማስተባበያ ቃል ይኖራቸው? አሁን ጊዜው የኦሮሞ ነው ይሉናል። ግን ጊዜ ጊዜአዊ ነው። አይተናል፤ ተራራ ላይ የወጡት መውረጃ ሲያጡ። ይህ አሁን ለእኔ ብቻ የሚለው የኦሮሞ ጠባብ ብሄርተኞች ስብስብ የእድሜ ልክ ተጠዋሪዎቹን ይዞ አዲስ ቀንድ አብቅሎ አሁን በከተማና በገጠር ሰውን ማስጨነቁና መግደሉ ዘላቂነት አይኖረውም። እንደ ኦፌኮ፤ ኦነግ ያሉት ሃይሎች ከሰላምና ከአንድነት ራሳቸውን እያራቁ “ኢትዮጵያ ልትናድ ትችላለች” እያሉ በየሚዲያው ሲናገሩ መስማት ያማል። እያፈረሱ ማላዘን!
    የአማራ ህዝብ በኤርትራው፤ በትግሬው፤ በኦሮሞው ወዘተ የተሸወደው ከንጉሱ ጀምሮ እንጂ አሁን የተጀመረ አይደለም። የአማራ ህዝብ ያኔም አልነቃም አሁንም አልነቃም። የተማሩ፤ ያወቁ፤ የነቁ የአማራ ልጆች በውስጥና በውጭ ሃይሎች እንዲጠሉ፤ እንዲገደሉ የተሰራው የውስጥ ሴራ ሰማይ ጠቀስ ነው። ሃገሬ፤ ምድሬ፤ ወገኔ ህዝቤ ብሎ ሁሉን አምኖ ተቀምጦ እያለ እነዚህ ከጥንት ጀምሮ በዘራቸውና በቋንቋቸው የሰከሩ ስንት ግፍ በኢትዮጵያ ምድር እንደፈጸሙ ለመዘርዘር ጊዜ አይበቃም። ግን ማን ነቅቶ ያኔ? አሁንስ ምን ያህል ህዝቡ ይህን ክፋት ለይቶ ጥንቃቄ ያደርጋል? ከትምህርት ተቋም እስከ ቤ/ክርስቲያንና መስጊዶች እነዚህ መሰሪዎች ሰው መስለው በበጎች መካከል ተኩላዎች በመሆን ስንቶችን በልተዋል አስበልተዋል? ቤቱ ይቁጠረው! ኢትዪጵያዊነታቸውን ተቀብለውና አምነው ለሃገሪቱ ዳር ድንበር ለወገን አለኝታና ኩራት ሆነው ያለፉም አሉ? ግን እነዚያን ማን ያወሳል?
    ስለ ያ ትውልድ ብዙ ማለት ይቻላል። ግን መሬቱ ለአራሽ መሆኑ ቀርቶ ለባለሃብት ሲሆን? የሰዎች እኩልነት በዘርና በቋንቋ ተመዝኖ የሌላው መጨቆኛና ማስፈራሪያ ሲደረግ፤ ትሻልን ትቼ ትብስን ሲያስብል፤ ከሞት የተረፈው የ 60 ዎቹ ትውልድ ቁጭ ብሎ ከማዘን ሌላ ምን ሊያደርግ ይችላል?፡ የጀግና ወሮታ – ከአምቦ እስከ ባልዲግ በተሰኘው መጽሃፍ ላይ ስለ መቶ አለቃ በቀለ በላይ በሰፈው ተተርኳል። ከዚያ ውስጥ አንድ ስንኝ እንዲህ ትላለች።
    የትላንቱን ነገር ይኸው ሆነ ዛሬ
    እድሜ ለትዝታ ድሮን አየሁ ኑሬ።
    ይህ ሰው ስለ ሃገሩ የከፈለው የመከራ ዶፍ በአሃዝ አይሰላም። ስለፉ በዘርና በቋንቋ በጎሳና በብሄር ሳይሆን በንጽህ ኢትዮጵያዊ መንፈስ በመሆኑ መከራው ለእኛ ትምህርት ሆኖናል። ግን በጥባጭ ባለበት ማን ጥሩ ይጠጣል? ገን ብዙ ሃበሳ ምድሪቱን ይጠብቃል። በዘሩና በቋንቋው የተሳከረ ህዝብ የሚያገኘው ትሩፋት መከራና ረሃብ ብቻ ነው።

  2. እውነቱን ሳናውቅ ዛሬም ነጻ አንወጣም። የተማሪዎች እንቅስቃሴ የሚባለው የምእራብ አምላኪ ለነበረው የእኛ ትውልድ የማታገያ አጀንዳዎች ተመርጠው የተሰጡት፣ ይበልጥ አፍራሽ ሊሆን የሚችለውን አይዲኦሎጂ በግልብ እንዲላበስ የተደረገና ከሌሎች ሀገራት ፍቱን የሆኑ አፍራሽ ስልቶች የተተገበሩበት እንቅስቃሴ ነበር። ሀገር ወለድ አልነበረም። የምእራብ ሀገራት ስውር እጆች ያንቀሳቀሱት ላይ ላዩን ምሥራቃዊ ዝንባሌ የነበረው የሚመስል የኢትዮጵያን የአንድነት ምሶሶዎች ብትንትን እንዲያወጣ የተወጠነ ነበር። በተሳካ ሁኔታም ያንን አስፈጽሟል።
    እኛ በኢህአፓ ውስጥ የሁለትና የሦስት አመት ትግል ያደረግን ይሄንን አፍራሽ ተልእኮ ማመን ከተሳነን የትግራይን ተወላጅ ስሙ አጠራሩ ከጎሳው ጋር ቁርኝት ያለውን፣ እህት ወንድሞቹን ያጣበትን የሕወሃትን ትግልና ሕወሃትን ካላወገዝክ ለማለት አይከብድም? በተመሳሳይ ለኦሮሞውና ለኦነግም እንዲሁ። ምን ጨፍጫፊ፣ አውዳሚና የባእዳን ተልእኮ አስፈጻሚዎች ቢሆኑ ባስከፈሉት መስዋእትነት ክብደት እና በራሱ ተሳትፎ ምክንያት ሊኮንን እና ሊያወግዛቸው ይቸገራል ማለት ነው። በዚያ ላይ የጎሳ ፖለቲካ ሲጨመርበት ጎሳውን ያስጠቃ ስለሚመስለው ባይወዳቸውም ‘በወንድሜ ግንባር ደም አልይበት” እንደሚባለው ሺህ ጊዜ በሆዱ ቢያማና ቢጠላቸው እንኳን ለባእድ ትችት አሳልፎ አይሰጣቸውም። አንድ ስው መጠነኛ መስዋእትነት የከፈለበትን ነገር ከንቱ ሆኖ ሲያገኘው ከንቱ ነበር ለማለት እንደሚቸገር እናያለን። በተለይ የሕይወት እድሎችን፣ ፍቅርን፣ የልጅነት ዘመንን የሰጡበት ዓላማ በባእዳን የሚዘወር ሀገር አፍራሽ ተልእኮ ነበር የሚለውን ተቀብሎ ለማመን፣ አምኖ ለመመስከር እጅግ ፈታኝና ራስን ማሸነፍን የሚጠይቅ ራስን በጩቤ የመውጋት ያህል፣ አካልን ቆርጦ የመጣል ያህል ከባድ ነገር ነው። ለዚህም ነው ብዙ ሰዎች በዚህ በንሥሃ መንገድ ላይ ቆመው የማይታዩት። ለዚህም ነው ትውልዱ ወደ እርቅና ፈውስ ሊጓዝ ያልቻለው
    የተከፈለው ዘግናኝ መስዋእትነት “ለከንቱ ነገር ነበር ያንን ያደርግኩት” ብሎ በራስ ላይ ሂስ ለማድረግ የኋሊት ምልከታውን የኪሊማንጃሮ ያህል ያገዝፈዋል።

    • ውድ ተስፋዬ
      እኔ አሁንም ቢሆን በነበርኩበት ወቅት የተካሄደው በውጪ ኃይሎች እጅ ሳይሆን፤ በአገራችን በነበረው ተጨባጭ ሁኔታ ነበር እላለሁ። አንተ በውጪ ለመሾፈሩና እኛ በግልብ የተነዳን ለመሆናችን ማስረጃ ካለህ፤ አሜን ብዬ ልቀበል ዝግጁ ነኝ። እኔ ነበርኩበት፤ አንተ ሰምተህ ወይንም በጫፉ ደርሰህ ይሆናል። ተሳስቼ ልሆን እንደምችል ገልጨልህ፤ አንተ ማስረጃ ማቅረብ ከተሳነህ፤ አንባቢ በማን እንደሚፈርድ ግልጥ ነው። ያኔ ልናገኝ የምንችለውን ዕድል አሳልፈን ህይወታችንን ለሕዝብ ስለሠጠን፤ በውጪ ኃይሎች ተታለንም ሆነ ተደልለን ያንን አደረጋችሁ ብሎ የሚናገር፤ ማስረጃ ማቅረብ ግድ ይሆንበታል። ድረገጾች ለመወያያ አመቺ ናቸው። መረጃ ደግሞ በግልጥ ሲታይ ያሳምናል። እና ወንድሜ ጋብዤሃለሁ። ማስረጃህን አቅርብና ልታረም።
      አክባሪህ አንዱ ዓለም ተፈራ

  3. አቶ አንዱ ዓለም ተፈራ፣
    እግዜር ይባርክዎት፣ ሃቁን በግልፅ ስላስቀመጡልን።
    ኢትዮጵያ ያፈራቻቸው ብርቅዬ ተማሪዎችና ምሁራን የተቀደሰ ትግል ነበር ያካሄዱት።
    ፋሺስቱ ደርግ በምሥራቆች፣ ተገንጣይ ኃይሎች (ሸዔቢያ፣ ወያኔ፣ ኦነግ) በምእራቦችና በአረቦች ከፍተኛ ድጋፍ ሲሰጣቸው ኢሕአፓ ግን ከጭቁኑ የኢትዮጵያ ህዝብ በስተቀር አንዳች ድጋፍ አልነበረውም፣ ሁሉም የውስጥና የውጪ ኃይሎች ተባብረው አዳከሙት። ዲሞክራሲ ገንብተን፣ ሰላም አውርደን ኢኮኖሚ እንዳናሳድግ እንቅፋት ሆኑብን።

    ስለዚህ ስለ ትውልዶች ሲወራ ሁል ጊዜ ባንዳውንና አርበኛውን፣ ሆድ አደሩንና ሃቀኛውን በሙሉ ባንድ ላይ መፈረጅ ትልቅ ኃጢያት ነው። ካለፉት ጠንካራና ደካማ ጎኖች ሳንማር ወደፊት መራመድ አንችልም

    ዛሬ ደግሞ ዘረኝነቱ ተባብሶ ይገኛል። ጸሐፊው በደንብ እንደገለጹት “ከአካባቢ ጥበቃ ተነስቶ፤ ወደ ሻለቃ፣ ብርጌድና አሁን ወደ ዕዝ የተመነደገው የፋኖ አገር አዳኝ ጦር፤ በየትኛውም ቦታ በር እያንኳኳ ነው”። ዓላማውም ራስን እየተከላከለ አገርም ለለለማዳን ስለሆነ የሁሉም ቅን ዜጋ ብርቱ ድጋፍ ይገባዋል።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

789999kik
Previous Story

   ‹‹የቆላ አጋዘን የገደለ መቶ ከብት ወይም ተመጣጣኝ ካሣ እንዲከፍል አባ ገዳዎች ወሰኑ፡፡››    

4
Next Story

ቤተ-መንግስቱ ታምሷል! | 4 ኪሎ ገብቶ የሰረቀው ሌባ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop