አምና ጳጳሳት ከይሁዳ ጋር ተደራድረው ምን አተረፉ?

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)

 

አምና ይሁዳ ጳጳሳትን ከመንበራቸው ፈንግሎ ተከታዮቹን እነ ሊቀ በርገርን ፓትርያሪክና ጳጳስ ሊያደርግ ሲቃጣ ምዕመናን አንገቱን ሊሰጥ በነቂስ ወጥቶ ከመፈንገል ዳኑ፡፡ በዚህ ወቅትም አያሌ ካህናትና ምዕመናን እንደ እስጢፋኖስ ተቀጥቅጠው ሰማእታት ሆኑ፡፡ ለሰማእታት ፍትህን ሳይጠይቁ ጳጳሳት ከይሁዳ ጋር ድርድር ተቀመጡና ቁጪ አሉ፡፡ ይሁዳም የምእመናኑ ቁጣ እንኳን ለእነ ሊቀ በርገር ለራሱም መቀመጫ አደጋ መሆኑን ተገነዘበና ሽብርክ ብሎ ለአንድ ዓመት ያህል አድብቶ መጠባበቁን ቀጠለ፡፡ ተይሁዳ የተዋዋሉት ጳጳሳትም ብቁ አደሉም ብለው በውግዘት ያባረሯቸውን እነ ሊቀ በርገርን ብቁ ናቸው ብለው በይሁዳ ትእዛዝ መልሰው ከሲኖዶሱ እንዳስገቡ ተናገሩ፡፡ ተዚያም አልፈው እነዚህ ጳጳሳት በመላ አገሪቱ ሕዝብ በባሩድም፣ በሰው ሰራሽ በሽታና ርሃብ ሲረግፍ የተዋዋሉትን ይሁዳ ላለማስቀየም ጪጭ ብለው ከረሙ፡፡ እንቅልፍ እማይወስደው ይሁዳ ግን እንደተለመደው ዉሉን ሰብሮ እያናጠለ ኣንድ በአንድ ማባረሩን ቀጠለ፡፡ እሚገርመው አንዱ ጳጳስ ሲባረር ሌላው ያልሰማ መስሎ ኩምቢውን እንደ ሰጎን ተምግብ ተክሎ መፈንገሉ ተራሱ እስተሚደርስ እየጠበቀ ነው፡፡ ተይሁዳ ጋር ሽምግልና፣ እርቅ፡ ድርድርና ውል የሚቀመጥ መጨረሻው ይኸው ነው፡፡ አሁን ያለው ምርጫ ይህ ነው፡፡ አንድ ላይ ክትሞ ለቤተክርስቲያኗ፣ ለሕዝብ፣ ለአገርና ለራስ ሲሉ ይሁዳን በጥናት ታግሎ ተክርስቶስ ጋር መሆን ወይም ለይሁዳ ገብሮ እነ ሊቀ በርገርን ጌታ ማድረግ፡፡ በአንዴ ለክርስቶስና በይሁዳ ለተሾሙት ለእነ ሊቀ በርገር መስገድ ወይም መታዘዝ አይቻልም፡፡ ለሁለት ጌታ መታዘዝ አይቻልም ብሏላ ቅዱሱ መጥሐፍ!

ከዚህ በታች ያለው ጽሑፍ ከዓመት በፊት ጳጳሳት ተይሁዳ ጋር ድርድር ሲጀምሩ የተሰጠ ምክር ነው! ዛሬም የሰሚ ያለህ! ዲያብሎስን ማመን የቀጠልነው መቼ በማተቡ ይጠናል ብለን ነው?

ተጨማሪ ያንብቡ:   የዐብይ አሕመድ መሰወርና የወያኔ ፕሮፓጋንዳ - መስፍን አረጋ

ሳጥናኤል ወይም ዲያብሎስ ከመላእክት አንዱ ነበር፡፡ ዳሩ ግን ሳጥናኤል የክህደትን፣ የቅጥፈትን፣ የስርቆትን፣ ሕዝብን ከሕዝብ የማጋጨትንና የጭካኔን መንገድ ስለመረጠ ከቅዱሳን መላእክት የተለየ እርጉም ሆነ፡፡  በዚህ እርጉምነቱም በእባብ ተመስሎ አዳምና ሄዋንን ከእግዚአብሔር አለያዬ፡፡ በሰላሳ ዲናር የይሁዳን ጭንቅላት በርዞ ክርስቶስን አሰከዳና አሰቀለ፡፡ በይህ አድግ ተመስሎ የኢትዮጵያን ሕዝብ መርጦ ባልተወለደበት ዘር ጨፈጨፈ፤ አስጨፈጨፈ፡፡  በሌላ አነጋገር የእባብንና ይሁዳን ፈለግ የተከተለ ዲያብሎስን አመነ፡፡ የይህ አድግ ገዥዎችን ያመነም ዲያብሎስን አመነ፡፡

“ዓይኔን ግንባር ያርገው!” ብለን  የውሸት መሐላ ካልማልን በቀር ለሰላሳ ዓመታት ያየነው የይህ አድግ ገዥዎች በኢትዮጵያ የፈጠሙት በደል ሳጥናኤል እባብንና ይሁዳን ተጠቅሞ ተፈጠመው በደል እጅግ የከፋ ነው፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ አሁንም የይህ አድግ ገዥዎችን አምኖ የሚናገሩትን የሚሰማ፣ በቃላቸው ይጠናሉ ብሎ በድርድር፣ በሽምግልናና በእርቅ አንድ ነገር ጠብ ይላል በሚል የሚንዘላዘለው የትዬ ለኔ ነው፡፡  ዛሬ ተፈጠመ የተባለው የጳጳሳት ድርድርም የዚሁ ተሳጥናኤል የከፉትን የይህ አድግ ገዥዎችን የማመን ከንቱ አባዜ ነው፡፡ ይኸንን መንዘላዘልና ከሳጥናኤል የከፉትን የይህ አድግ ገዥዎችን ሰው ማመን የሚያቆመው መቼ ነው?

ጳጳሳትም ሆነ ሌላው ዘለዛላ ፍጡር ተዋህዶንና ኢትዮጵያን ለማጥፋት ቆርጠው የተነሱትን የሳጥናኤል መንገድ ተከታዮች አምነው “አግዚአብሔር ሰማን” እያሉ የተሰውትን ሰማእታት ዘንግተው ወደተለመደው ዓለማዊና የሆድ ኑሮ ማቅናታቸው የሚያሳየው አሁንም የሳጥናኤል የማታለያ ቁማር ገመድ አለመበጠሱንና የሰውም የመጃጃል ኪሳራ አለማለቁን ነው፡፡

ጳጳሳት ሆይ ለመሆኑ የሰሟችሁ እግዚአብሔርና ስማቸውን የተሸከማችሁት ቅዱሳን መላእክት ወይስ  የይህ አድግ አምበሎችና አጫፋሪዎች?

እስከምናውቀው ድረስ ለመጀመርያ ጊዜ ጳጳሳትን እንደ አሽከር ተቢሮ እየጠሩ  ትእዛዝና ተግፃፅ የሰጡ ከመንፈስ ልእልና፣ ከባህልም ሆነ ከሃይማኖት የራቁ የይህ አድግ አምበሎች ናቸው፡፡ የጳጳሳት ትርጉሙ ክርስቶስ የተሰቀለበትን መስቀል የተሸከሙ፣ የመንኩሰ ሞተን ምልክት ቆብን የደፉ፣ መንፈሳቸውን አጎልብተው ሥጋቸውን ያደቀቁ፣ እውነትን የሚሰብኩ፣ የእግዚአብሔር ትእዛዛት ፈጥመው በአርያነት የሚያስፈጥሙ፣ መሰዋእትነትን የሚከፍሉ የእግዚአብሔር አገልጋይዎች ማለት ነው፡፡ ጳጳሳትን በትእዛዝ የጠሩት ደሞ የይህ አድግ አምበሎች ናቸው ፡፡ ይህ አድግ ደሞ ሕዝብን መርጦ ባልተወለደብት ዘሩ ከፋፍሎ የሚያሽጨረግደው፣ በስልጣን ሽሚያ ሚሊዮኖችን ያሳጨደው፣ ዋሽቶና ቀጥፎ የማያባራው፣ ሰርቆና ዘርፎ የማይጠግበው፣ የሳይጣን መንገድ የተከተለው የዲያብሎስ ቀፎ ነው፡፡ ይህም ማለት የእግዚአብሔር አገልጋዮች ታዝዘው ወደ ሳጥናኤል አገልጋዮች ቢሮ ሄዱ ማለት ነው፡፡ ጳጳሳት በትእዛዝ የሄዱትና ተደራድረው የተመለሱት መቼውንም በማተባቸው ተማይገኙት የይህ አድግ ገዥዎች ወይም ወደ ሳጥናኤል ሰዎች ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  አፍ ያለው ጤፍ ይቆላል ወይንስ ካልተናገሩ ደጃዝማችነት ይቀራል - በፓስተር ዲጎኔ ሞረቴው  

በሳጥናኤል ተከታዮች ታዝዞ ለድርድር ቀርቦና እነሱን አምኖ “እግዚአብሔር ሰማን” ማለት እንኳን በእግዚአብሔር አንደ ብረት ባልዛገ የሰው ህሊናም መቀለድ ነው፡፡ እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ በዘር በሽታ ሕዝብን እርሱ በርሱ የሚያባለውን፣ የእርጉዝ ሆድ የሚያሰነጥቀውን፣ የህፃን አንገት የሚያስቀላውን፣ አሩግን ተቤቱ እያፈናቀለ ሜዳ የሚጥለውን፣ የሕዝብ አጥምና አጥንት የተገነባ አገር እንደ ካብ የሚንደውን ይህ አድግን እንደ ቡትቶ ሽርክርክ አርጎ ይቀደው ነበር፡፡ እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ በክርስቶስ ሐዋርያት የተቆረቆረችና በስንት አባቶች የተገነባች ቤተክርስትያን የሚያጠፋውን ይህ አድግን እንደ ሰሃራ በርሃ ድርቅ ያደርገው ነበር፡፡እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ  ዘርፎና ሰርቆ የማይበቃውን፣ ዋሽቶና አታሎ የማይታክተውን ይህ አድግን እንደ ቀትር ጉም ብን አርጎ ያጠፋልን ነበር፡፡ እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ የሰላማዊ ሕዝብ አንገት የሚያስቀነጡስትን የይህ አድግ ገዥዎችና ካድሬዎች እንደ ድንጋይ ሐውልት ድርቅ አድርጎ ባቆማቸው ነበር፡፡እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ የይህ አድግ ገዥዎችን እንደ ይሁዳ በፀፀት ራሳቸውን እዲሰቅሉ ባደረጋቸው ነበር፡፡ እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ ይህ አድግ በግፍ የጨፈጨፋቸው ዜጎች ፍትህን በተጎናፀፉ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ ለቃልቻ አምላኪው ፈርኦን የሚሰግዱ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ጋር የሚነጋገገሩ፣ ስቃይንና ሞትን የማይፈሩ እንደ ሙሴና እያሱ ያሉ የመንፈስም ሆነ ዓለማዊ መሪዎች በሰጠን ነበር፡፡

ስለዚህ ጳጳሳት ሆይ፡- የሰሟችሁ የመሰላችሁ ጉዶች ዶሮ ሳይጠባ ሺህ ጊዜ የሚክዷችሁ የይህ አድግ አምበሎች ወይም ዲያብሎሶች ናቸው፡፡ ይኸንንም ዶሮ ገና አንዴ ሳይጮህ የምታዩት ነው፡፡ የይህ አድግ አምበሎች ያዘዟችሁም አውግዛችሁ ተቤተ ክርስትያን ያባራራችሁቸውን ወሮ በሎች ተነገረ መለኮትና ቀኖና ውጭ ወደ ቅድስትና መቅደስ እንድትመልሱ ነው፡፡ ይኸንን ያዬ እግዚአብሔር ይታዘባል እንጅ የሚሰማን ምኑን ነው?

ተጨማሪ ያንብቡ:  በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ፣ በናይል ተፋሰስ የውሃ ፓለቲካ እና በአፍሪካ ቀንድ ጂኦፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የተደረገ ቃለመጠይቅ - ፕሮፈሰር ተስፋዬ ታፈስ

ዛሬም የሰሚ ያለህ! ዲያብሎስን ማመን የቀጠለው መቼ በማተቡ ይጠናል ብለን ነው?

 

የካቲት ሶስት ቀን ሁለት ሺ አስራ አምስት ዓ.ም.

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share