የኢትዮጵያ የትምህርት ጥራት እንዲሻሻል ከፍተኛ የፖለቲካ ለውጥ ያስፈልጋል

የኢትዮጵያ፤የውዪዪትና፤መፍትሔ፤መድረክ
Ethiopian Dialogue Forum
9900 Greenbelt RD.  E#343 –  Lanham, MD 20706

በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ምሁራን፣ የኢትዮጵያ የውይይትና መፍትሄ መድረክ (EDF) እና እምቢልታ ድርጅት በጋራ ያወጡት መግለጫ።

በ 11 ኛውና በ12ኛው ክፍለ ዘመን ጊዜ፣ በዓለም ላይ ገና የህንጻ ስራ ጥበብ ባልዳበረበት ወቅት፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የነበሩ የስነ ህንጻ ባለሙያዎች ግን ከምድር በታች ህንጻ ለመገንባት የቻሉ መሃንዲሶች እናት ኢትዮጵያ ። የአክሱም ሃውልትን አተካክል ስነ ጥበብ ስናይ ኢትዮጵያውያን በወቅቱ ምን ያህል ምጡቅ የሆኑ የጥበብ ሰዎች ሃገር አንደሆነች ይመሰክራል። በየአድባራቱና በሃገራችን በተለያዩ ክፍሎች የሚገኙ ተጨባጭ የሆኑና ያልሆኑ የጥበብ ስራዎች ኢትዮጵያ የጥበበኞችና የአዋቂዎች ሃገር እንደሆነች ሁሉ ህያው ምስክር ናቸው። ዘመናዊ የጽህፈት ጥበብ ሲመጣ ኢትዮጵያውያን የስነ ልሳን ምሁራን የራሳቸውን ፊደል ከመቅረጻቸውም በላይ የቀረጹት ፊደል በዓለም ላይ ካሉት ፊደላት ሁሉ በተሻለ  የሰው ልጅን ድምጽ ለመጻፍ የቀረበ መሆኑ አጅግ አስደናቂ ፈጠራ ከመሆኑም በላይ በወቅቱ ኢትዮጵያ በዘመናዊ ትምህርት ትልቅ መስፈንጠሪያ ላይ አንደነበረች ያሳያል።

በፍልስፍናው ዘርፍ እነ ዘርዓያቆብን ማንሳት ይቻላል። ወደዚህ እኛ ወዳለንበት ዘመን ስንመጣ ደግሞ ስማቸውን ብንጠቅስ እስኪታክተን ድረስ የምናገኛቸው ብርቅዬ ሃኪሞችን፣ የስነ ጥበብ ሰዎችን፣ ኢኮኖሚስቶችንና በሌሎችም ዘርፎች ተሰማርተው በአለም አደባባይ የኢትዮጵያን ስም ያስጠሩ ምሁራን ሃገር ናት ኢትዮጵያ። ይሁን አንጂ የዓለም ዘመናዊ ትምህርት በከባድ ፍጥነት በሚራመድበት በዛሬው ወቅት የኢትዮጵያ ትምህርት ግን አጅግ ኣሳሳቢ ደረጃ ላይ ወድቆብናል። ከታችኛው ክፍል ጀምሮ  እስከ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ አስከ ዩኒቨርሲቲ ድረስ ያለው የጥራትና የፍትሃዊነት ደረጃው ሲበዛ የወደቀ ነው። እውነት ነው በቅበላ ደረጃ ከዓመት ወደ ዓመት የተሻለ በመሆኑ  በዚህ ረገድ ብዙ ትችት የለውም። ነገር ግን ከፍ ሲል እንደገለጽነው በተለይ በትምህርት ጥራት ጉዳይ ላይ በታሪካችን ያልታዬ የውድቀት ደረጃ ላይ ነን።

በቅርቡ ትምህርት ሚንስቴር ባወጣው ሪፖርት ላይ በዘንድሮው ዓመት የአስራ ሁለተኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና ከወሰዱት 896520 ተማሪዎች መካከል   29909  ያህሎ ብቻ ከመቶ ሃምስና በላይ ማምጣታቸውን፣ ሌሎቹ  96.7% የሚሆኑት ደግሞ ሃምሳ በመቶ የሚሆን ውጤት ማስመዝገብ አለመቻላቸውን ገልጿል። በኣጠቃላይ በትምህርት ቤቶች ደረጃ  ደግሞ  2959  የሚሆኑ ትምህርት ቤቶች ይህንን ፈተና ያስፈተኑ ሲሆን ከነዚህ ውስጥ 1161 የሚሆኑት ትምህርት ቤቶች      ካስፈተኗቸው ተማሪዎች መካከል አንድም ተመሪ ሃምሳ በመቶ ማስመዝገብ እንዳልቻለ ተነግሮናል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በአርባ ምንጭ የባልደራስ አመራሮች እገታን በተመለከተ የፓርቲው ድርጅታዊ መግለጫ

ይህንን የትምህርት ሚኒስቴር ውጤት ስናይ ብዙ የሚነገረን ነገር አለ። በትምህርት ዓለም ውስጥ አንዲህ ዓይነት ከፍተኛ የተማሪዎች መውደቅ ሲኖር በአንድ በኩል ራሱ ፈተናው የወደቀ ወይም ደረጀ መጣኝ ያልሆነ ሊሆን እንደሚችል ይታመናል። በመሆኑም ተማሪዎቹ በዚህ ደረጃቸው ሊያውቁት የሚገባቸውን ያገናዘበ ፈተናው  ነበር ወይ? የሚለው ላይ ምርመራ ይፈልጋል። በሌላ በኩል ግን በሃገራችን ውስጥ የትምህርት ጥራት ጉዳይ በየጊዜው እያሽቆለቆለ ከሚሄድባቸው መሰረታዊ ጉዳዮች መካከል ዋና ዋናዎቹ የሚከተሉት ናቸው።

 

፩. ከፍተኛ የሆነ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ችግር መኖሩ (lack of political commitment)

ትምህርት የሚለወጠው ወደ ስልጣን በሚመጡ ሰዎች የፖለቲካ ቁርጠኝነት ነው። ወደ ስልጣን የሚመጡ መሪዎች የፖለቲካ ራእያቸው በትምህርት የበለጸገ ትውልድ ለማፍራት ቁርጠኝነት ያለው ሊሆን ይገባል። የሃገራችን ትምህርት በአሁኑ ጊዜ የተራበው ይህንን ነው።  ለምሳሌ ያህል ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ በቅርቡ ለፓርላማ ሲናገሩ በአምስት መቶ ቢሊዮን ብር ቤተ መንግስታቸው አካባቢ ግንባት ጀምረዋል።  ግንባታዎች በራሳቸው መልካም ቢሆኑም ነገር ግን ቅድሚያ ለሚሰጠው ጉዳይ ቅድሚያ መስጠት በተለይ አንደ ኢትዮጵያ ላሉ የሃብት ውሱንነት ላለባቸው ሃገራት ወሳኝ ጉዳይ ነው። ጠቅላይ ሚንስትሩ በኢትዮጵያ ስም ተበድረውም ይሁን ተለግሰው ይህንን ብር ሲያገኙ ቶሎ ሊታያቸው ይገባ የነበረው የተጎሳቆሉ ተማሪ ቤቶች ጉዳይ ነበር። ይህንን ብዙ ብር ኢትዮጵያ ውስጥ ላሉ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በጀት ቢመደብ እያንዳንዱ ትምህርት ቤት አንድ ቢሊዮን ተኩል ብር ያገኝ ነበር። ይህ ብር የሁሉንም የኢትዮጵያ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የቤተ መጻህፍት፣ የቤተ ሙከራ፣ የተለያዩ ፋሲሊቲዎችን ሁሉ በግሩም ሁኔታ የሚያሟላ ነበር። ነገር ግን ጠቅላይ ሚንስትሩ ወለል ብሎ የሚታያቸው ጉዳይ የጫካው ፕሮጀክትና የቅንጦት ቤተመንግስት ነው። ትምህርት ላይ ብናተኩር የሚቀጥነው ትውልድ ይህንን የሳቸውን ፕሮጀክት ከፈለገውና ከአመነበት በአንድ ወር ሊሰራው ይችላል። መጀመሪያ ትምህርት ላይ ኢንቨስት ማድረግ ለብዙ ሃገራዊ ራእዮቻችን መሰረት ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አገዛዙ አለኝ የሚለውን ህገ መንግስት በተግባር ቀዶ ጥሎታል!

 

፪. የፖሊሲ ችግርና የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት በትምህርት አስተዳደር ውስጥ

የትምህርት ጥራት የሚያድገው የጠራ ፖሊሲ ሲኖርና የትምህርት አስተዳደሩ ከፖለቲካ ጣልቃ ገብነት የጸዳ ሲሆን ነው። የሃገራችን የትምህርት ችግር በተለይም በትምህርት አስተዳደሩ አካባቢ  ከፍተኛ የሆነ የፖለቲካ ስራ የሚሰራበት ቦታ መሆኑ ነው። የትምህርት አስተዳደር ከዚህ ሊጸዳ ይገባዋል። አገዛዙ ከአካዳሚ ነጻነት ይልቅ በትምህርት ነጻነት ውስጥ የያዘው ጣልቃ ገብነት ትምህርትን በመግደል ኢትዮጵያንና ትውልዱን የእውቀት ድሃ ወደ ማድረግ እየተጓዘ ይመስላል። የትምህርት አስተዳደሩን የተጣባው ይህ የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት መሰረታዊ የትምህርት ጉስቁልናችን ችግር ነው። የዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንቶች፣ በየደረጃው ያሉ ዳይሬክተሮችና ሃላፊዎች በብቃታቸው ሳይሆን የፖለቲካ ወኪል ሆነው ስለሚሾሙ ትምህርት ላይ ከባድ ችግር ጭነውበታል። ትምህርት ነጻነት ያየለበት ከባቢ ይፈልጋል። ፖሊሲን በተመለከተ ኢትዮጵያን ማእከል ያደረገና ከዘመኑ የአለም ስልጣኔና እውቀትን ያገናዘበ ሆኖ በባለሙያዎች መቀረጽ ይኖርበታል። ትምህርት የፖለቲካ ማስፈጸሚያ ሆኖ ከተቀረጸ የዛሬውን ትውልድ ብቻ ሳይሆን ያለፈውን ታሪካችንን ሁሉ እንደገዢዎቹ ፍላጎት ስለሚያዛባው እጅግ አደገኛ ይሆናል፣ ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል ማለት ነው።

 

፫. የመምህሩ ኑሮ የማሸነፍ አቅም መዳከም

መምህሩ የሚያገኘው ደመወዝና ጥቅማጥቅም በጣም ዝቅተኛ በመሆኑ ኑሮውን ለማሸነፍ ሲል ባተሌ ይሆናል። ይህ ጉዳይ ደግሞ ዞሮ ዞሮ በትምህርት ጥራት ላይ ከፍተኛ አሉታዊ  ተጽእኖ ይኖረዋል። ስለዚህ መንግስት የመምህራንን ኑሮ ለማሻሻል ጠንክሮ ካልሰራ የትምህርት ጥራት አያድግም።

 

፬. የትምህርት ቤቶች መርጃ መሳሪያዎ አለመሟላትና የመምህሩ አቅም ግንባታ ስራ ማነስ

ትምህርት ቤቶች በመርጃ መሳሪያዎችና በብቁ መምህራን መታጠቅ አለባቸው። መንግስት ትኩረት ሰጥቶ ለመምህራን ተገቢውን ትምህርት መስጠት ይገባዋል። በአሁኑ ጊዜ በሳይበሩ  አለም ውስጥ ብዙ እውቀት ስላለ መምህሩን ከዚህ ጋር በማገናኘት በየጊዜው ራሱን በዋለበት ሙያ እንዲያሳድግ ያስፈልጋልና መንግስት ተገቢውን ድጋፍ ሊያደርግ ይገባል። መርጃ መሳሪያዎችን በተመለከትም መንግስት ትኩረት ሰጥቶ ትምህርት ቤቶችን ሊያግዝ ይገባል። ይህ ካልሆነ ትምህርት አያድግምና።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከአ.ህ.ኢ.ን በአማራ ወገኖቻችን ላይ ተጠናክሮ የቀጠለውን መንግስት መራሹን ሰቅጣጭ የዘር ፍጅት ወንጀል በተመለከተ የተሰጠ የአቁዋም መግለጫ

 

፭. የሃገሪቱ የፖለቲካ አለመረጋጋት

በቅርቡ ትምህርት ሚንስቴር ባወጣው ሪፖርት ብዙ ሰው ተደናግጦ ይታያል። ትክክል ነው። ነገር ግን በጦርነትና በፖለቲካ ቀውስ ምክንያት እጅግ ብዙ  ተማሪዎች ደግሞ ለፈተናም   አልቀረቡም። በትግራይ ሙሉ በሙሉ ትምህርት ቆሟል፣ እጅግ ብዙ ዜጎች ተፈናቅለው ትምህርት አቋርጠዋል። ትምህርት ያለባቸው አካባቢዎች ደግሞ መረጋጋት ስለሌለ በትምህርት ላይ ከፍተኛ ጥቁር ጥላ ጥሎበታል። ስለዚህ የፖለቲካ መረጋጋት ይመጣ ዘንድ ያስፈልጋል። የተረጋጋና ሰላማዊ ህይወትን ለማህበረሰቡ ለማጎናጸፍ፣ ጦርነት ናፋቂና የርስበርስ ግጭትን ፈጣሪ ከሆነው ከዘር ፖለቲካ ሲስተም ተላቀን ወደ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ስርዐት ለመሸጋገር አጥብቀን ልንታገል ይገባል።

 

፮ የተማሪዎች የኑሮ ሁኔታ

ተማሪው በድህነት የከፋ ችግር ላይ ሲወድቅ በትምህርቱ ላይ የሚኖረውን ተጽእኖ መገመት ቀላል ነው። በከፍተኛ ረሃብና ጉስቁልና ውስጥ ያሉ የሃገራችን ወጣቶችና ህጻናት ትምህርታቸውን  በትኩረት ለመከታተል ያስቸግራቸዋል። ልጆች የእለት ጉርሳቸውን ለማግኘት ሲሯሯጡ የትምህርት ጊዚያቸው ይባክናል።  ስለሆነም መንግስት በየአካባቢው ያሉ ድሆችን የሚደጉምበት ሁኔታ መፈጠር አለበት። በአንዳንድ ትምህርት ቤቶች የተጀመረው ምገባ መልካም ነገር ሆኖ ነገር ግን ይህ ፕሮግራም እንዲስፋፋ  ያስፈልጋል።

 

በመጨረሻም ሃገራችን ኢትዮጵያ በዚህ ወቅት ያለችበት የትምህርት ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ በመሆኑ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ለትምህርት ትኩረት እንዲሰጥ፣ በሃገሪቱ ውስጥ ፖለቲካዊ ለውጥ  መጥቶ የተሻለ ሽግግር በመፍጠር ለትምህርት ትኩረት ሰጥተን ብቁና ችግር ፈቺ የሆኑ ዜጎችን እንድናፈራ ጥሪ እናደርጋለን።

 

ኢትዮጵያችን _ለዘላለም _ትኑር!

የኢትዮጵያ፤የውዪዪትና፤መፍትሔ፤መድረክ

Ethiopian Dialogue Forum

9900 Greenbelt RD.  E#343 –  Lanham, MD 20706

 

1 Comment

  1. የትምህርቱ ጥራት እንዲለወጥ ብርሃኑን መለወጥ ነው ቦታው ሃገር ግምባታ እንጂ ተክለ ሰውነት የሚገነባበት ልምድ የሚያካብቱበት እርሶ የሚባልበት ሊሆን አይገባም፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share