December 10, 2022
18 mins read

አደገኛ የበግ ለምድ ለባሽ ቀበሮዎችን የማይፀየፍ ትውልድ

lemd

December 10, 2022
ጠገናው ጎሹ

ዳንኤል ክብረት ማህበር ከተሰኘ ማህበራዊ ሚዲያ ጋር ያደረገውን ቃለ ምልልስ በጥሞና ተከታተልኩት ።
lemdቃለ ምልልሱን በጥሞና የተከታተልኩት እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት የቆጠረውን ፊደል  ፣ ያነበበውንና የሚያነበውን ንባብ እና የቃረመውንና የሚቃርመውን ተረትና ምሳሌ ጥሩ አድርጎ ባሰለጠነው አንደበቱ እያዥጎደጎደ ሲፈልግ ትናንት የተናገረውን ዛሬ ከሚለው ጋር በቀጥታ እያላተመ  እመኑኝ ሲል ፈፅሞ ምንም የማይመስለው፣ እና ለምንና እንዴት ተብሎ ሲጠየቅ ደግሞ “አይ እናንተ ስላልገባችሁ ነው እንጅ ማለት የፈለግሁት እኮ …”  በሚል በህዝብ መሠረታዊ ግንዛቤ (እውቀት) ላይ ሊሳለቅ ሲሞክር ጨርሶ ህሊናውን የማይኮሰኩሰው ግለሰብ የተለየ በጎ የፖለቲካ፣ የሞራልና የመንፈስ ሰብዕና ተላብሶ ይመጣል የሚል እምነት ስለነበረኝ አይደለም።

ይህ ማለት ግን እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት የአስመሳይነትና የአድርባይነት ልክፍተኞችን እንደ ልማደኛ እየቆጠሩ ማለፍ ያስፈልጋል ማለት አይደለም። የእንዲህ አይነት ግለሰቦችን  አስተሳሰብና አካሄድ በጥሞና እየተከታተሉ ቢቻል ከተዘፈቁበት ክፉ የቤተ  መንግሥት ፖለቲካ አባዜ ራሳቸውን እንዲታደጉ፣ ካልሆነ ግን ጊዜና ሁኔታ አምጦ በሚወልደው ህዝባዊ እምቢተኝነት ተገደው ገለል እንደሚደረጉ በግልፅና በቀጥታ መንገር  የግድ ነውና።

አዎ! በሰአብዊ ፍጡርነት ካባ/ለምድ ተጀቡነው (ተሸፍነው) የዛሬን ብቻ ሳይሆን የነገ እጣ ፈንታውን የመከራና የውርደት እያደረጉበት ያሉትን እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት ተኩላዎች ከምር ለመፀየፍና በቃችሁ ለማለት የተሳነው ትውልድ የዴሞክራሲና የዴሞክራሲያዊት አገር ናፋቂ የመሆኑ እንቆቅልሽ በእጅጉ አስከፊና አስፈሪ በመሆኑ በእጅጉ ሊያሳስበንና ተገቢውን ሁሉ ለማድረግ ከምር ሊያነሳሳን ይገባል።

ለዘመናት የመጣንበትና አሁንም እጅግ አስከፊ በሆነ ሁኔታ የምንገኝበት ሸፍጠኛ፣ ሴረኛና ጨካኝ የጎሳ ጥንት ስሌት ፖለቲካ  ቁማርተኞች (ነጋዴዎች) ሥርዓት ማብቃትና በእውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መተካት ካለበት እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት ህሊናቸውንና አንደበታቸውን ለእኩይ ተግባር አሳልፈው የሸጡና የሚሸጡ ወገኖች በግልፅና በቀጥታ በቃችሁ መባል ይኖርባቸዋል።

እንደ ገና ልድገመውና ቃለ ምልልሱን የተከታተልኩት ከእንደ ዳንኤል ክብረት አይነት መስሎና አስመስሎ በመኖር እኩይ ሰብእና ከተካነ “ሙዓዘ ጠበባት”  በጎ ነገር ይገኛል በሚል ተስፋና እምነት በፍፁም አይደለም።  ይህንን ለመረዳት ዳንኤል ክብረት የሸፍጠኛ፣ የሴረኛና የጨካኝ ተረኞችን የቤተ መንግሥት ፖለቲካ ከተቀላቀለበት ጀምሮ የሆነውንና ያደረገውን ከምር ልብ ማለት ብቻ በቂ ነው።

አዎ! የዳንኤል ክብረት እጅግ አሳሳችና አደገኛ ፖለቲካዊ ፣ ሞራልዊና መንፈሳዊ ሰብእና ትዕሥትን የሚፈታተን ቢሆነም በጥሞና ለተከታተለ ሰው ገና ለቃለ ምልልስ ሊቀርብ ነው ወይም የአደባባይና የአዳራሽ ውስጥ ዲስኩር ሊደሰኩር ነው ሲባል ምን  ሊል  እንደሚችልና  እንዴት  ሊለው  እንደሚችል  ለመገመት  ብቻ ሳይሆን  ለማወቅም  አያስቸግርም   አዎ! አገረ ኢትዮጵያን ለዘመናት ከኖረችበት የመከራና የውርደት አዙሪት እና  ከአራት ዓመታት ወዲህ ደግሞ በተረኛ ኦህዴዳዊያን/ኦነጋዊያን ከገባችበት እጅግ ለማመን የሚያስቸግር ምድረ ሲኦልነት መውጣትና ዴሞክራሲያዊት አገር ማድረግ ካለብን እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት እጅግ ወራዳና አዋራጅ ወገኖችን አስተሳሰብና አካሄድ በተመለከተ አካፋን አካፋ በሚል ደረጃ  መነጋገር ይኖርብናል ።

እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት ወገኖች ፍርፋሪ የሚወረውሩላቸውን እኩያን የቤተ መንግሥት ጌቶቻቻውን ያስደስትልናል ብለው ካመኑ ሃሰቱን እውነት፣ ኩነኔውን ፅድቅ፣ የግፍ ግድያን የግጭት ጉዳይ፣ ኢፍታዊነትን ፍትሃዊነት፣ የሰብእና ታናሽነትን ታላቅ ሰብእና፣ ኢሞራላዊነትን ሞራላዊነት፣ ጦርነትን ሰላም፣ ርሃብን ጥጋብ፣ ቁልቁል መውረድን ከፍታ፣ ውድቀትን ትንሳኤ ፣ ሲኦልን ገነት፣ ውድመትን የልማት ትሩፋት ፣ እስርና እንግልትን ህግ ማስከበር ፣ የታሪክ አተላነትን የታሪክ አርበኝነት ፣ ገዳይነትንና አስገዳይነትን የአገር ባለውለታነት ፣  ወዘተ አድርገው በማቅረብ “እውነት እውነት እንላችኋለን እመኑን” ሲሉን ጨርሶ ህሊናቸውን አይኮሰኩሳቸውም ።

ይህ እጅግ አስከፊ ምንነታቸውና ማንነታቸው በእውነተኛ ነፃነትና ፍትህ ፈላጊ ወገኖች የተጋለጠባቸው መስሎ ሲታያቸውና የሚጣልላቸው የአድርባይነት ፍርፋሪ አደጋ ላይ የሚወድቅ ሆኖ ሲሰማቸው ደግሞ  የአገር ተደፈረች እሪታቸውንና ውግዘታቸውን ያለ ምንም ሃፍረት የሚያዥጎደጉዱ እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት እጅግ አደገኛ ግለሰቦች ከሚተራመሱበት የፖለቲካ አውድ እንኳንስ እውነተኛውን አምላክ “ለዘብተኛውን ሰይጣንም” ፈልጎ ማገኘት ፈፅሞ አይቻልም።

“ዲያቆን እና ሙዓዘ ጥበባት” የተሰኙ የማዕረግ ቅፅሎቹን የገደፍካቸው (የተውካቸው) በስህተት ነው ወይስ  ? ብለው የሚጠይቁ ወገኖች እንደሚኖሩ እገምታለሁ። ጥያቄውም ተገቢ ነው።

ለዚህ የሚኖረኝ መልስ የመርሳት ጉዳይ ሳይሆን እንደዚህ አይነት እጅግ ሰፊና ጥልቅ የሆኑ ትርጉሞችና እሴቶች ያላቸውን የሙያና የእውቀት ባለቤትነት ማዕረግ መጠሪያዎችን እንደ ዳንኤል ክብረት ለመሰሉ እጅግ በተበላሸና አደገኛ በሆነ የፖለቲካና የሞራል ሰብእና ለተለከፉ ወገኖች መጠቀም ቅዱስና ርኩስ ነገሮችን የመቀላቀል ያሀል መስሎ ስለሚሰማኝ ልጠቀምባቸው አልፈለግሁም የሚል ነው። ይህንን አባባሌን በየዋህነትም ሆነ በማወቅ የዳንኤል ክብረትና የመሰሎቹ የማስመሰልና የአድርባይነት ሰለባዎች የሆኑ ወገኖችን ስሜት በማይጎረብጥ አገላለፅ ብገልፀው ደስ ባለኝ ነበር። ይህ ግን ለምድሩም ሆነ ከሞት በኋላ ተስፋ ለሚደረገው ህይወት ፈፅሞ አይጠቅምምና አላደረግሁትም።

አዎ! በእውነት ስለ እውነት ከተነጋገርን ጥልቅና የተቀደሰ ትርጉም የተሸከሙ የማዕረግና የሙያ መጠሪያ ፅንሰ ሃሳቦችን (ቃላትን) እናት ምድርን ለንፁሃን ልጀቿ ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ ሁኔታ ምድረ ገሃነም/ሲኦል ላደረገና በመድረግ ላይ ለሚገኝ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ቁማርተኞች ሥርዓት ታማኛ አማካሪ (አገልጋይ) ለሆኑ እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት ወገኖች መጠቀም የራስን (የሰብአዊ ፍጡርነትን) መሠረታዊ  ማንነትና ምንነት ብቻ ሳይሆን  አምላክን ራሱን በአስከፊ ወንጀል የተዘፈቁ ፖለቲከኞች ተባባሪ ማድረግ ነው የሚሆነው።

“ዳንኤልና መሰሎቹ በሠሩት ራሳቸው ይጠየቃሉ እንጅ ትውልድ ምን አደረገና ነው…? ” የሚል ጥያቄ ሊነሳ እንደሚችልም እገምታለሁ። ለዚህ ያለኝ መልስ በሥልጣነ መንበር ላይ እየተፈራረቁ  መከረኛውን ህዝብ የመከራና የውርደት ናዳ ያወረዱበትንና እያወረዱበት የቀጠሉትን እኩያን ገዥ ቡድኖችን እና እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት እጅግ ሃሰተኛ፣ ነውረኛ፣ ህሊና ቢስ፣ እና ጨካኝ አድርባይ አሽከሮቻቸውን ፈፅሞ ለመፀየፍ እና የነቃ፣ የተደራጀና የተቀናጀ ትግል ለማካሄድ የተሳነው ትውልድ ሃላፊነቱን አልተወጣምና ራሱን መመርመር ይኖርበታል የሚል ነው።

አዎ! እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት የተቀደሰውን ሃይማኖታዊ እምነት ከለየለት የሸፍጠኞች፣ የሴረኞችና የጨካኞች የፖለቲካ ሥርዓት አማካሪነታቸው ጋር እያቀላቀሉ ህዝብን ፍፃሜ ያጣ የመከራና የውርደት መናኸሪያ (ሰለባ) እንዲሆን ሲያስደርጉ  በቃችሁ ለማለት የተሳነው ትውልድ የትኛውን ዴሞክራሲና የትኛዋን ዴሞክራሲያዊት አገር እንደሚናፍቅ ለመረዳት የሚቻል አይመስለኝም።

ምንም እንኳ ዳንኤል ክብረት በቃለ ምልልሱ ለተነሱ ጥያቄዎች ለመመለስ የሄደባቸው መንገዶች ሁሉ የራሱን ግዙፍና ግልፅ የፖለቲካና የሞራል ሰብእና ውድቀት ከመግለፅ ያለፈ ፋይዳ ባይኖራቸውም አንድ ጉዳይ ግን ባይገርመኝም በእጅጉ አሳዝኖኛል። ያሳዘነኝ ዳንኤል ክብረት ስለ ተናገረው ሳይሆን ዘመን ጠገቡና ማቆሚያ ያጣው የዚህ ትውልድ ውድቀት እንቆቅልሽ መቸና እንዴት ነው የሚፈታው? የሚለው ጥያቄ እንኳንስ አመርቄ የሆነ በቅጡ ስሜት የሚሰጥ መልስ ሳያገኝ የመቀጠሉ ግዙፍና መሪር እውነት ነው።

ዳንኤል ክብረት “እውነትን የማውቀው በማውራት ወይም በመናገር ሳይሆን በመኖር (ሆኖና አድርጎ በመገኘት ነው)” በሚል በመከረኛው ህዝብ መሠረታዊ ግንዛቤ (እውቀት) ላይ እጅግ ርካሽና ጨካኝ ስላቅ ሲሳለቅ “ለነውረኝነትህና ለንቀትህ ገደብ ይኑረው!” ለማለት ፖለቲካዊና ሞራላዊ ልእልና የሚሳነው ትውልድ እጣ ፈንታው የሸፍጠኞች፣ የሴረኞችና የግፈኞች ፖለቲካ ሥርዓት እና የግብረ በላዎቹ ሰለባ ሆኖ ቢቀጥል ያሳዝን እንደሆነ ፈፅሞ አይገርምም!

ውድ አገር ወዳድ ወገኖች ሆይ! ይህንን የዳንኤል ክብረትን “የእውነተኝነት ሰብእና” ዲስኩር በሚሊዮኖች የግፍ አሟሟት፣ በብዙ ሚሊዮኖች የቁም ሰቆቃ እና በአጠቃላይ በመከረኛው ህዝብ ሁለንተናዊ ጉስቁልና ላይ ለተሳለቀውና በመሳለቅ ላይ ለሚገኘው ጠቅላይ ሚኒስትር ተብየ  የቅርብና ታማኝ አማካሪ ከሆነው ዳንኤል ክብረት ግዙፍና መሪር እውነታ ጋር ከምር ተመልከቱት!!!

እንደ አገር መሪነቱና የንፁሃንን መከራና ሰቆቃ ቢያንስ በሰብዊነት ስሜት እንደሚረዳ ሰው “በሆነው ሁሉ እያዘንኩ ይህ አስከፊ ውድቀት ይቆም ዘንድ ሃላላፊነቴን  ለመወጣት ጥረት እንደማድርግ አረጋግጣለሁ” ለማለት የፖለቲካና የሞራል አቅም ፈፅሞ የሌለውን አብይ አህመድን የኢትዮጵያ ስም ሲጠራ በእንባ ጎርፍ እንደሚታጠብ ሲነግረን ከንፈራችን እየመጠጥን እንድናምነው የከጀለን እኮ ሌላ ዳንኤል ክብረት ሳይሆን ዛሬም የመፀፀትና የመታረም ሰብእና ፈፅሞ የሌለው ዳንኤል ክብረት ነው።

የራሱን እጣ ፈንታ በነፃነት ለመወሰንና ለመኖር የሚያስችለውን  የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ሽግግር ትግሉን እየቀለበሱ ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ  (ከመቃብር ሙትነት ባልተሻለ ) ሁኔታ የመከራና የውርደት ናዳ የሚያወርዱበትን ሸፍጠኛ፣ ሴረኛ፣ ባለጌና ጨካኝ ገዥ ቡድኖችንና እንደ ዳንኤል ክብረት አይነት ግብረበላዎቻቸውን ከምር ለመፀየፍና በቃችሁ ለማለት በአስፈሪ ሁኔታ ወኔው የከዳው ትውልድ መቼና እንዴት ከተለከፈበት የምንነትና የማንነት ቀውስ ሰብሮ ሊወጣ እንደሚችል እንኳን ለማመን ተስፋ ለማድረግም  በእጅጉ ይከብዳል  ።

ይህ ትውልድ ከዚህ ክፉ አዙሪት ሰብሮ መውጣት ካለበት  በአንድ እጃቸው  መጽሐፍ ቅዱስ እና በሌላው እጃቸው   ደግሞ በንፁሃን ደም የጨቀየ የፖለቲካ ሰነድ  ተሸክመው  የመዳን ቀን አሁን ነውና  ንስሃ እየገባችሁ ተደመሩ የሚሉንን ዳንኤል ክብረቶችን  በቀጥታና በግልፅ በቃችሁ ማለት የግድ ነው!

እናም ልብ ያለው ልብ ይበልና አደገኛ የበግ ለምድ ለባሾችን በቃችሁ ይበል!!!

5 Comments

  1. ጠገናው ጎሹ “በየበግ ለምድ ለባሽ ቀበሮዎች” ጽሁፋቸው ዲያቆን ዳንዔልን የተሳደቡበት ያንቋሸሹበት እና እሱን ባልተሳደብነው ሰዎች ላይ ብስጭታቸውን የገለፁበትን ጽሁፍ አነበብኩ ፡፡ ስለዳንዔል ዳንዔል ይመልስ ፡፡ እሱን በቃህ ስለማይለው ዜጋ ግን ይገደኛል፡፡ ዳ/ን ዳንዔል ያገኘውን መዐረግ ያገኘው በስራው መሆኑን ስለማምን የሚቃወሙት ን አልደግፍም: የጠቅላዩ አማካሪ የሆነው ጠቅላዩ ስለጠየቁት ከሩቅ ሆኖ ከማለቃቀስ ከመተቸት ከመሳደብ ያገኘውን ዕድል ተጠቅሞ በመቅረብ ባመነበት እና በሚችለው አገሩን ለመታደግ እንጂ ስልጣን ወይም አንዳች ቁሳዊ ፍላጎት ሽቶ አለመሆኑን ስለማምን ከሁሉም በላይ ከብዙዎች የተሻለ ስላነበበ ስላየ እና ሰለፃፈ በሚከተለው አሰራር ስለማሞነው ነው፡፡ እርስዎም የጦርዎን አቅጣጫ ከዳንዔል ይልቅ ወደ ጠላት ያድርጉ፡፡ ዲ/ን ዳንዔል በሚያምንበት መንገድ እየሰራ ነውና፡፡

    • ሰላቶው ሃይለ ሚክዔል አንድም ራሱ ወለወልዳው ዳንዔል አለዚያም እርሱን መሳይ ባንዳ ነህ፡፡ ለዚህም ማስረጃው “ስለዳንዔል ዳንዔል ይመልስ ፡፡” ብለህ አራት ነጥም ታስቀመጥክ በኋላ ወለወልዳውንና ባንዳውን ዳንዔል መከላከል ጀመርክ፡፡ ሌላ የምለው የለም፦ ዳንዔል ወይም አንተ እንደ ደምፅ ማጉያ በምታገለግሏቸው አውሬዎች በመላ አገሪቱ የሚፈሰው የአማራ ደም በምድርም በሰማይም ይፋረድህ፡፡

  2. ዳንኤል ክብረት ከመንፈሳዊ ተግባሩ እርቆ ፖሊቲካውን በማሳከርና ለስጋዊ ፍላጎቱ እራሱን ለማስገዛቱ በተከታታይ የሰጠው ዲስኩር በእስላሞች መድረክ ተጋብዞ ከዚህ በፊት የጻፍኩት ሁሉ ሃሰት ነው ብሎ እነሱን ለማስደስት መናዘዙን አሁን ደግሞ ቅኝቱን ከአራጅ ኦሮሙማ ጋር መቃኘቱን ስናገናዝብ በኢትዮጵያ ባህል አቶ ዳንኤል ብለው እንጠራው ካልሆነ ዲያቆን ዳንኤል ወይም ሙአዘ ጥበባት የሚል የቤተ ክርስቲያን የክብር መጠሪያ የሚገባው አይመስልም፡፡ ይህን አስመልክቶ አንባቢ ሃሳብ እንዲሰጥበት እንጠይቃለን፡፡ መሰረታዊ እምነቱን ጥሎ ዛሬ በአራጆች ቅኝት ከተጓዝ የንጹሃንን ጭፍጨፋ ደሞዝ ከፋዮቹን ፈርቶ ካላወገዘ ነገ እስራኤል ዳንሳ ወይም ዮናታን አክሊሉ አይጸልዩለትም ወይም ሁሉን እርግፍ አድርጎ ወደነሱ አይቀላቀልም ብሎ ለመገመት ይቸግራል፡፡ ሰው የሚበላው ሳያጣ እንዲህ እራሱን አሽቀንጥሮ ይጥላል? ሰይጣን እየጋለበው ስለሆነ የቤተ ክርስቲያንን ምስጢራት እንዳያባክን የቤተክርስቲያን በሮች ለእርሱ ክፍት ባይሆኑ መልካም ነው፡፡

  3. ልጅ Hailemichael;
    ዳንኤል ክብረትንና መሰሎቹን አስመልክቶ በሰጠሁት ሂሳዊ ትችት ላይ በተረዳኸው ፣ ባመነክበትና አቋም በያዝክበት መጠን አስተያየት በመስጠትህ አመሰግናለሁ ።
    ይህ አባባሌ መሪሩን እውነት ለመጋፈጥና ቢቻልም የጋራ ግንዛቤ ለመፍጠር የሚደረግ የሃሳብ (የአስተሳሰብ) ልዩነትና ፍጭት መለመድ ያለበት የፖለቲካ ባህል እንደሆነ ካለኝ እምነት የሚነሳ ነው።
    በሌላ በኩል ግን ፦
     የተጠቀምኩባቸው ቃላትና ሀረጎች በዳንኤል የግል ሰብእና ላይ ሳይሆን አገርን ምድረ ሲኦል እያደረገ በቀጠለ የእኩያን ገዥ ቡድኖች ቤተ መንግሥት አማካሪነቱ (ፍርፋሪ ለቃሚነቱ) መሆኑ አሁንም ግልፅ ይሁንልኝ፣
     ለዚህ ደግሞ በመሬት ላይ እየሆነ ያለውን መሪር እውነት እና የዳንኤልን ልክ የለሽ የቅጥፈትና የአሽቃባጭነት የፖለቲካ ሰብእና ልብ ማለት ብቻ በቂ ነው። ህዝብ ማለት እንዲህ አይነቱን ግዙፍና መሪር እውነታ የማይገነዘብ የሰዎች ስብስብ ነው ካላልን በስተቀር አራት ዓመት ሙሉ የሆነውና አሁንም የቀጠለው የዳንኤልና የመሰሎቹ የፖለቲካና የሞራል ዝቅጠት ይኸው ነው፥
     አገርን አገረ ሲኦል እያደረገ ለቀጠለው የሸፍጠኞች፧ የሴረኞችና የጨካኞች የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ሥርዓት ህሊናውን አሳልፎ በርካሽ የሸጠውን ዳንኤልን ከገባበት የነውርነትና የውርደት አዘቅት እንዲወታ በግልፅና በቀጥታ መንገርና መናገር ከተራ ስድብ ጋር ፈፅሞ ግንኙነት የለውም፣ ይህ ስድብ ነው ለሚል ወገን ያለኝ መልስ ከሆማ ይሁን (If you say so, so be it) የሚል ነው።

  4. በፍሬው* የተያዘው ማኅበረ ቅዱሳን

    ሴቶች ከወንድ ልጅ ጋር ሲደባደቡ ወንዱን ልጅ እንደምንም ብለው ፍሬውን ለመያዝ ይሞክራሉ። ከዚያ በኋላ ምንም ምርጫ የለውም ጸጉሯንም ይዟት፣ አንገቷንም አንቋት ከሆነ ይለቅቃል።

    እነ አቢይ አህመድ ዳንኤል ክብረትን በኦነጉማ ጉያ ውስጥ ሲይዙ በቤተክርስትያን ውስጥ ትልቅ ኃይል የሆነውን ማኅበረ ቅዱሳንን በፍሬው እንደያዙት መገንዘብ ይቻላል። ቤተክርስትያን ቢቃጠል፣ ምእመናን ቢጨፈጨፉ፣ የተዋሕዶ ልጆች ከሥራ ገበታ ቢገፉ፣ ከመንግሥት መዋቅር ቢራገፉ ዝም! ጭጭ! የተማረ የሰው ኃይል አለው፣ ገንዝብ አለው፣ ሚዲያዎች አሉት። ወይ ትንፍሽ፣ ወይ ንቅንቅ!

    እርግጥ ወያኔ ራሷ የሰለበችውን ተቋም የትግራይ ልጆች “ስንጨፈጨፍ ምንም አላለም” ብለው ቢከስሱት ወይ የግንዛቤ እጥረት ነው ወይም ድርቅና ነው። ከዝምታ አልፎ ተርፎ ግን የተቋሙ ፍሬ የጦርነት እምቢልታ ነፊ ሲሆን ተቋሙ ራሱን ለማራቅ አልፎም ለማውገዝ አለመቻሉ ተቋሙ የተሽመደመደበትን ደረጃ እና እውነትም በፍሬው የመያዙን ጉዳይ የሚነግረን ነው።

    ብልጽግና የቁማር ሞተሩ ነክሶ በቸርኬው ሊቆም ሲል በዙፋን ላይ ያለውን ዝገት ለማራገፍ መጀመሪያ አፈር የበላቸውን፣ የላስቲክ ሽፋናቸው ተቦጫጭቆ በድድ የቀሩ ጎማዎቹን መወልወል ፈልጓል። እነዚህ የኦነግ/ብልጽግና ጋሪ ዋና ዋና ጎማዎች ኢዜማ፣ ዳንኤል ክብረት፣ አብን ወዘተ መሆናቸውን ማንም አይስተውም። በዚህም መሠረት የዙፋኑን ክብር ከገባበት ቅሌት ለመመለስ መጀመሪያ እነዚህን ዝገውና ተቦተራርፈው እያስቀየሙ ያሉና የነከሱ ጎማዎቹን ማሳደስ ፈልጓል። ለዚህም ነው ሲያስጠቁት የከረሙትን የሕዝብ አጀንዳ ቀምተው በመግለጫ እንዲያራግቡ የተፈቀደላቸው። የኢዜማና አብንን ሰሞነኛ አስመሳይ መግለጫዎች ማስተዋሉ በቂ ቢሆንም የሌላውን (ጎማው ተገንጥሎ በቸርኬ የቀረውን) አካል የዳንኤልን ክብረትን ሕዳሴ እንይ።

    ለዚህኛው የዙፋን ቸርኬ እድሳት በሚሌንየም አዳራሽ ጉባኤ ማዘጋጀት ድረሰ ተኪዷል። በወለጋ ጫካ እስላም ክርስትያኑ በኦነጋውያን (መንግሥትና ሸኔ) ቅንጅት እየተጨፈጨፈ፣ የአጀንዳ ማስለወጫ ብቻ ሳይሆን እባቡ ቆዳውን ገፍፎ ባዲስ ቆዳ እንዲከሠት የማድረግ ወራዳ ሥራ ተሠርቷል። በጨፍጫፊው የአቢይ አህመድ መንግሥት ውስጥ በዝምታም ሆነ በትብብር ስላደረገው ተሳትፎ ይቅርታ ሳይጠይቅ፣ በምእመናን ላይ፣
    በቤተክርስትያኒቱም ላይ፣ በቤተክርስትያኒቱም አባት ላይ ስለሰነዘረው ጥቃትም ንስሐ ሳይቀበል፤ ዳንኤል በቤተክርስትያን ስም መድረክ ተዘጋጅቶ በእምነትና በሕዝቡ ላይ እንዲያፌዝ መፈቀድ አልነበረበትም።

    መጀመሪያም ቢሆን በቅድሚያ ሰላማቸው እንዲረጋጋ ሳይሠራ፣ በአሁኑ ሰዐት በሸኔ ቁጥጥር ሥር በሆኑ የኦሮሚያ ዞኖች በቤተክርስትያን እድሳትና ማቋቋም ስም ከምእመናን ገንዘብ ሰብስቦ መላኩ በራሱ ሸኔን በገንዘብ ከማጠናከር ተግባር ተናንሶ የሚታይ አይደለም። የሚያስጠረጥር ጉዳይ ነው። በተለይ አሁን ሸኔ ውንብድናው ከፍቶ ድሆች እያገተ እስከሚሊዮን ድረስ በሚጠይቅበት ጊዜ። የገንዘብ ማሰባሰቡ ይደረግም ከተባለ ድርጊቱ ለነዳንኤል ክብረት ስም ማደሻ ከመሆን ይልቅ በተከበሩ አባቶች ተመርቶ በቤተክርስትያን ወይም በቤተክህነት ቢደረግ ተሻይ ነበር።

    ዓላማው ግን (ዳንኤል ጽፎለት አቢይ እንዳነበበልን የንሥር አሞራ ታሪክ) የንሥሩን ጥፍሮችና የንሥሩን መንቆር የማደስና የመሳል ዓላማ ነው።

    ፍሬው = የወንድ የዘር ፍሬ
    ፍሬው = የኦነግ ሊቀመንበር የዳውድ ኢብሳ ስም

Leave a Reply

Your email address will not be published.

balege
Previous Story

በኦሮሚያ እና ቤንሻንጉል ክልሎች ንፁሀን የአማራ ተወላጆች ላይ ለሚደርሰው ተደጋጋሚ የዘር ጥቃት መንግሥት ለምን ደንታ-ቢስ ሆነ?

abn
Next Story

በአዲስ አበባ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop