የአውሮፕላን ጠለፋውና የኢህአዴግ ማዕከላዊ ኮሚቴ አስቸኳይ ስብሰባ (አጭር ወግ)

ከአዘጋጁ፡ ውድ አንባቢያን ይህ ጽሁፍ ከወሰንሰገድ ገ/ኪዳን በሚል የጸሐፊው ስም ወጥቶ ነበር። በኢሜይል ወሰንሰገድ ገ/ኪዳን በሚል የደረሰን በመሆኑ የጸሐፊውን ስም በቀጥታ መጠቀማችን ይታወሳል። አሁን ግን ይህን ጽሁፍ ወሰንሰገድ ገ/ኪዳን  የተባለው ጋዜጠኛ የኔ ጽሑፍ አይደለም፤ ሲል ገልጿል። በመሆኑም ጸሀፊው ወሰንሰገድ ገ/ኪዳን ጋዜጠኛው አለመሆኑና የዚህ ወግ ጸሐፊ ሌላ ሰው እንደሆነ ይታረምልን። በዚህ አጋጣሚ ለተፈጠረው ስህተት ጋዜጠኛውን ይቅርታ እንጠይቃለን-።   መልካም ንባብ፡

የኢህአዴግ አመራሮች ለአስቸኳይ ጉዳይ ቤተመንግስት ተጠርተዋል:: ሊቀመንበሩን የስብሰባውን አጀንዳ መናገር ጀመሩ::

እንደምታውቁት መጪው 2007 የምርጫ ጊዜ ነው:: እና ጠላቶቻችን ከአሁኑ ምርጫው ; ፓርቲው እና አገሪትዋ ላይ አደጋ ለማድረስ እየሞከሩ ነው:: ለዛ ምሳሌ የሚሆነው እና ዛሬ የተሰበብንበት ምክንያት ትላንት የተጨናገፈው የአውሮፕላን ጠለፋ ነው:: ፓርቲያችን እንደ ትላንት አይነቱ ጸረ-ልማት የሆነ ተመሳሳይ ተግባር እንዳይፈጸም ቅድመ ጥንቃቄ ማድረግ አለበት:: ለዚህም አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ ይጠበቅብናል::
በእዚህ አጀንዳ ላይ ያላችሁን አስተያየት ስጡና እንወያይበት::

አንዱ አመራር እጁን አወጣ:: እንዲናገርም ተፈቀደለት::

<<ሁሉም የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች ጋር ፌዴራል ፖሊስ መመደብ አለበት:: ለሚኒባስ ታክሲ አንድ ;ለአውቶቡስ ሁለት ከፊት እና ከኋላ ይመደብ:: ምንም እንኳን ኢኮኖሚ ው የሚጎዳ ቢሆንም መጪው ምርጫ ላይ ፈጽሞ አደጋ እንዲጋለጥ መፍቀድ የለብንም::>>
እሱ ተናግሮ እንዳበቃ ሌላኛው እጁን አወጣ::

<<ይሄ የጠለፋ ተግባር ጥልቅ ምርመራ ያስፈልገዋል:: የጠለፋ ወንጀል ጉዳቱ የከፋ ነው:: ለዚህ አደገኛ የአሽባሪዎች ስራ ሊጋለጡ የሚችሉ የህብረተስብ አካላቶችን ለይተን ማውጣት አለብን:: ከዚህ ቀደም በሌላ የጠለፋ ወንጀል እንዲሁም ስራ ላይ የተሰማሩ ሰዎችን ፖሊስ የቅርብ ክትትል ሊያደርግባቸው ይገባል:: ሴት የጠለፉ ; ሊጠልፉ ሲሉ የተያዙ ; ወይም የሴት ጠለፋቸው የከሸፈባቸው ሰዎች ፖሊስ የትኩረቱ አካላት ያድርጋቸው:: ጠለፋ እንደሌሎች ወንጀሎች ተዛማጅ ነው:: ከዚህም አንጻር የሀገር ቀሚስ ጠለፋ ላይ የተሰማሩ ሰዎች ለሴት ጠለፋ ወንጀል የተጋለጡ እንደሆነ ከዚህ በፊት የተደረገ ጥናት ያሳያል:: ስለዚህም ፖሊስ ጨርቆስ እና ሽሮሜዳ አካባቢ ያሉ ጥልፍ እና ቀሚስ ጠላፊዎችን ትኩረት ቢያደርግባቸው ክፋት ያለበት አይመስለኝም:: ታሞ ከመማቀቅ አስቀድሞ መጠንቀቅ እንዲሉ ለጠለፋ የሚያጋልጡ ቀዳዳዎች ን ሁሉ መድፈን አለብን::>>

ተጨማሪ ያንብቡ:  ያማራ ሕዝብ የሕልውና ትግል የመጀመሪያና የመጨረሻ ግቦች  

ሌላኛው ቀጠለ

<<ፓርላማው አሸባሪ ተብሎ ከፈረጃቸው ከእነ ግንቦት ሰባት እና አል-ሸባብ በተጨማሪ ጠላፊዎችን መጨመር ይጠበቅበታል:: ለዚህም ህግ አርቃቂው ኮሚቴ ህጉን እንዲያሻሽል ይደረግ::>>
ሌላኛው አከለ

<<ለጥንቃቄ ያህል ከእንግዲህ አይሮፕላኖቻችንን ማብረር ያለባቸው የፓርቲ አባላቶች ብቻ መሆን አለባቸው::በተለይ ከፍተኛ ባለስልጣኖች የሚጓዙበት አይሮፕላኖች በታማኝ አባሎቻችን መሆን አለባቸው:: አባል ያልሆኑ ፓይለቶች ሆኑ ኮፓይለቶች እንዲሁም ሆስተሶች አባል የሚሆኑበት መንገድ ይመቻች:: አድር ባይ እና ኪራይ ሰብሳቢ ያልሆኑ ሀቀኛ የአይሮፕላን ሰራተኞች ማፍራት ይጠበቅብናል:: አባል መሆን የማይፈልጉ ወይም ተቃዋሚ ፓርቲን የመደገፍ ዝንባሌ የሚያሳዩ ሰራተኞች ከስራቸው መሰናበት አለባቸው:: በምትኩም ታማኝ እና አንጋፋ አባሎቻችን የማብረር ትምህርቱ ተሰጥቷቸው ስራውን እንዲቀላቀሉ ይደረግ::>>

ሌላኛው የህወሃት አመራር እንዲህ አለ

<<ይሔ ጠለፋ የተካሄደው በጠላቶቻችን የተቀነባበረ ሴራ ነው:: ለካቲት 11ን የትግራይ ህዝብ እንዲሁም መላው የኢትዮጵያ ህዝብ በደስታ እንዳያከብር ለማድረግ ሆን ተብሎ የታሰበ ስለሆነ የህውሃት አባላት እና ደጋፊዎች እንዲሁም የብአዴን ; ኦህዴድ እና ድህአዴግ እንዲሁም አጋር ፓርቲዎች ጠለፋውን የሚያወግዝ ሰልፍ ህዝቡ እንዲወጣ የተለመደውን ቅስቀሳ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል::>> አለ

በስብሰባው መጨረሻ ፓርቲው ጠለፋውን የሚያወግዝ ጽሁፍ አውጥቶ እና ባለ ሰባት ነጥብ የአቋም መግለጫ ላይ በመወሰን አምራሩ ተበተነ::
በነጋታውም በከተማው የታክሲ እና አውቶቡስ ተሳፋሪ መጫኛ እና ማውረጃ ቦታዎች ላይ የፌዴራል ፖሊሶች ተመድበው ተሳፋሪው ጥብቅ ፍተሻ እየተደረገበት መሳፈር እና መውረድ ጀመረ::

Share