የማለዳ ወግ …ሳውዲ ጉዳይ – ዛሬም ድጋፍ በምድረ አሜሪካ – ዋሽንግተን ዲሲ !

ትናንት በሳውዲ ሰአት አቆጣጠር እኩለ ሌሊት ፣ በምድረ አሜሪካ ዋሽንግተን ከቀትር በኋላ እልፍ አዕላፍ ከሚቆጠሩት በምድረ አሜሪካ ነዋሪ ከሆኑ ኢትዮጵያውያን መካከል “የወገናችን ጉዳይ ያገባናል !” ያሉት ጥቂቶች በአለም አቀፉ እርዳታ አሰባሳቢ ቡድን በተጠራው Global Alliance የድጋፍ ማሰባሰቢያ ተገኝተው ነበር ። እኔም በሳውዲ ስላለው ነባራዊ ሁኔታ አጭር ንግግር እንዳደርግ በተጋበዝኩት መሰረት ዝግጅቱን በ Skype በእስካይፒ ተከታትየዋለሁና መረጃውን ላካፍላችሁ …
በትናንት ምሽቱ የድጋፍ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር ከተገኙት ታዋቂ ሰዎች መካከል የአለም አቀፍ ስደተኞች IOM የዋሽንግተን ዲሲ ተወካይ Mr. Luca Dall’Oglio, የክርስትና እምነት ተወካይ ዶር ቀሲስ አማረ ካሳ ፣ ከፕሮቴስታንት ፖስተር ዳንኤል ጣሰው ፣ ከእስልምና እምነት ተወካይ ሸህ ካልድ ኦመር እና የእርዳታ አሰባሳቢው ሊቀ መንበር ታዋቂው አክቲቪስት እና አርቲስት ታማኝ በየነ በድጋፍ ማሰባሰቢያው ተገኝተዋል ። እኒሁ ስመ ጥር ታዋቂ ተጋበዥ እንግዶች ለወገናቸው ያላቸውን የተቆርቋሪነት ስሜት የታየበት ንግግርም አድርገዋል።
እኔም በተያዘልኝ ሰአት በሳውዲ አረቢያ ስላለው ነባራዊ ሁኔታ አጥር ያለ ማብራሪያ ሰጥቻለሁ። እርግጥ ነው በአሁኑ ሰአት ሳውዲ አረቢያ የምንኖር ኢትዮጵያን በህገ ወጥነት የተፈረጁ ኢትዮጵያውያን ጉዳይ የበረደ የቀዘቀዘ ቢመስልም ዳሩ አሁንም መጭው አሳሳቢ ለመሆኑ የሰሞኑ ፍተሻዎች ጠቋሚ ናቸው ። ከሁሉም አስጊ የሆነው ያለ አሰሪዎች የሚሰሩት በህገ ወጥነት የተፈረጁበት እና በኮንትራት ስራ ስም በመላ ሳውዲ እንደ ጨው ተበትነው የቀሩት ዜጎች ይዞታ አሳሳቢ መሆኑን ለማስረዳት ሞክሬያለሁ። በአሁኑ ሰአት ወደ በተለያዩ የሳውዲ ከተሞች ሃገር ለመግባት እጃቸውን የሰጡ ዜጎች በየእስር ቤቱ ከወር በዘለቀ ጊዜ በእስር ላይ የሚገኙበትን ሁኔታ አሳሳቢነት እና በኮንትራት የመጡ ዜጎች እንግልትና በቀጣይ ጊዜያት በአስፈሪ አደጋ የተከበበ መሆኑን ግንዛቤ ለማስጨበጥ ጊዜው ባይበቃም አቅም የፈቀደውን መረጃ ለመስጠት ሞክሬያለሁ ።
በሳውዲ ኢትዮጵያውያን በደል ሲፈጸም በተለይም በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በዚህ መሰሉ ሰብዕና መሰረት ባደረገ አለምን ያስደመመ ህብረት ላደረጉት ተቃውሞ ሰልፍና ተጽዕኖን ፈጥረው በውጭ የሚኖሮ ኢትዮጵያውያን ታላቅ ውጤት አስገኝተዋል። በእርግጥም አለም አቀፍ ሰፊ ተቃውሞን በማድረግ ተጽዕኖ መፍጠር ባይቻል ኖሮ 180 ሽህ የሚደርሱ ዜጎችን በአጭር ጊዜ ወደ ሃገር ሊገቡ ይችሉ ነበር ብሎ መገመት ያዳግታል። ለዚህም ታላቁን ስራ በመስራቱ ረገድ ቀዳሚው ተመስጋኝ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ናቸው ። ዲያስፖራ የምንላቸው ። እውነት ነው ፣ በፖለቲካ ዘባተሎ የተለያየው ዲያስፖራ በሳውዲ ጉዳይ ልዩነትን አሰወግዶ በህብረት በመነሳቱ ትልቅ ስኬትን ለማየት በቅተናል። በወገኖቻችን ኮርተንባችኋልም! ያም ሁሉ ሆኖ በአሁኑ ሰአት ድጋፍ ለማሰባሰብ በሚደረገው ጥረት መለያየቱን ትተን በህብረት እንሰራ ዘንድ ባደረግኩት ንግግር በመማጸን ለተደረገልን ሁሉ አክብሮትን ከምስጋና አቅርቤያለሁ ።
በአለም አቀፉ እርዳታ አሰባሳቢ ቡድን Global Alliance የድጋፍ ማሰባሰቢያ ለሁለት ጊዜ ያህል ያሰባሰበውን ገንዘብ ለአለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት IOM ማስረከቡ አይዘነጋም !
በሰብዕና ወገን ለወገን እንዲህ ቀናኢ ሲሆን ያስደስታል ! ያኮራልም !
ቸር ይግጠመን !
ነቢዩ ሲራክ

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኮ/ል መንግስቱ ሃይለማርያም ዜና ምንጭ ወያኔ ነው
Share