በትዳርሽ ላይ የምትፈጽሚያቸው 5 ታላላቅ ስህተቶች (በተለይ ሴቶች እንዲያነቡት የተዘጋጀ)

ትርጉም ከኢሳያስ ከበደ

ደስተኛ ለመሆን የነደፍኩት ፕሮጀክት ከሚመለከታቸው አበይት ጉዳዮች መካከል አንዱ የትዳር ህይወቴ ነው፡፡ እንደ በርካታ ሰዎች ትዳር ለእኔም የሕይወቴ፣ የቤተሰቤና የደስታዬ ዋነኛ አላባዎች መካከል አንዱ ነው፡፡
ደስተኛ ህይወት ለመኖር የወጠንኩትን ፕሮጀክት ስጀምርና በህይወቴ መለወጥ ስለምፈልጋቸው ነገሮች ሳሰላስል በትዳሬ አምስት የተለያዩ ችግሮች እንዳሉብኝ ልገነዘብ ችያለሁ፡፡ ምንም እንኳን ፈታኝ ቢሆኑም፣ ችግሮቹና ልቋቋማቸው የነደፍኳቸው ስትራቴጂዎች ቀጣዮቹ ናቸው፡፡

1. ምስጋናና ሙገሳ መፈለግ
መቼስ፣ ምስጋናንና ሙገሳን የማይፈልግ ሰው በዚህች ምድር ማግኘቱ አስቸጋሪ ነው፡፡ እኔ ደግሞ የቤት ውስጥ ስራዬን በሰራሁ ቁጥር ከባለቤቴ ምስጋናንና ሙገሳን እጠብቃለሁ፡፡ በዚህ ረገድ ግን ባለቤቴ ደካማ መሆኑ ያናድደኛል፣ የሰራሁት ስራም ተቀባይነት ያላገኘ ይመስለኛል፡፡
ለዚህም ምላሽ እንዲሆን በአሁኑ ወቅት ይበልጡኑ ነገሮችን ለራሴ ብዬ ለመስራት እያሰብኩ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም፣ ‹‹መጻህፍቱን በየቦታው ማስቀመጤን ሲያይ ደስ ይለዋል››፣ እንዲሁም ‹‹መኪናዋን ለጉዟችን በሚያስፈልጉት እቃዎች በመሙላቴ ይደሰታል››፣ ወዘተ… በማለት ለባለቤቴ ጥሩ ነገሮችን እያደረግሁ እንደሆነ ለራሴ እነግረው ነበር፡፡ ሳያመሰግነኝ ሲቀር ግን በንዴት እጦፋለሁ፡፡ አሁን ግን እነኚህን ነገሮች የማደርገው እኔ ስለፈለግሁ እንደሆነ ለራሴ እየነገርኩት ነው፡፡ ይህንንም ተከትሎ ‹‹እንዴ፣ የማእድ ቤቱ መሳቢያዎች በሙሉ ጽዱ ሆነዋል!››፣ ‹‹አስቤዛችንን ሳያልቅ መግዛቴ ጠንቃቃ እንደሆንኩ ያሳያል!›› የሚሉትን የመሰሉ አስተያየቶች ለራሴ መናገር ጀምሬያለሁ፡፡ ነገሮችን ለራሴ ስል ስለማደርግ ባለቤቴ በማንኛውም መልኩ ምላሽ ይሰጠኛል ብዬ አልጠብቅም፡፡

2. ቆጣ ብሎ መናገር
በተፈጥሮዬ ግልፍተኛ በመሆኔ በቀላሉ ቱግ እላለሁ፤ ይሁንና ባለቤቴ በቁጣ አንደበት ስናገር ደስ አይለውም፡፡ ይህን ጻባዬን ለመቆጣጠር ብዙ ነገሮችን ሞክሬያለሁ፡፡ በጣም እሰኪርበኝና እስኪበርደኝ ድረስ አልጠብቅም (ከነኚህ ሁኔታዎች ላይ የምደርሰው በቀላሉ ነው) ምስቅልቅል ወይም ዝርክርክ ያለ ነገር ስለሚጨንቀኝ የምንኖርበትን አፓርታማ በተቻለኝ አቅም ሁሉ ስርዓት ያለው እንዲሆን እጥራለሁ፡፡ ባለቤቴ ቁጣዬን በተመለከተ ቀልድ ቢጤ ጣል ለማድረግ ሲሞክር አብሬው ለመሳቅ እሞክራለሁ፡፡ ድምፄ ትዕግስት የለሽ ወይም ወቃሽ እንዳይመስል ቀለል ያለና አስደሳች ላደርገው እሞክራለሁ፡፡ በዚህ ጉዳይ ዙሪያ ለዓመታት በጽናት ብታገልም፣ አሁንም ድረስ ያስቸግረኛል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የደ/ሰ/መ/ቤ/ክ ፓሪሽ ፕሮግራም አመታዊ ሄልዝፌር (በሚኒሶታ ለምትኖሩ ወገኖቻችን ነፃ የህክምና ምርመራና ትምህርት ቀን)

3. በቂ ግምት አለመስጠት
የተለያዩ ጥናቶች እንደሚያሳዩት፣ ባለትዳሮች አንዳቸው ለሌላኛው ካላቸው የበለጠ ትህትና ለሌሎች ሰዎች ያሳያሉ፡፡ እኔም ብሆን ለባለቤቴ ብዙም ትህትና አላሳየውም፡፡ ያም ሆኖ፣ ከዚህ ጋር በተያያዘ አንዳንድ መሰረታዊ ለውጦችን እያደረግሁ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል፣ እቤት ሲገባና ሲወጣ ሞቅ ያለ ሰላምታ እሰጠዋለሁ፣ ከሱ ጋር በስልክ እያወራሁ እያለ ሌላ ነገር አልሰራም፡፡

4. ነጥብ ያዥነት
እኔ በበኩሌ አንዳችን የሰራነውን ነገር በተመለከተ ሁሌ ነጥብ እንደያዝኩ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል፣ ባለቤቴን ‹‹ወጥ ቤቱን ስላፀዳሁ፣ ‹‹አስቤዛ የምትገዛው አንተ ነህ›› እለዋለሁ፡፡ ይህን ዝንባሌ ለመታገል ሁለት ዘዴዎችን አግኝቻለሁ፡፡
በቀዳሚነት፣ ለምናበረክተው አስተዋፅኦ ሳናውቀው ከሌሎች ሰዎች አንፃር የተጋነነ ግምት እንደምንሰጠው ራሴን አስታውሰዋለሁ፡፡ በእርግጥ፣ ሌሎች ሰዎች ከሚሰሩት ነገር ይልቅ እኛ ስለምናከናውነው ነገር የበለጠ ግንዛቤ ስለሚኖረን ይህ አባባል ትክክል ነው ማለት ይቻላል፡፡ The Happiness Hypothesis መጽሐፍ ደራሲ ጆታናን ሄይድን እንደሚሉት፣ ‹‹ባሎችና ሚስቶች እያንዳንዳቸው ስለሚሰሩት የቤት ውስጥ ስራ መቶኛ ሲያሰሉ ግምታቸው ከ120 በመቶ በላይ ይመጣል›› የመብራት፣ የጋዝና የውሃ የመሰሉ ሂሳቦችን ለመክፈል ስለማቃጥለው ጊዜ ቅሬታዬን ብገልፅም፣ ባለቤቴ መኪናችንን ለማሳደስ የሚያቃጥለውን ጊዜ ከግምት ውስጥ አላስገባውም፡፡ ይህ አይነቱ አካሄድ በባለትዳሮች መካከል ቅሬታንና የተጋነነ የይገባኛል ስሜትን ይፈጥራል፡፡ ስለዚህም፣ ‹‹እንዲህ ለማድረግ የምቸገረው እኔ ብቻ ነኝ›› ወይም ‹‹ለምንድን ነው እኔ ሁሌ…›› ከማለት ይልቅ ስለማላደርጋቸው ሰዎች ራሴን አስታውሰዋለሁ፡፡
በሁለተኛው ደረጃ የመንፈሳዊ መሪዬን የሊሲዬዋ ቅድስት ቴሬስን፣ ‹‹አንድን ሰው ስናፈቅር ስሌት ማድግ የለብንም›› የሚለውን አባባል ራሴን አስታውሰዋለሁ፡፡ ስለዚህም፣ ትዳሬን በተመለከተ በስሌት መመራት የለብኝም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  Health: ‹‹በእንቅልፍ ማጣት የዕለት ተዕለት ሕይወቴ ደስታ ርቆታል›› ጥያቄና የሕክምናው ምላሾች

5. ባለቤቴን ችላ ማለት
ቀደም ብዬ እንደጠቀስኩት ሁሉ፣ ባለቤቴ የሚያከናውናቸውን የቤት ውስጥ ስራዎች በተመለከተ በርካታ በጎ ጎኖቹን በመተው ለህፀፆቹ ትኩረት እሰጣለሁ፡፡ ለምሳሌ ያህል፣ በቁጣ ቃል አለመናገሩ ቢከብደኝም፣ ባለቤቴ አንድም ጊዜ በዚህ መልኩ አናግሮኝ አለማወቁ አንድ የሚያስመሰግነው ነገር ነው፡፡ ባለቤቴን የምወድባቸውን ነገሮች በንቃት ለመከታተልና በትንሽ ትልቁ መበሳጨቱን ለመተው እየሞከርኩ ነው፡፡ ይሁንና፣ ይህን መተግበሩ ቀላል አልሆነልኝም፡፡
ከባለቤቴና ከልጆቼ ጋር ፍቅር አዘል በሆነ መልኩ የትዳር ህይወቴን ለመግፋት ከበፊቱ ይበልጥ መሳሳም፣ መተቃቀፍና መደባበስ ውጤታማ እንደሆነ ደርሼበታለሁ፡፡ የትዳሬን ሳንካዎች ለማስወገድ ተግባራዊ ከማደርጋቸው መፍትሄዎች መካከል አንዱ ይኸው ይበልጥ መሳሳም፣ መተቃቀፍና መደባበስ ነው፡፡ ይህን መፍትሄ መተግበሩ ምንም አይነት ተጨማሪ ጊዜ፣ ጉልበት ወይም ገንዘብ አይጠይቅም፡፡ ከዚህም በላይ በትዳሬ ላይ እውነተኛ ለውጥ አምጥቷል፡፡

ምንጭ፡ ዘ-ሐበሻ ጋዜጣ ቁጥር 47

Share