ተስፋዬ ገብረአብ በ53 ዓመት ዕድሜው ከዚህ ዓለም በሞት መለየቱን የቅርብ ቤተሰቦቹ ለቢቢሲ ገለጹ

ተስፋዬ ገብረአብ ለወራት በህመም ላይ የቆየ ሲሆን በኬንያ ዋና ከተማ ውስጥ ህክምና ሲከታተል ቆይቶ ነው አርብ ከሰዓት በኋላ ታኅሣሥ 15 ቀን 2014 ዓ.ም ነው ያረፈው።
በሥነ ጽሁፍ ሥራዎቹ በስፋት የሚታወቀው ተስፋዬ ነሐሴ 22/1960 ዓ.ም ከኤርትራውያን ቤተሰቦቹ ከአዲስ አበባ በስተምሥራቅ 40 ኪሎ ሜትር ያህል ርቃ በምትገኘው በቢሾፍቱ ከተማ ነበር ተወልዶ ያደገው።
– በደርግ ዘመን ማብቂያ አካባቢ ላይ ወደ ጦር ሠራዊቱ ተመልምሎ ሥልጠና ከወሰደ በኋላ ብዙም ሳይቆይ ወታደራዊው መንግሥት ወድቆ ከኢህአዴግ ጋር ወደ አዲስ አበባ ተመልሶ በጋዜጠኝነት ሲያገለግል ቆይቷል።
– ዕለታዊ የመንግሥት ጋዜጦችን የሚያሳትመው የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ሥራ አስኪያጅ ሆኖ አገልግሏል።
– ከኢህአዴግ ፓርቲ ጋር ጥብቅ ቁርኝት የነበረው “እፎይታ” መጽሔትን መርቷል።
– ኢትዮጵያ ውስጥ እያለ ከጋዜጠኝነት ሙያው ጎን ለጎን መጽሐፍቶችን አሳትሟል፣ ከገዢው ፓርቲ ጋር በነበረው አለመግባባት ኢትዮጵያን ጥሎ ከወጣ በኋላ ኬንያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ኔዘርላንድስና ሌሎችም አገራት ውስጥ ኗሯል።
– የጋዜጠኝነት ሥራውን ካቆመ በኋላ አስከ ህይወቱ ፍጻሜ ድረስ የሙሉ ጊዜ ፀሐፊ በመሆን ከ8 በላይ ሥራዎችን ለአንባቢያን አድርሷል።
– ከ8 በላይ ስራዎችን በአማርኛ ቋንቋ ያሳተመ ሲሆን በአንባቢያን ዘንድ በስፋት ያስተዋወቀው ” የቡርቃ ዝምታ ” የተሰኘው ረዥም ልብ ወለዱ ነው። ይህ የልብወለድ መጽሐፉ በበርካታ የአማርኛ ልብወለድ አንባቢያን ዘንድ ነቀፌታን አሰንዝሮበታል።
– የግል ማስታወሻዎችን፣ ልብወለድ፣ አጫጭር ልብወለድ እንዲሁም ወጎችን በመጻፍ አድናቆትን አትርፏል።
– ከህዝባዊ ወያነ ሓርነት (ህወሓት) ትግል ጅማሬ አስከ ኢህአዴግ አዲስ አበባ መግባት ድረስ ያለውን ዋና ዋና ታሪክ እና ገድል የሚተርከውን ተከታታይ ቅጽ ያለውን ” ተራሮችን ያንቀጠቀጠ ትውልድ ” መጽሐፍትን አሳትሟል።
– በጋዜጠኝነቱና በሥነ ጽሁፉ ዘርፍ የገዢው ኢህአዴግ ዋነኛ ሰው በመሆን የተለያዩ ሥራዎችን ሲሰራ ቆይቷል፤ እሱ እንደሚለው ከአገሪቱ ዋነኛ ፖለቲከኞች ጋር በተፈጠረ አለመግባባት ኢትዮጵያን ለቅቆ ለመሰደድ በቅቷል።
– ከአገር ለቆ ከወጣ በኋላ ብዙ መነጋገሪያ የሆኑ በወቅቱ ገዢ ፓርቲ የነበረው ኢህአዴግና የባለሥልጣናቱ የውስጥ ምስጢር የሆኑ ጉዳዮችን የያዙ “የጋዜጠኛው ማስታወሻ” እና “የደራሲው ማስታወሻ” የተሰኙ መጽሐፎችን ለንባብ አብቅቷል።
ጋዜጠኛ እና ደራሲ ተስፋዬ ገብረአብ ኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ ውስጥ በ53 ዓመት ዕድሜው ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።
ተጨማሪ ያንብቡ:  ወ/ሮ መአዛ አሸናፊ የመጀመርያዋ ሴት የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ሆኑ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share