የአሜሪካ ልዩ መልዕክተኛ ጄፍሪ ፌልትማን ወደ ኢትዮጵያ ድጋሚ ሊጓዙ ነው

“ለወራት የዘለቀው ጦርነት በታላቂቱ አገር በውጊያ የማይሽር ብርቱ መከራ እና መከፋፈል አምጥቷል” ሲሉ የፕሬዝደንት ጆ ባይደን የብሔራዊ ጸጥታ አማካሪ ጄክ ሱሊቫን የልዩ መልዕክተኛውን ጉብኝት ይፋ ባደረጉበት የትዊተር መልዕክታቸው ጽፈዋል። ጄክ ሱሊቫን “ሁሉም ወገኖች በአፋጣኝ ወደ ድርድር እንዲመጡ ጥሪ እናቀርባለን” ብለዋል።

41650861 303
41650861 303

የአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ጄፍሪ ፌልትማን ወደ ኢትዮጵያ ድጋሚ ሊጓዙ ነው። የአሜሪካው ፕሬዝደንት ጆ ባይደን ወሳኝ ባሉት በዚህ ወቅት ጄፍሪ ፌልትማን በድጋሚ ወደ ኢትዮጵያ እንዲጓዙ መጠየቃቸውን የብሔራዊ ጸጥታ አማካሪያቸው ጄክ ሱሊቫን ትናንት ሐሙስ ዐስታውቀዋል።

ልዩ መልዕክተኛው ወደ ኢትዮጵያ የሚጓዙት ዘጠኝ ወራት የዘለቀው የትግራይ ውጊያ ወደ አማራ እና አፋር ክልሎች ተሻግሮ አሳሳቢ በሆነበት ወቅት ነው።

“ለወራት የዘለቀው ጦርነት በታላቂቱ አገር በውጊያ የማይሽር ብርቱ መከራ እና መከፋፈል አምጥቷል” ሲሉ የፕሬዝደንት ጆ ባይደን የብሔራዊ ጸጥታ አማካሪ ጄክ ሱሊቫን የልዩ መልዕክተኛውን ጉብኝት ይፋ ባደረጉበት የትዊተር መልዕክታቸው ጽፈዋል። ጄክ ሱሊቫን “ሁሉም ወገኖች በአፋጣኝ ወደ ድርድር እንዲመጡ ጥሪ እናቀርባለን” ብለዋል።

ጄፍሪ ፌልትማን ባለፈው ሚያዝያ ልዩ መልዕክተኛ ሆነው ከተሾሙ በኋላ በግንቦት መጀመሪያ ወደ አዲስ አበባ ተጉዘው ጠቅላይ ምኒስትር ዐቢይ አሕመድን ጨምሮ ከኢትዮጵያ መሪዎች ጋር ተወያይተው ነበር።

ከሚያዝያ 26 እስከ ግንቦት 5 ቀን፣ 2013 ዓ.ም. በምሥራቅ አፍሪካ ባደረጉት የመጀመሪያ ጉዟቸው ግብጽ፣ ኤርትራ እና ሱዳንን ጎብኝተው ከአገራቱ መሪዎች ጋር ተነጋግረዋል።

በሁለተኛው ዙር ጉብኝታቸው ወደ ኳታር፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች እና ኬንያ አቅንተዋል። ከግንቦት 23 እስከ 29 የዘለቀው ሁለተኛ ዙር የፌልትማን ጉብኝት “የተረጋጋ እና የበለጸገ የአፍሪካ ቀንድ በትብብር መደገፍ በሚቻልበት መንገድ ላይ ለመወያየት” የታቀደ የሚል ነበር። በዚህ ጉብኝት ኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብጽ የሚወዛገቡበት የታላቁ የኅዳሴ ግድብ ጉዳይ ሌላው አጀንዳ ነበር።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ለአሸባሪው ሕወሓት ፅንፍ የወጣ ድጋፍ እያሳዩ ያሉት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ኢትዮጵያን ከአግዋ ዕድል ተጠቃሚነት የሰረዙበት ውሳኔ ተችትን እያስተናገደ ነው

ልዩ መልዕክተኛው ከነሐሴ 9 እስከ 18 ቀን፣ 2013 ዓ.ም. ባሉት ቀናት ከኢትዮጵያ በተጨማሪ ወደ ጅቡቲ እና የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች እንደሚጓዙ የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ዐስታውቋል።

DW

 

 

1 Comment

  1. ልዪ መልዕክተኛው ለምን ይሆን የሚንሸራሸሩት? በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ አሜሪካ እንዲህ ለኢትዮጵያ የተጨነቀች መስላ የቀረበችበት ታሪክ የለም። አረብ ኤሜሬትስንና ጅቡቲን የሚረግጡት የጆ ባይደን ተላኪ ምን ይዘው፤ ምን ለማለት ነው እንዘጥ እንዘጥ መባሉ? አሁን ክአፍጋኒስታን ልክ እንደ ቬትናም እግሬ አውጪኝ በማለት ፍርጠጣ ላይ ያለው የአሜሪካ ጦርና የውጭ ጉዳይ ፓሊሲ ምን አስቦ ነው ነጋ ጠባ ኢትዮጵያ የሚመላለሰው? አሜሪካኖች የወያኔ አገልጋዪች እንደሆኑ ለመረዳት ብሊንከን የሰጠውን ያለፈና የቅርብ ጊዜ መግለጫ ቃል በቃል አንቦ መረዳት ነው። ይመስለኛል ወያኔ ድረሱልን አለቅን ያላቸው ይመስላል። በአፍሪቃ አንድ አርቆ አሳቢና አስተባባሪ መሪ ሲኖር ቶሎ የሚቀጨው ሚስጢሩ ምንድን ነው? ሳሞራ ሚሽልን፤ ፓትርስ ሉቡንባን፤ ኩዋሜ ንክሩማ፤ቶማስ ሳንካራ፤ ጋዳፊንና ሌሎችንም ማን ነው ለዘለቄታ እንዳይተነፍሱ ያረጋቸው? ልብ ያለው የሚነገረውንና የተገዛ የዜና ማሰራጫ የሚያናፍሰውን በመተው ነገርን መርምሮ መረዳት ይችላል። አሁን እንሆ ወያኔ ጥፍር ሲያወልቅ፤ ሶዶማዊ ተግባር በእስረኞች ላይ ሲፈጽም፤ በአደባባይ ሰው ሲረሽን፤ ከሁለት ሚሊዪን በላይ አማሮች ጠፉብኝ ሲል (ራሱ አፍኖና መርዞ ገድሎ) አሜሪካ የት ነበረች? የዛሬው ሽር ጉድና የመግለጫ ጋጋታ ከየት መጣ? በመሰረቱ የአሜሪካ የእምነትም ሆነ የመንግስት ነክ የተራዶ ድርጅቶች ሁሉ የስለላው መረብ አካል ናቸው። ይህን ለመረዳት በዚሁ የጠለፋና የማታለል መረብ ውስጥ የሰሩ ሰዎች የጻፏቸውን መጽሃፍት በማንበብ መሰሪነታቸውን መመልከት ይቻላል።
    ፓለቲከኛ ለመሆን ቀጣፊ መሆን ቀዳሚው የመመዘኛ ነጥብ ነው። አሜሪካና አውሮፓ የጥቁር ህዝብ አንገቱን ቀና አድርጎ ኑሮውን በማስላት እንዲኖር አይፈቅድለትም። ሁሌ እሳትና ጭድ እያቀበሉ እንድንባላ በቀጥታም ሆነ በእጅ አዙር ይሰራሉ እንጂ። የዚህ ቀጣፊ ሰውዬውም የድጋሚ ጉዞ ዝምባባ ይዞ ለሰላም ሳይሆን ለማስፈራራት፤ ተንኮል ለመዝራት አልፎ ተርፎም ያው እንደተለመደው ማዕቀብ እናረጋለን በማለት የሃገርን ኢኮኖሚ ለማሽመድመድ ነው። በምንም ሂሳብ ቅንነት ያለበት የፓለቲካ ዘይቤ የአሜሪካ የውጭ ፓሊሲ አይፈቅድም። ካሮት አሳይቶ ድላ፤ ዱላ አሳይቶ ካሮት እንጂ! ሁሉም ነገር ለአሜሪካ ጥቅም ብቻ ነው። ለዚህ ሴራቸው ግብጽን፤ ሱዳንን፤ ትራፊ ወያኔዎችን አልፎ ተርፎም ሳውዲ አረቢያን (ስደተኛን በማባረርና በሸር) ሌሎችንም እያስተባበሩና ጉቦ እየሰጡ በማሰለፍ ኢትዮጵያን ከወያኔ ሌላ ማንም አይገዛትም ብለው ተነስተዋል። ነገር ግን በቅርብ ቀን በኢትዮጵያ ውስጥ የታየው ህብረትና ቆራጥነት ደግሞ አስደንግጧቸዋል። ዘር፤ ቋንቋ፤ ሃይማኖት ሳይለያቸው ከዳር እስከ ዳር ወያኔን ለመቅበር የኢትዮጵያ ህዝቦች ሲነሱ መላ ጠፍቷቸዋል። ለዚህ ነው አንዴ የኢትዮጵያን አንድነት ሌላ ጊዜ የአማራና የኢትዮጵያ ጦር ይውጣ እያሉ የሚቀባጥሩት። ባይገባቸው ነው እንጂ ወያኔ ሞቷል። ከአሁን በህዋላ የሚኒሊክ ቤ/መንግስት ውስጥ ለመኖር ቀርቶ ለዓይኑ አያየውም። ሲያምርሽ ይቅር የሚሉት አበው እንዲህ አይነቱን ነው።
    ባጭሩ የአሜሪካ የውጭ ፓሊሲ የሚታመን አይደለም። እዚህ ጋ አንድ ነገር ብለው እዚያ ጋ አፍራሽ ቃል ያወራሉ። በአንድ በኩል እሳት ሰተውና የሰው ህይወትና ንብረት አውድመው በሌላ በኩል የተራዶ ድርጅት ልከው ስንዴ ያከፋፍላሉ። በየመን የምናየው ይህኑ ነው። አፍሪቃ የነጭ ዓለምን ተንኮልና የአረብን ሴራ ተረድቶ ራሱንና ሌላውን ለማዳን መቼ እንደሚጥር አይገባኝም። የአፍሪቃዊያን ችግር ጥልፍልፍ ነው። የሚበዛው ችግር የሚመነጨው ከራሳችን ነው። መፍትሄውም በእጃችን ነው። ግን ያልተጋበዘ ሰው እየጋበዝን ወገናንች እየገደልንና እያሰረን፤ የተከመረ እህል እያቃጠልን ተራብን፤ ተጠማን ብንል እንዴት ነጩ ዓለም አይቀልድብን። ይገባቸዋል። አሁን ማን ይሙት በወያኔና በሌሎች ሃይሎች የሚደረገው ፍልሚያ እብደት አይደለም የሚል ሰው አለ? ልብስ ያስወለቀ እብደት ነው እንጂ! ግን ሙታን ቋሚንና እኖራለሁ የሚልንም ነው ይዘው የሚሞቱት። ወያኔ የሚያደርገው ይህኑ ነው። የትግራይ ልጆችን አስጨርሶ እሱ ዳግም ስልጣን ላይ ሊወጣ። ኢትዮጵያን ሲኦል ድረስ አድርሶ እሱ በገነት ሊኖር። ይህ የእብድ ቋንቋ ነው። ወያኔ የአውሬዎች ስብስብ ነው። የአሜሪካ የቀጥታና የእጅ አዙሪ ወያኔን መደገፏም ተላላኪ ፍለጋ ነው። 40 ዓመት ሙሉ በግብጽ ሆስኒ ሙባረክን ደግፈው አቅፈው ይዘው ስልጣን ላይ ያቆዩት ተላላኪ በመሆኑ ነው። ህዝብ የመረጠውን ዶ/ር ሞሃመድ ሞርሲን በጦር ሃይሎች ጉልበት እንዲወርድ አድርገው ሌላ መለዪ ለባሽ አል ሲሲን ነው ያስቀመጡት። ይህ አይታየኝም የሚል ፓለቲከኛ ጠንጋራና ደንባራ ነው። ከላይ እንዳልኩት የዚህ ልዪ መልዕክተኛ ተብየው የአሁን ጉዞም ክፋትን እንጂ መልካምነት የለውም። ቆይተን እንይ! በቃኝ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share