ኢሕአፓ፣ ኢትዮጵያን በአንድነት እናድን ይላል!!

/

ነሐሴ  3 ቀን 2013 ዓ/ም

የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ )
Ethiopian People’s Revolutionary Party (EPRP)

ኢትዮጵያ ሀገራችን ላይ ታላቅ አደጋ እየተጋረጠ በመሆኑ መስቀለኛ መንገድ ላይ ትገኛለች፡፡  በሀገር ውስጥ የበቀሉ አሸባሪዎችንና የባዕዳን ተላላኪዎችን እየተጠቀሙ በነፃነትዋ ታፍራና ተከብራ የኖረችውን፣ ውድ ሀገራችንን ለማጥፋት የውጭ ጠላቶች አሲረው ተነስተውብናል።  በለመዱት ሀገራትን በሀሰት የማጠልሸት ዘዴያቸው ከዕውነት በራቁ ትርክቶች ኢትዮጵያን እያብጠለጠሏት ይገኛሉ።  ህወሓትን፣ ኦነግ ሸኔ የሚባለውን (ራሱን የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት እያለ የሚጠራው)፣ ሌሎችንም ባንዳ ቡድኖች አሠልፈው ሀገራችንን ሰንገው ይዘውታል።  በተለይም አሸባሪው ህወሓት ትንንሽ ልጆችን ጭምር በጦር ግንባር በማሠለፍ እየማገዳቸው ይገኛል።

የፌዴራል መንግሥቱና የጦርነት ቀጠናዎች የተደረጉት ክልሎችን የሚያስተዳድሩት የክልል መንግሥቶች ሀገራችንን ከአሸባሪዎች የመከላከል ግዴታ ስላለባቸው ተገቢነት ያለው ህግን የማስክበር እርምጃዎች እየወሰዱ ናቸው።  ማንኛውም ጦርነት ጎጂ፣ አስከፊ፣ ሞትን፣ አካላዊ ጉዳትን፣ የልማት አውታሮች ውድመትን ይዞ ስለሚመጣ መራር ነው። ይሁን እንጂ አሸባሪዎቹ ላይ አስፈላጊው ሁሉ እርምጃ መወሰዱ ተገቢ፣ አስፈላጊ፣ ፍትሃዊም ነው።

በአሁኑ ወቅት ሀገራችን ትልቅ ኅብረተሳባዊ ቀውስ ውስጥ ትገኛለች፡፡  በተለይ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል ለአለፉት ዘጠኝ ወራት ክቡር የሆነው የሰው ህይወት በየደቂቃው በሚያስብል ደረጃ እንደ ቅጠል እየረገፈ ይገኛል፡፡  ርኅራሄ የማያውቀው ህወሓት “መጠቀሚያው ያደረገውን የራሴ” የሚለውን የትግራይ ሕዝብም አንድም ጊዜ ሳስቶለት አያውቅም።  በርካታ ወገኖቻችን በጦርነት እያለቁ ስለሆነ ያማል።

ህወሓት ለእርዳታ የሚገባውን እህል ከረሃብተኛው እየነጠቀ በጦርነቱ ያሰለፈውን ተዋጊ ኃይል እየመገበ መሆኑን የእርዳታ ሰጭ ድርጅቶች ያውቃሉ፡፡ የተቸገረው ሕዝብ እርዳታ በሰዓቱ እንዳያገኝ የስንቅ ማጓጓዣ መንገዶችን እየዘጋ ለሕዝቡ የሚሄደውን ዕርዳት እያስተጓጎለ ይገኛል፡፡  ከጦርነቱ አካባቢዎች ሕዝብ ተፈናቅሏል፣ ተሰዷል፤ ሴቶች የሚደፈሩበት የሚጉላሉበት ሁኔታ ተፈጥሯል። የመንግሥታዊና የግል ድርጅቶች እንዲሁም የግለሰቦች ሀብትና ንብረቶች ተዘርፈዋል፡፡ ይህ ሁሉ እየሆነ ሰብዓዊነት የራቀው፣ አሸባሪው ህወሓት፣ በዓለም የተወገዘውን ሕፃናትን የጦር መሣሪያ አስታጥቆ ወደ ጦርነት የማሠለፍ ተግባር ዛሬም በገፍ እየፈጸመው ይገኛል።  የአሸባሪው ቡድን መሪዎች ሁሌም ይሉኝታ ቢሶች ስለሆኑ፣ ይህንኑ ነውራቸውንም በቪዲዮ እየቀረጹ እያሳዩን ናቸው።

ትግራይ ውስጥ ለብዙ ዓመታት የተጠለሉ የኤርትራ ስደተኞችን አብራችሁን ተሰልፋችሁ የኢትዮጵያን መንግሥት ካልወጋችሁ በሚል ከቤሰቦቻቸው ፊት በጥይት መረሸኑን የተራድኦ ሠራተኞችና እንደምንም ከትግራይ የጦር ቀጠና አምልጠው አዲስ አበባ የገቡ ኤርትራውያን ስደተኞች እየገለጹልን ይገኛሉ፡፡  ይህ ሁሉ እየሆነ የምዕራቡ ዓለም መንግሥታትም በሌላው ጊዜ “አትያዙን-ልቀቁን” ይሉ የነበሩት “ለሰብዓዊ መብት እንሟገታለን” የሚሉት መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እንዲሁም የብዙሃን መገናኛ ተቋማትም ሆኑ ጋዜጠኞቻቸው የወያኔን ግፍ የሚያወግዝ አንድም ቃል ሲውጣቸው አልተደመጡም፡፡ እንዲያውም በተቃራኒው የሚከሱት የተኩስ አቁም ያደረገውንና ለትግራይ ሕዝብ እርዳታ እንዲደርስ ከፍተኛ ጥረት የሚያደርገውን የኢትዮጵያን መንግሥት ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  አሸባሪ ትህነግ ዛሬም ሀገር የማፍረስ አጀንዳ አንግቦ ጦርነት እያደረገ መኾኑን የሰሜን ወሎ ዞን አስታወቀ

በሌላ በኩል በኢትዮጵያ መንግሥት በአሸባሪነት የተፈረጀውን፣ ህወሓትን መልሶ ወደ ሥልጣን ለማምጣት እንዲቻል ምዕራባውያን በርካታ ሤራዎችን እየጎነጎኑ መሆናቸው ከበቂ በላይ አውቀናልና “አቁሙ” እንላቸዋለን።  “እጃችሁን ከኢትዮጵያ ላይ አንሱ!!!” እንላለን።

የህወሓት አጋርና ተባባሪ የሆነው ኦነግ-ሸኔ የሚባለው ቡድን በወለጋና በሌሎችም የኦሮሚያ ክፍሎች በተለይም አማራዎችን መግደሉን ቀጥሏል።  በቤንሻንጉል አካባቢ የሚንቀሳቀሰው የጉምዝ አሸባሪ ቡድን ዘርን መሠረት ያደረገ ግድያና መፈናቀል ማድረጉን ዛሬም አላቆመም፡፡  ይህ በቀድሞው የጎጃም አካል በነበረው መተከል ውስጥ በህወሓት መሠሪ ዕቅድ መሠረት በተፈጠረው ክልል ውስጥ የሚካሄድ የግድቡንም አካባቢ ሠላምና ፀጥታ የሚያናጋ ግድያና ማፈናቀል፤ ለአለፉት 30 ዓመታት  በህገመንግሥትና የክልል አወቃቀር ተደግፎ ከቤኒሻንጉል ብሄረሰቦች ውጭ ያሉትን “መጤዎች” እያሉ በመጥራት መብት አልባ አድርጎ፣ ሆን ተብሎ የተተከለ የጥፋት ፖለቲካ ነው ዛሬም አካባቢውን እያናወጠ ያለው።

በቅርቡ የኢትዮጵያ መንግሥት የተናጠል የተኩስ አቁም አድርጎ ከትግራይ ክልል የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊትን አስወጥቶ ነበር።  አሸባሪው ወያኔ፣ እንኳን ሕዝቡ እፎይታ እንዲያገኝ ተኩስ ሊያቆም ቀርቶ፣ ሠራዊቱ ከአካባቢው በመውጣቱ የተፈጠረውን ክፍተት ተጠቅሞ በመላው ትግራይ በንፁሀን ዜጎች ላይ “ከፌደራል መንግሥት ጋር ተባብራችኋል በሚል” ዘግናኝ ግድያዎችን መፈጸሙንና፣ ይባስ ብሎ ወደ አማራና ወደ አፋር ክልል ጦርነቱን በማስፋፋት ወጊያ ክፍቷል፡፡  ከዚህም አልፎ በከፍተኛ እብሪትና በማናለብኝነት ስሜት ተኩስ አናቆምም፣ እንዲያውም አዲስ አበባ ድረስ በመግባት ኢትዮጵያን እናፈርሳታለን፣ የሚያግደንም ኃይል የለም እያሉ እያቅራሩ ናቸው።  ይህ አሸባሪ ቡድን፣ ከባዕዳኑ የተሰጠውን ኢትዮጵያን የማፍረስ ተልዕኮውን፣ “በሚደረግልኝ ትብብር ተጠቅሜ እፈጽመዋለሁ!!” እያለን ነው።  ለኢትዮጵያውያን ከዚህ የበለጠ መደፈር፣ ንቀትና ውርደት፣ ሊኖር አይችልም።  ኢትዮጵያውያን በማያወላውል መንገድ፣ “እምቢ፣ የኢትዮጵያችን ጠላቶች መሆናችሁን በርግጠኛነት ስለምናውቅ በአንድነት ተነስተን የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና አንድነት እናስከብራለን ልንላቸው ይገባል።

በባዕዳን እየታገዙ ኢትዮጵያን ለማፈራረስ የሚሯሯጡትን ፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ተሸንፈው ተገቢ ቅጣታቸውን በሀገሪቱ ሕግ መሠረት ማግኘት አለባቸው።  በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥትም ያሉበትን ጫናዎች በሕዝብ ድጋፍና ትብብር ለመወጣት ከመሥራት ውጭ፣ የሕዝቡን ቁርጠኛነት ጠላቶቹን የማውደም ተግባሮቹን በምንም ምክንያት ሊያዳክም አይገባም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ለመሆኑ  የከሞት በኋላ ህይወት መንገዱና መግቢያው ምንድን ነው?

ኢትዮጵያ ተገቢውን መስዋዕት ከፍላ ነፃነትዋን ሳታስደፍር እስከዛሬ ኖራለች።  በቅኝ ግዛት ሥር ወድቀው የነበሩት የጥቁር አፍሪካውያን ሀገሮች ለነፃነታቸው እንዲታገሉ ረድታለች።  በአርዓያነትዋም ለመላው ጥቁር ሕዝብ ለነጮቹ ያልተዋጠ ነገር ግን ለጥቁሩ ሕዝብ “የተስፋና የይቻላል” ግዙፍ እውነታ ማሳያ ሆናለች።  አሁን ደግሞ ከአፍራሾች እጅ አምልጣ ዓባይንም ገድባ በመብራት ኃይል መጠቀም ችላ፣ እራሷን ልታሳድግ እያኮበኮበች ነች።  ታሪካዊ የሚባሉትና ሌሎችም ጠላቶችዋ ዕድገትዋንና አርዓያነትዋን ከመጠን በላይ እየፈሩት ይገኛሉ።  ሀገር-በቀል አሸባሪዎችን በመጠቀም ግብግብ ሊገጥሙን ተነስተውብናል።  ዛሬ ዜጎችዋ ልክ እንደ ዐድዋው ወቅት በአንድ ላይ ቆመን የራሳችንን ጉዳይ እኛው ነን የምንወስነው ልንላቸው ይገባል።  እኛም የእነዚያ ጀግኖች ልጆች ነንና!

በዚሁ በባዕዳኑ እኩይ ዓላማ ተበረታትው፣ ጎረቤቶቻችን፣ ሱዳንና ግብጽ፣ ሁሉንም ዓይነት ደባና ሤራ እየሠሩ ናቸው።  በተለይ ዐባይን እንዳንገድብ ለማደናቀፍ፣ ወዳጆቻቸውን ከኋላቸው አስልፈው ኢትዮጵያን በኢኮኖሚም ሆነ በፖለቲካ፤ እንዲሁም በማኅበራዊ ኪሳራ ውስጥ እንድትወድቅ ተባብረው ሌት ተቀን እየሠሩ ነው፡፡  ሱዳን ይህን አጋጣሚ ተጠቅማ የአገራችን ድንበር ጥሳ ገብታ መሬታችን ይዛለች፡፡ የአገራችን ዜጎች በሱዳን ወታደሮች በየቀኑ እየተገደሉና ንብረታቸው እየተዘረፈ መሆኑን መንግሥት እየገለጸ ነው፡፡  በበርካታ ችግሮች ተሰንጋ የተያዘቸው አገራችንን፣ በአሁኑ ሰዓት በኢኮኖሚም፣ ይበልጥ እንድትዳከም ለማድረግና ለእነሱ ትዕዛዝ እንድትበረከክ ለማድረግ፣ በተለይ በአሜሪካ የሚመራው የምዕራባውያኑ ጥምረት፣ በዛቻና ሤራ ተጠምዷል።  ምዕራባውያን ሉዓላዊነታችንን በምጽዋት እንድንለውጥ ሊያደርጉን ይፈልጋሉ።  እንራባለን፣ ቀበቶአችንን እናጠብቃለን እንጂ ልንበረከክ ግን ፈጽሞ አይገባም እንላለን።

ሀገራችን እንዲህ ባለ ችግር ውስጥ ስትወድቅ ከእያንዳንዱ ዜጋ ምን ይጠበቅበታል፤ ብለን በሀገር ወዳድነት መንፈስ ማሰብና መምከር ያስፈልገናል።

በእኛ እምነት ልንወጣው የማንችለው ችግር የለም።  ሀገራችን በነፃነትዋ ታፍራና ተከብራ እንድትቀጥል ዜጎችም ከረሃብና ችጋር፣ ከሠላም እጦትና ከማያባራው የጦርነት ሁኔታ እንዲላቀቁ ማድረግ አለብን።  አሁን ያለውን አስቸጋሪ ሁኔታ ለመለወጥ ምንም ዓይነት የፖለቲካ ልዩነት ሳይበግረን በአንድነት በውጭና በውስጥ ጠላት የተደቀነብንን አደጋ መከላከልና ጠላቶቻችንን በጠንከራ ክንድ ማድቀቅ አለብን፡፡

በኢሕአፓ እምነት፣ አሁን በአገራችን እየደረሰ ያለው አደጋ የኢትዮጵያውያን ሁሉ እንጂ የተወሰኑ የመንግሥት ባለሥልጣናት ወይም የፖለቲካ ድርጅቶች ጉዳይ ብቻ አይደለም፡፡   በአድዋና በሌሎች ፈታኝ የሀገራችን ታሪክ ወቅቶች እንዳደረግነው ሁሉ ዛሬም በአንድነት ሆነን መከፈል የሚገባውን መሰዋዕትነት ከፍለን ሀገራችንን ከውጭና ከውስጥ ጠላት ማዳን የግድ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሕብር ሬዲዮ የካቲት 3 ቀን 2011 ዓ.ም. ፕሮግራም

ስለዚህ ይህን አጋጣሚ በመጠቀም ኢሕአፓ ለሚመለከታቸው ሁሉ በአንድነት ሆነን ሀገራችንን እናድን የሚለውን ጥሪውን ሊያስተላልፍ ይወዳል፡፡

  1. በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ አገራት የምትገኙ የኢሕአፓ አባላትና ደጋፊዎቻችን ሀገራችንን ለማፈራረስ የተሰለፉብንን የውጭና የውስጥ ጠላቶች፣ ከመላውከሕዝባችን ጋር ቆማችሁ እንድትታገሉት ጥሪ እናቀርባለን!
  2. መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አቅሙ በፈቀደው መጠን ሁሉ በጦር ግንባር ተሰልፎ ደሙን ከሚያፈሰው ሠራዊትና ልዩ ኃይል ጎን እንዲቆም፣ የስንቅ፤ የገንዘብናየመረጃ ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪያችን እናቀርባለን፡፡
  3. ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች እያሳያችሁትያለውን ከሕዝብ ጋር የወገነ እርምጃ እጅግ አበረታችና የሚደገፍ ነው፡፡   ይህ ጅምር ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥልና አመርቂ ውጤት እንዲያስገኝ  አገራችንን እንዴት እናድን በሚለው ላይ ምክክር እንድናደርግ ጥሪያችን እናቀርባለን፡፡
  4. በውጭ ሀገር የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ትክክለኛ መረጃ እንዲያገኝና በሀገራችን ላይ እየተደረገ ያለውን አፍራሽ ተግባር ለማክሸፍ የሀገርና የሕዝብ ጠበቃ በመሆን በሚደረግው ትግል ውስጥ ተቀላቅላችሁ የድርሻችሁን እንድታበረክቱ ኢሕአፓ ጥሪውንያቀርባል፡፡
  5. በተለያየ የሙያ መስክና ተጽእኖ ፈጣሪነት የተሰማራችሁ ሁሉ በዚህ ታሪካዊ ወቅት በተሰማራችሁበት መስክ ሀገርንና ሕዝብን ለማዳን የበኩላችሁን  ድርሻ እንድትወጡ ጥሪያችንን እናቀርባልን፡፡
  6. በመጨረሻም ገዥው ፓርቲ እነሆ ሀገራችን የተደቀነባትን ክፍተኛ አደጋ ለመመከት ምንጊዜም ተጠቂ የሚያደርጉንን መዋቅራዊና ተቋማዊ ተግዳሮቶችንም ነቅሎ በመጣል አሁን እየታየ የሚገኘውን የሀገር ፍቅርና የአንድነት ስሜት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ከዚህ ቀውስም ሀገራችን በአቸናፊነት እንድትወጣ ያላንዳች ማመንታት ግንባር ቀደም  ሥራ በመሥራት ይህን ታሪካዊ ኃላፊነት እንዲወጣ እናሳስባለን፡፡ በዚህ አኳያም ሀገራችን በታሪኳ ታላቅ ቀውስ ውስጥ የምትገኝ ስለሆነ በሀገር ውስጥም ይሁን በዲፕሎማሲው መስክ የሚያስፈልጋት አመራርም በሁሉም መስክ ይህንኑ የሚመጥን ሊሆን ይገባዋል፡፡

 

የኢትዮጵያ ባዕዳን ጠላቶች ይቸነፋሉ!

ኢትዮጵያ በጀግኖች ልጇቿ መስዋዕትነት ታፍራና ተክብራ ለዘለዓለም ትኖራለች!
ኢሕአፓ ለተሻለች ኢትዮጵያ እና ለተሻለ ነገ!

3 Comments

  1. “ኢሕአፓ ለተሻለች ኢትዮጵያ እና ለተሻለ ነገ” – ማለፊያ አባባል ነው። በሃገራችን ውስጥ ከተነሱ ግራም ሆነ ቀኝ ዘመም የፓለቲካ ድርጅቶች ሁሉ እንደ ኢህአፓ ሁሉን አቀፍ የሆነ ድርጅት ተፈጥሮ አያውቅም። ገና በወጣትነታቸው ለአመኑበት ዓላማ በደርግ ጥይት የወደቁ፤ በስቆቃ ውስጥ አልፈው አካለ ጎደሎ የሆኑ፤ ሚስጢር አናወጣም በማለት በምርመራ ውስጥ ህይወታቸው ያለፈ እልፍ ናቸው። የኢህአፓ አወቃቀር እንደ ወያኔና ሻቢያ ስልት ዘርን ቋንቋን ወይም ክልልን ያማካለ ባለመሆኑ በኢህአፓ ውስጥ የነበሩ አመራሮችና ታጋዪች ከየትኛውም የሃገሪቱ ክፍል ተጠራርተው በአንድ ዓላማ ሥር የተሰባሰቡ ነበሩ። በዚህ ድርጅት ውስጥ በአመራርም ሆነ በውጊያው ሜዳ የትግራይ ልጆች ቀዳሚዎች ነበሩ። ግን ምን ያደርጋል። የማይተማመን ባልንጀራ በየወንዙ ይማማላል እንደሚሉት የኢህአሠ ሰራዊት መሳሪያውን ጥሎና ቀብሮ ትግል በቃኝ እስካለበት ድረስ በከተማም ሆነ በገጠር ኢህአፓ ተፋልሟል፤ ተሰውተዋል። በበሽታ ሞተዋል። አሁን ከዚያ የፓለቲካ ነውጥ የተረፉት እይታቸው ሰፍቶ ለሃገርና ለወገን በጭንቋ ሰአት ድምጽ ማሰማታቸው እሰየው ያሰኛል። የሃገራችን ተረት እንደሚለው “እሾህን በእሾህ” ነውና ወያኔን ከሻቢያና ከኢህአፓ የበለጠ ጠንቅቆ የሚያውቀው የለም። ለዚያም ነው የእነዚህ ሁለት ሃይሎች ድጋፍ ዛሬ ከቁራሽ የተረፈችው ሃገር ካለበት መከራ ለመውጣት ሃሳባቸውም ሆነ ድርጊታቸው ደራሽ የሚሆነው።
    የአለምን ታሪክ አበጥሮ ለተመለከተ ብዙ መማር ይቻላል። ለ 45 ዓመት በጃፓን የመከራ ጦስ ውስጥ የነበሩት ኮሪያዊያን በሩሲያና በሌሎችም ጥምረት ጃፓንን ከሰሜን ኮሪያ ጠራርገው ካወጡ በህዋላ ዞረው ተመልሰው አለቃ የሆኑት ሩሲያዊያን ነበሩ። አሜሪካኖች ደግሞ ግማሹን ኮሪያ በመያዝ ኮሪያን ለሁለት ገምሰዋት ይኽው እስከዛሬ አለን። የሚያሳዝነው ግን የኮሪያው መሪ ኪም ኢል ሱንግ በ 80 ዓመቱ አካባቢ ሞት እስከወሰደው ድረስ በሰሜን ኮሪያ ህዝብ ላይ የፈጸመው በደል ጃፓኖች ከፈጸሙት ይበልጣል። ከዚያም ልጅን አሁን ደግሞ የልጅ ልጅ ስልጣን ላይ በመሆን የሰሜን ኮሪያን ህዝብ በባርነት ይነድታል። ለዚህ ሁሉ መንሴኤዎቹ ግን ራሽና አሜሪካ ናቸው። ለሰው ልጆች መብት ቁሜአለሁ የሚሉን አሜሪካኖች በ 50ዎች በሰሜን ኮሪያ በተደረገ ፍትጊያ ከሁለት ሚሊዪን በላይ የሆኑ ኮሪያዊያንን በአየር ድብደባ ብቻ እንደፈጅ ታሪክ ያወሳል። ያ የውጭ ፓሊሲያቸው ዛሬም አልተቀየረም። ለዚያ ነው ኢራቅ፤ ሊቢያ፤ የመን፤ ሶሪያ አሁን ደግሞ አፍጋንስታን የወንጀለኞች መፈንጫ የሆኑት። ታዲያ ይህ የማያነቃው ጥቁር ህዝብ አሁንም ወንድምና እህቱን እየገደለ ሲፎክር ማየት እንዴት ያሳፍራል? የሱዳን መንግስት የኢትዮጵያ አምባሳደሩን ጠራ ይለናል ወሬ ነጋሪው። ሲዳን የራሷ ሲያርባት እንዲህ በለለ ቤቷ የኢትዮጵያን ድንበር መያዟ የአሜሪካ አይዞህ ባይነት እንዳለበት አያጠራጥርም። የሱዳንና የአሜሪካ ፍቅር ሞቅ ሞቅ ማለቱ ደግሞ ለአሜሪካ ጥቅም እንጂ የሱዳን ህዝብ ምንም አያተርፍም። በነጮች የቀን መቁጠሪያ በያዝነው ዓመት በተሰላ ሂሳብ ሱዳን 400% የዋጋ መናርን እያስተናገደች ህዝቦቿም ፍትህና የሚበላ እየጠየቁ እንደሆነ ይነግሩናል። ግን ከጎረቤት ሃገሮች ጋር እንዲላተሙ እሳትና ምክር የሚያቀብሉት አሜሪካኖች ናቸው። በዚህ የፓለቲካ አሻጥር ግን የሚያተርፍ የለም። ለሱዳንና ለኢትዪጵያ ህዝብ የሚበጀው ሰላምና አብሮ መኖር ብቻ ነው። ይህ ግን ወያኔ እያለ አይሳካም። የኢትዮጵያ ጠላት ወያኔ አይደለም መጠለያ፤ ትጥቅና የዝውውር የነጻነት የሚሰጠው በተለይም የሱዳን ወታደራዊ አገዛዝ እንጂ። ታዲያ ይህን ሁሉ ምን አመጣው ጽሁፉ ስለ ኢህአፓ መግለጫ ነው ይል ይሆናል ያልገባው። የኢህአፓና የሌሎች ተቀናቃኝ ሃይል አባላትን ይዞ ለወያኔ ያስረከበ የሱዳን መንግስት ነው። ብዙዎቹ በወያኔ ተረሽነዋል። ዛሬም የወያኔና የሱዳን ባለስልጣኖች ጥምረት ሃገራችንና ህዝባችን ለመከራ እየዳረገ ነው። ስለሆነም ከሞትና ከደርግ የሰቆቃ ድላ የተረፉት የኢህአፓ አባላት የሚወዷት ሃገራቸው ዛሬም ትፈልጋቸዋለችና በሚችሉት ሁሉ ወያኔና የውጭ ሃይሎችን መፋለም አለባቸው። የተሻለ ነገ ሊፈጠር የሚችለው ሰው በሰውነቱ ሲመዘን ብቻ ነው። 70 ዓመት የተለፋበት የራሽያው ሶሻሊዝም/ኮሚኒዚም ከእጅ እንዳመለጠ ሸክላ ፍርክርኩ ሲወጣ ማየት ምንኛ በሌኒን/በስታሊንና በሌሎችም ዘመነ ሙታን ግፊት ያለቁት ራሽያዊያን ህይወት ከንቱ እንደሆነ ያሳያል። እብዶች በጀርመን፤ በሩሲያ፤ በኢትዮጵያ፤ በዪጋንዳ፤ በአርጀንቲና፤ በቺሌ በሌሎችም ስፍራ ተነስተው ብዙ አጥፍተው ከስመዋል። የወያኔም ህልፈት በደጅ ነው። ወያኔ ካለ የትግራይ ህዝብ በሰላም መኖር አይችልም። ኢትዮጵያም ሰላም አይኖራትም። ወያኔ መወገድ ያለበት ጥርሱ አልቆ በድድ ብቻ የሚያመነዥክ አልጠግብ ባይ የሙታን ስብስብ ነው። በቃኝ!

  2. ወቅቱ የሚጠይቀውን መግለጫና የአንድነት ጥሪ ስላቀረባችሁ በግሌ እጅግ አደንቃችኋለሁ። ብዙ ወገናችን ጥሪአችሁን ተቀብሎ የሚተባበር ይመስለኛል። ሰው በጠፋበት ስዓት የሃገር ጠበቃ ሆናችሁ በመቅረባችሁ ክብር ለናንተ ይሁን። ሰማነህ

    • ትክክል ነው ስሜነህ ይህን የሀገር ጥሪ ለማጠናከር ተቃዋሚዎች በአስቸኳይ ምክክር እንዲያደርጉ ያስፈልጋል፡፡ ሁላችንም ይህ እውን እንዲሆን በያለንበት እንወትውት፡፡ ሀገር ማዳን Yእሁላችንም ተግባር ነው

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share