April 11, 2021
5 mins read

አይ የሰው ነገር! የጥላቻ አጥር ክልል- በአልማዝ አሰፋ – ዘረ ሰው

የጥላቻ አጥር ክልል

አይ! የሰው ነገር
በአልማዝ አሰፋ – ዘረ ሰው

206 አጥንት : ሰውነታችን አዝሎ
ሁለት ዓይኖች ይዘን: ምስለ አሎሎ
አይታያቸውም እንዴ : ቢወራ ተብሎ
አይተን እንሸሻለን : ቢገጥመን ቀን ጎሎ::
እውነትን ከውሸት : ለመስማት ለይተን
የፈጠረን ጌታ : ሁለት ጆሮ ሰጠን::
አደጋ ሲያጋጥመን : ብር ብለን ለመሄድ
ሁለት እግር ፈጥሯል : ቆመን ለመራመድ::
እነዚህ የአካል ክፍሎች : ስራ ተሰጧቸው
በሚገባ ረገድ : ሲሟላ ሚናቸው
አይ የሰው ነገር : ዋጋ አሳጣቸው::
ማየቱስ ይቅርብን : አልታደልንም እኛ
መራመዱም ይቅር : እግራችን እስረኛ
እንዴት ማንቃት ይቻል? ውሸት ላይ የተኛ::

በጎሳ ስም ይሁን : ወይም በብሔሩ
ሕዝብን ሲያንገላቱ : ስቃይ ሲጨምሩ
መኖርያ ሲያሳጡ : ሰውን በአገሩ
የሰው ልጅ መሆናቸው : ጠፋቸው ነገሩ?
የእኔ ጎሳ እንዲ ሲል : የእኔ ጎሳ እንዲያ
ሸቀጥ አስመሰሎ : ዘር አዘል ጆንያ
ይመስላል ነጋዴ : ሚወጣ ገበያ::

ልዩነት የሌለው : ይህ የሰው ፍጡር
እርስ በርስ ሲባላ : በማይረባው ነገር
ተባብሮ ከመስራት : አገር ከማዳበር
ግዜውን ይፈጃል : ጥላቻን ሲያዋቅር::
እዩት ይህን ጉድ : ለሰው ማይሰጥ ዋጋ
ለሌላው አስቦ : ራሱን ሚወጋ::
ኧረ ሰከን በሉት: ቱክ ቱክ አብርድ
ይቅርብህ ወንድሜ : በክፋት ማበድ::

ጎሳ ጎሳ ስትል : ቋንቋን መሪ አድርገህ
ከፈረሱ ጋሪ : እያልክ አስቀድመህ
እኔን አምሳልህን: መቀበል ተስኖህ
እውነት ቅጀት ሆኖ : ሰላምን አጥተህ
በእንክሮ ማሰቡ : እንዳስቸገረህ
መሆንክን ስረዳ : ፍፁም ማይገባህ
ምን እንደሆንክ አንተ : እስቲ ልጠይቅህ
መነሻህን ልወቅ : ስለአፈጣጠርህ
የሰው ዘር ወይስ አውሬ : ከየት ነው አመጣጥህ?

ይህ ሁሉ ክፋት: ንብረት ስታቃጥል
ያ ሁሉ ጭካኔ : የሰውን ልጅ ስትገድል
ከተወለደበት ከኖረበት መሬት: ሰውን ስታፈናቅል
የኔ ቤተሰብ ቢሆን : ምንስ ይሰማኛል
ብለህ በማሰብ : ራስህን ጠይቀሃል?

ኦሮሞ ተበድሎ : አማራ አልደላው
ሲዳማ ተጎድቶ : ወላይታ አልተመቸው
ትግራይ ጠግቦ ሳለ : ጋምቤላ አልራበው
ሱማሌ ሲዝናና : አፋር አልቅሶ ነው?
በድህነት ቀንበር : ደክሞ ሰውነታቸው
ማየት ተስኖህ ነው? ሁሉም አፈር መስለው
ጎሳ ጎሳ እያልክ : ቱልቱላ ምትነፋው
ማንኛው ደልቶት ነው : ጎሳን ያስቀደምከው?

ልንገርህ ወንድሜ : ሰው ነኝ ለምትለው
ተማርኩኝ ብለህ : እውቀትን ላቀፍከው
ጥቅምን አስቀድመህ : ሕዝብን ለረሳኸው
ሰው መሆን ትተህ : ጎሳን ላራመድከው
ጎሰኝነት አዝለህ : በነጭ አገር : ጥገኛ ለሆንከው
ሻንቅላ ባሪያ : ኒገር ለተባልከው
በጥላቻ ምክንያት : ስድብ ለቀመስከው
ሰው መሆንህ ሳይታሰብ : ውርደት ለለበስከው
በሰፈሩት ቁና : መሰፈር እንዲህ ነው::
አንተ ስትሰደብ : አገር እንደሌለህ
ስሜትህ ተነክቶ : ሃዘን ላይ ወድቀህ
የሰው ያለ ስትል : መፅናናት ፈልገህ
ታዲያ ለምን ብለህ ሌላውን : አገር ታሳጣለህ?

እንግዲህ ተረዳ : ይግባህ ማንነቴ
ጎሳ ቋንቋ ሳይሆን : የማ ልጅነቴ
ከ200 በላይ : ተቆጥሮ አጥንቴ
ባለ ሁለት አይን : ተጣርቶ ማየቴ
ሁለት ጆሮ አለኝ : እርግጥ ነው መስማቴ
በሁለቱም እግሮቼ : ቆሞ ሰውነቴ
እንዳንተ ሰው አለመሆኔን : አስረዳኝ በሞቴ::

በጣም ያሳዝናል : ያንተማ ነገር
ያንተው ተመሳሳይ : የእግዚአብሔር ፍጡር
ሰው መሆኔን ትተህ : ጎሳ ስትቆጥር
አንተ ሰው መሆንህን : ምን ብዬ ልናገር?
ሰው ለመሆንህስ : ምን ይዤ ልመስክር?

አይ የሰው ነገር : መተሳሰብ ትተን
አይ የሰው ነገር : ሰባዊነት ከድተን
የሰው ልጅነት : ዘር መሆኑ ረስተን
የጥላቻ አጥር : ክልልም ከልለን
እንባላ ጀመር : ከአውሬም አንሰን::
አውሬ አስተዋይ ነው : አለው መላ መላ
እንደዘመኑ ሰው : ዘሩን ሳያጥላላ
ወገኑ ሲጠቃ : በመቆም ከለላ
አውሬ ዘር ያውቃል : እንደጎሰኞቹ ወገኑን አይበላ::

ሰላምና ብልፅግና ለኢትዮጵያና ለሕዝቦቿ!!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

eeeeew
Previous Story

ማን  ምን እንዲል  እንጠበቅ ?  – ማላጂ   

የማንቂያ ደወል
Next Story

ኢትዮጵያ የዮጎዝላቪያ እጣ ፋንታ እንዳይገጥማት የሚል ስጋትን ማጋራት ሟርት ሳይሆን ውስጣዊ አንድነቷን አጠናክራ የውጭ ጠላትን መመከት እንድትችል የሚቀርብ የማንቂያ ደወል ነው!!!

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop