አማራን ነጥሎና አሳድዶ ማጥቃት የመጨረሻ ግቡ ኢትዮጵያን ማፍረስ ነው! – አንድነት ይበልጣል – ሐዋሳ

አንድነት ይበልጣል – ሐዋሳ – መጋቢት 27 2013

“የጄኖሣይድ” ፕሮጀክቶች

“ጄኖሣይድ”

“ትግራይ ጄኖሣይድ”፣ “አማራ ጄኖሣይድ”፣ “ኦሮሞ ጄኖሣይድ”፣ “ቅማንት ጄኖሳይድ”፣ “ወላይታ ጄኖሣይድ”፣ “ጉሙዝ ጄኖሣይድ” ወዘተ፣ እነዚህ ሁሉ የወያኔ፣ የግብጽና የኢትዮጵያ ጠላቶች የአዞ እንባዎች ናቸው! ዓላማቸው የሕዝብን የህልውና ችግር ከሥሩና ለዘለቄታው መፍታት አይደለም፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያን የማፍረሻ ሥልቶች ናቸው፡፡  የነዚህ ጩኸቶች ዓላማ የኢትዮጵያን ሕዝብ ለውጥና ለውጡን ተከትሎ የሚመጣውን ሐገራዊ ጥንካሬ ማኮላሸት ነው፡፡ በዚህም ግርግር፣ ወንጀለኞች የራሳቸውንና የኢትዮጵያን ጠላቶች ድብቅ ፍላጎት ማሳካትን ያልማሉ፡፡

የጄኖሣይድን ጉዳይ ፕሮጀክት በማድረግ እንደ ታፔላ ብቻ የመለጠፍ እኩይ ስልት እያየን ነው፤ የዚህ ፕሮጀክት ዋና አካል ሆኖ፣ ኢትዮጵያንም ለማፍረስ ያስችላል ተብሎ የተያዘው አንድ ሥልት፣ የአማራን ሕዝብ ማጥቃት፣ ማስቆጣትና ማማረር ነው፤ ሌላው ደግሞ፣ የአማራ ክልል መስተዳድር አመራሮችን መተንኮስ፣ ያለበቂ ምክንያት ማሳጣትና መኮነን፣ ስማቸውንና ሥራቸውን ማጠልሸት፣ ውጥረት ውስጥ መክተትና ሚዛን ማሳጣት ነው፡፡

አማራን ማስቆጣት፣ ማማረር

አማራ በመላ ኢትዮጵያ ተበትኗል፤ በተገኘበት ሁሉ በማጥቃት በተለይ በክልሉ የሚኖረውን የአማራን ሕዝብ የማማረር ሤራ ነው የተያዘው! የአማራ ሕዝብ ብሶትና ቁጣው ገንፍሎ፣ ከሁሉም በፊት ከአማራ ክልል መስተዳድር፣ በወዲህ በኩል ደግሞ ከፌዴራል መንግስትና በመጨረሻም ከመላ ኢትዮጵያ ጋር እንዲጣላና እንዲጋደል ነው የተፈለገውና እየተሠራ ያለው፡፡

አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ፣ የአማራ ክልል አመራሮች፣ የአማራን ጭፍጨፋ ለማስቆምም ሆነ በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ ችግሮች ትልቅ የመፍትሔ አካል ናቸው፡፡ እናም በአማራ ክልል አመራሮችም ላይ ከፍተኛ ጫና በማድረግና ተቃውሞ በማስነሳት፣ ተዓማኒነት የማሳጠትና ከጨዋታ ውጪ የማድረግ ደባ እየተሠራ ነው፤ በተጨማሪም የትግራይም፣ የአማራም፣ የኦሮሞም፣ የቤኒሻንጉልም ስም ለሚለጠፍባቸው፣ በአብዛኛው የፈጠራ ለሆኑ ጄኖሣይዶች ፌዴራል መንግሥቱን (የለውጡን ቡድን) ተጠያቂ የማድረግና በሕዝብ እንደ ጠላት እንዲታይ በማድረግ መግፋትና ከጨዋታ ውጭ ማድረግ ነው የተያዘው፡፡

የዚሀ ሤራ የቅርብ ውጤቱ፣ በተለይም የአማራን ሕዝብ በኢትዮጵያዊነቱና በአንድነቱ ተስፋ ማስቆረጥ፣ በአማራ ክልልና በፌዴራል ደረጃ ያለውን የለውጥ አመራር ማፍረስ፣ በክልሎች የለውጥ አመራሮች መካከል ያለውን አንድነት ማናጋትና ኢትዮጵያን በዚህ ክፉ ጊዜ አውራ-አልባ ማድረግ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከመሠረታዊ  ዴሞክራሲያዊ   የሥርዓት ለውጥ ውጭ ሌላ መውጫ መንገድ የለም!

አማራ በክልሉ አመራሮች ላይ ዕምነት እንዲያጣ ማድረግና ከፌዴራል መንግሥት ማፋጠጥ፤

ለምሳሌ በቅርብ ቀን ኦነግ/ሸኔ በምዕራብ ወለጋ በአማራ ተወላጆች ላይ የፈጸመውን ጭፍጨፋ በሚመለከት የአብን ሊቀመንበር የሆነው ሰው (በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ) የሰጠውን ምክር እንመልከት፡፡ በዚህ ምክሩ፣ “የአማራ ብልጽግና ዋናውን የብልጽግና ፓርቲ ፕላት ፎርም ገምግሞ ድርጊቱን ተቃውሞ አቋርጦ መውጣት አለበት” ብሏል፡፡ በዚህ ምክሩ ላይ የኮንቪንስና የኮንፊዩዝን የፖለቲካ ቁማር ጨምራችሁ ስትመለከቱ የተጋረጥብን አደጋ ምን ያህል ከፍተኛ እንደሆነ መረዳት ትችላላችሁ፡፡

ይህ በፓርቲ ሊቀመንበር ደረጃ የተሰጠ ምክር ቢደመጥና እንዳለ ቢተገበር የሚያስከትለውን ውጤትና የሚኖረውን አንደምታ እስኪ ገምቱት፡ (ሊቀመንበሩን ለማሳያ ያህል ጠቀስኩ እንጂ የምክረ ሀሳቡ ባለቤት የሆኑ እኩያን እና የዋሐን ብዙ ናቸው፡፡)

በተለይ በአሁኑ ጊዜ (ከምርጫ በፊት፣ የውጭ ኃይሎች አደጋ በተጋረጠበት ወቅት) የአማራ ክልል/ፓርቲ አመራሮችን ከብልጽግና ውጡ ማለት …

– በፌዴራል መንግሥት ያላችሁን ሥልጣን አስረክባችሁ ወደክልላችሁ ውጡ/ውረዱ፤

– ከፌዴራል መንግሥትም ሆነ ከሌሎች ክልሎች ጋር ያላችሁን ግንኙነት አቋርጡ፤

– እንደፈረሰው የወያኔ የክልል አገዛዝ ራሳችሁን ለዩ፣ ባታውጁትም (De-Facto) የተገነጠለ የክልል አስተዳደር መሥርቱና ከሁሉም ጋር ተፋጠጡ (የራሳችሁን ምርጫም አካሂዱ)፤

– ከአማራ ክልል ውጭ (በኦሮሚያ፣ በደቡብ፣ በቤኒሻንጉል ወዘተ) በአረመኔዎች እየተጨፈጨፉ የሚገኙ የአማራ ወገኖቻችንን ለመታደግ፣ ጀግናውን የአማራ ክልል ልዩ ኃይልና ሚሊሻ (ፋኖንም) ከነዚህ ክልሎች ልዩ ኃይሎችና (ዞሮ ዞሮም ከጀግኖቹ የመከላከያና የፌዴራል ፖሊስ ኃይሎች ጋር) እንዲዋጋ አድርጉ፤ ወዘተ

የአማራ ክልል ልዩ ኃይል፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል (መተከል)፣ ደቡብ ክልል (ጉራፈርዳ)፣ ኦሮሚያ ክልል (ምሥራቅና ምዕራብ ወለጋ፣ ምሥራቅና ምዕራብ ሐረርጌ) በራሱ ፈቃድ ብቻ ዘምቶ ከየክልሎቹ መንግሥታት ጋር ሲዋጋ እስኪ ይታያችሁ!

ተጨማሪ ያንብቡ:  እንዳንደናገር እንጠንቀቅ፣ - ክገብረ አማኑኤል

ለመሆኑ በምን ስሌትስ ነው፣ በየቦታው ለሚጨፈጨፉት ንጹሃን የአማራ ተወላጆች፣ የአማራ ክልል መንግሥትና የአማራ ክልል ነዋሪዎች ብቻ መቆርቆርና መቆጣት ያለባቸው? የብሔር ብሔር ጨዋታ ሥሌት? አጉል ልምድ? ወይስ ለጀማሪ የብሔር ተቆርቋሪዎች ፋሽን መሆኑ ነው? እኔ በጣም የሚገርሙኝ በወያኔ ጠንሳሽነትና አጋፋሪነት 40 ዓመት ሙሉ ተሞክሮና ተተግብሮ መክሸፉ ወደተረጋገጠው ወደዚህ የድንቁርና ሠፈር እንደአዲስ እየዘለሉ የሚገቡ ጨዋ ሰዎች ናቸው!

 

እስኪ የሚከተሉትን ጥቂት ቀላል ጥያቄዎች በየግላችን እንመልስ፤

– በአንድ በኩል በአማራ ሕዝብና በክልሉ መስተዳድር መሪዎች፣ በሌላ በኩል በሌሎች ክልሎች ህዝቦችና መስተዳድሮች መካከል እንዲኖር በምንጎተጉተው በዚህ መለያየት፣ ፍጥጫና ግጭት ውጤት በእርግጥ የአማራን ጭፍጨፋ ማስቆምና በሐገራችን ሰላም ማስፈን ይቻላል?

– በእርስ በርስ ግጭቱ ውጤት፣ ከእልቂት ውጭ ስለመጪው ምርጫና ወደ ዴሞክራሲና ወደ ሰላም ስለመሸጋገር ማሰብ ይቻላል?

– በእርስ በርስ ግጭቱ ጊዜና በማግሥቱ፡

– ስለሕዳሴ ግድብ ውኃ ሙሌትና ሙሉ ሥራውን ስለማስጀመር፣ የሕዝባችንን የመብራት፣ የሐይልና የተጨማሪ ገቢ ፍላጎት ስለማሟላት ማሰብ ይቻላል?

– ግብጽና ተባባሪዎቿ የደቀኑብንን የህልውናና የሉዓላዊነት አደጋ ለመመከትና ለማስቀረት የሚበቃ ቁመና ይተርፈናል?

– ወይስ የጎርጎራና መሰል የልማት ፕሮጀክቶችን ዳር አድርሶ ዘርፈ-ብዙ አካባቢያዊ፣ ክልላዊና ሐገራዊ ጥቅሞችን ማረጋገጥ ይቻላል?

እየተቀሰቀሰ ካለው የእርስ በርስ ፍጥጫና ከግጭቱ ምንድነው የምናገኘው? የምናጣውስ? ብሎ በእርጋታ መጠየቅ፣ ማሰብ፣ ማመዛዘንና ግልጽ አቋም መያዝ ይገባል፡፡

ለማጠቃለል፤

– በአማራ ክልል አመራሮች ላይ ተገቢ ያልሆነና ከልክ ያለፈ ጫና በማድረግ ሚዛን የማሳጣትና የማዛል ተንኮለኛ ሥራ እየተሠራ ነው፤

– በሰበባ-ሰበብ የኦሮማራን ሕብረት ለማፍረስም እየተሠራ ነው፤

– ከዚህም አልፎ ሁሉም ክልሎች እርስ በርስና ከፌዴራል መንግሥት ጋር እንዲገፋፉና እንዲጓተቱ እየተሠራ ነው፤

የዚህ ሁሉ ሤራ የመጨረሻ ግቡ ሐገሪቱን ወደ እርስ በርስ ጦርነት ማስገባትና ከተቻለም ማፍረስ ነው፤ ይህ ነው የተደገሰልን፡፡ ዘመዶች፣ እንንቃ!

ተጨማሪ ያንብቡ:  [የሚኒሶታው ደብረሰላም መድሃኔዓለም ጉዳይ] - ማን ለጠበቃ ፈረመ???

ወያኔም ሆነ ኦነግ (በግብጽ እየተደገፉ)፣ ያለፈውን ትተን፣ በአሁኑ ሰዓት በንጹሃን ላይ ግፍ የሚፈጽሙት / የሚያስፈጽሙት፣ የሚጨፈጭፉትን ሕዝብ መልሶ ወይም እንደአዲስ ለመግዛት በማለም አይደለም፡፡ ዓላማቸው ግፍ በፈጸሙበት ሐገርና ሕዝብ ላይ ተመልሶ ወይም እንደ አዲስ ባለሥልጣን ለመሆን አይደለም፡፡ ይህ እንደማይቻል ማለትም በፊትም ሆነ አሁን የጨፈጨፉት ሕዝብ ጨርሶ ሊገዛላቸው እንደማይችል ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡ ስለዚህ ትልቁ ዓላማቸውና እናሳካዋለን ብለው የገመቱት፣ የተዳከመችና የተበታተነች ኢትዮጵያን ለጠላቶቿ ለነግብጽና ለሌሎች የውጭ ኃይሎች አሳልፎ መስጠትና በሩን ከፍቶ ማስገባት ነው፡፡ ይህ ውጤት የሚሰጣቸውን ትርፍራፊ ጥቅም እናጣጥማለን ብለው አስበውም ይሆናል፡፡ ነገር ግን ፈጽሞ አይሳካም! ፈተናውና መከራው የበዛውን ያህል ቢበዛም፣ እነወያኔ በ40 ዓመት “የጉብዝና ወራት” እንኳን ሊያሳኩት ያልቻሉትን ኢትዮጵያን የማፍረስ ሤራ ዛሬ ፈራርሰው፣ ሲዖል ሆነው፣ በየቃሊቲው ተወርውረውና በየሥርቻው ተበታትነው መተንፈስ ባቃታቸው ጊዜ ሊያሳኩት አይችሉም! ቅዠት ነው!

ኢትዮጵያውያን እንንቃ! በጊዜ ካልነቃን ብዙ ጉዳት እናተርፋለን፤ ይህ ብቻም አይደለም፤ ኢትዮጵያ ባትፈርስም፣ ትዝብት ላይ መውደቃችንና የኋላ ኋላ ለትልቅ የግል ጸጸትና ሐፍረት መዳረጋችን የማይቀር ነው፡፡ አሁንም አልረፈደም፤ የኢትዮጵያ ጠላቶችን ሤራ፣ መላ ኢትዮጵያውያን ያለአንዳች ልዩነት፣ መዘናጋትና ማመንታት በአንድ ከፍተኛ የቁጣ ድምጽ እንቃወመው፣ ታግለን እናሸንፈው! የትኛውንም ጄኖሣይድ በአንድነት ተዋግተን እናሸንፈው!

አሁን በአማራ ወገኖቻችን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጭፍጨፋ አማራ፣ ኦሮሞ፣ አፋር፣ ሶማሌ ወዘተ ሣንል ሁላችንም በአንድነት እናውግዝ፣ እንታገለው፡፡ የአንድ ንጹህ አማራ ሕይወት መጥፋት፣ አካል መጉደል፣ መፈናቀል መላ ኢትዮጵያውያንን ሊያስቆጣ ይገባል፡፡ በዚህ አካሄድ ነው አማራንም ከጭፍጨፋ፣ ኢትዮጵያንም (ባትፈርስም) ከከፍተኛ ጉዳት መታደግ የምንችለው፡፡ የውሸት ጄኖሣይዶችን አጭበርባሪ ጩኸት ያለይሉኝታ እናጋልጥ! በእርግጥም የሚፈጸሙ ጄኖሳይዶችን ደግሞ ያለአድልዎ በአንድነት ታግለን እናስቁማቸው!

ኋላ እንዳይቆጭሽ …

ፈጣሪ ይርዳን!!

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share