እውን ኩሩዎች ነን? – ጠገናው ጎሹ

ተብለን ብንጠየቅ ኩሩነት ምንድነው ?

ኩሩው ሰውስ ማነው?

እንዴት ብለን ይሆን ምላሽ የምንሰጥው?

እንዲያው በደምሳሳው እንዳይሆን መልሳችን

እስኪ ኩሩነትን

በምሳሌ አስረዱን ብለው ቢጠይቁን

እውን ወኔው አለን?

ፊት ለፊት ላይ ወጥተን

ብለን ለማስረዳት እኛው ምሳሌ ነን!

ከዓመታት ውድቀት ባለመማራችን

ስለ ጨነገፈው ‘የለውጥ’ ትርክታችን

ብንባል አስረዱን

በልበ ሙሉነት በአደባባይ ወጥተን

በእውነት ችሎት ፊት ስለ እውነት ቆመን

ለመስጠት ቃላችን

የእምነት ክህደታችን

ወኔው የማይገደን

እውን ኩሩዎች ነን?

ብንባል ንገሩን ወይንም አስራዱን

ዋነኛ ምክንያቱን

ሽቅብ ወጣን ስንል ቁልቁል የመውረዱን

የሞራል ውድቀቱን

የመንፈስ ድቀቱን

የኑሮ ምሬቱን

ተስፋ የማጣቱን

መከራና ውርደት የመለማመዱን

በእውነት ስለ እውነት ግልፅልፅ አድርገን

በአርበኝነት ወኔ እንመሠክራለን?

ወይስ እንደ ለመደብን

የሰበብ ድሪቶ እንደራርታለን ።

አዎ! የሰው ልጅ መገኛ ስለመሆናቸን

የአርኪኦሎጅው ግኝት ያረጋገጠልን

የሉሲ አገር ሰዎች ኢትዮጵያዊያን ነን ።

አዎ! የእነዚያ ልጆች ነን

አገረ ኢትዮጵያን

በደምና በአጥንት ጠብቀው ያቆዩን

ያለፉ አውርሰውን

ወርቃማ ውርሳችን

የታሪክ ቅርሳችን

አገረ ኩራትን

ከእኛ አልፎ በዓለም የታወቅንበትን።

ነገር ግን የእኛ እውነት

የዘለቅንበቱ ለሩብ ምዕተ ዓመት

አሁን ያለንበት

ከቶ አይናገርም የእኛን አርበኝነት

አገርን የማድረግ የፍትህ የነፃነት ።

ሃቁን እየሸሸን ማስመሰሉን ትተን

እስኪ እንጠያየቅ ግልፅና ግልፅ ሆነን።

የትውልድ ድርሻችን እውን ተወጥተናል?

ከዘመናችን ጋር አብረን ዘምነናል?

በአስተሳሰብ መጥቀን በአሠራር ልቀናል?

ከድህነት አዘቅት ለመውጣት ጥረናል?

ተመፅዋችነቱ እውን ሰልችቶናል ?

የስደት ላይ ሞቱ ወይንም ውርደቱ በእውነት መሮናል?

ወይስ ተላምደነው አልታየን ብሏል?

የከፈልንበትን መሪር መስዋእትነት

ሞቶ ይቀበር ዘንድ የመከራው ሥርዓት

ተጨማሪ ያንብቡ:  አልቃሾ - በመኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ 

በእውን እውን ሆኖ የአዲስ ሥርዓት ውልደት

የፍትህ የነፃነት

የፍቅር የእኩልነት

ብሎም የጋራ እድገት

መልሰን መላልሰን የምናመክንበት

ምድነው ጋግርቱ የተለከፍንበት?

እንኳን ሥርዓት ልንፈጥር ለእኛ የሚበጀን

በአንድ አገር ህዝብነት በአብሮነት ቆመን

የአደራ ውርሳችን

አኩሪ ታሪካችን

ያስተሳሰረንን የፍቅር ክራችን

ከአጥፊዎች ጠብቀን

ደግሞም ተንከባክበን

ማቆየቱ ከብዶን

በነጋ በጠባ እግዚኦ! እንላለን

ሸፍጠኛ ገዦችን እንማፀናለን።

ታዲያ በየት በኩል

ኩሩዎች ነን እንበል?

አዎ! ኩሩነት እሴት ነው ያውም ወርቃማ እሴት የበጎ ሰብእናን ስፋትና ጥልቀት በእውነት ስለ እውነት የምንለካበት የዜግነት ልኩን የምንመዝንበት ሚዛኑ ሲዛባ የምንጠይቅበት ባለጌ ገዦችን የምንሞግትበት የሸፍጥ ፖለቲካን በቃ እምንልበት። ግን ፍትህ የት ሊመጣ ከሌለ ኩሩነት ኩሩነት ከሌለስ የት አለ ነፃነት? ውሸትና ሸፍጥን ባልተፀየፍንበት

በየት በኩል ይግቡ ፍቅርና አብሮነት ?

ጥያቄው ጠፍቶብን የተነሳንበት

የሥርዓት ለውጥ ይሁን! እያልን የጮህንለት

ወደ ቁማርነት በተለወጠበት

የጋራ አገር ስሜት በኮሰመነበት

የአርበኝነት ወኔ ብርቅ በሆነበት

የተዘጋው በርስ እንደምን ይከፈት?

ለውጥስ እንዴት ይምጣ ኩራት በሌለበት ?

በነፈሰበቱ አብረን እየነፍስን

በስሜት ትኩሳት ሽምጥ እየጋለብን

ለሸፍጠኛ ገዦች ውዳሴ እየዘመርን

ሙሴ ሥጋ ለብሶ ተነሳልን እያልን

መከረኛውን ህዝብ ግራ እያጋባን

ከዋናው ጥያቄ እያንሸራተትን

ትግልህ ፍሬ አፍርቷል በሚል እያታለልን

ይኸው በዚህ ዘመን

ዓለምም ታዘበን

እኛም በእጅጉ አፈርን።

እናም ነገራችን ሁሉ የተበለሻሸው

የሸፍጠኞች ዲስኩር ሰለባ የሆነው

ገና ከጅምሩ ለውጥ ፈነዳ ብለን የፈነዳን እለት ነው።

ታዲያ እንደዚህ እየሆን

እውን ኩሩዎች ነን?

ከእኛ ወዲያ ምሁር ወይም አስተማሪ ላሳር ነው እያልን የመማር ትርጉሙን ወደ ከርስ መሙያነት ዝቅ እያደረግን ግፍና መከራን ያላየን ይመስል ፀጥ ብለን እያለፍን ከዚህም በከፋ የሸፍጥ ፖለቲካ ተንታኞች እየሆን

ተጨማሪ ያንብቡ:  ወላፊንድ አሥተሳሰብ ካለን “እኛ ሰው ነን ።”ማለት ይከብደናል (መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ)

ትውልድ መቅረፅ ሳይሆን ትውልድ እየገደልን

ምኑን ኩሩዎች ሆን?

በግፈኛ ገዦች ህሊና ቢስነት

በእኛው በእራሳችን ልክ የሌለው ውድቀት

ለሩብ ምእተ ዓመት ለተዘፈቅንበት

ዛሬም ላጋጠመን የለውጥ ጭንጋፍነት

በሸፍጠኛ ገዦች ለተዋረድንበት

ድርሻቸው ጉልህ ነው የሃይማኖት ተቋማት።

ቃሉ (መጽሐፉ) እንደሚያዘን

በእውነት ስለ እውነት እንነጋገር ካልን

እስከዚህ ድረስ ነው ግልፅነት የሚያሻን ።

የሞራል ልእልና በኮሰመነበት

ቃል መሬት ላይ ወርዶ ህይወት ባልዘራበት

አስመስሎ መኖር በተንሰራፋበት

እውነተኛ ሰላም ቅንጦት በሆነበት

የፍቅር ውበቱ ለዛው በጠፋበት

ልክ ያጣው ድህነት

ሥጋንና ነፍስን ወጥሮ በያዘበት

ተማርኩ ያለው ሁሉ በደነቆረበት

ወንጀለኛ ገዦች ባልተወገዱበት

የበሰበሰና የከረፋን ሥርዓት

ታድሷል እያሉ በመከረኛው ህዝብ በሚሳለቁበት ህዝብም ግራው ገብቶት

ከላይ ፈጣሪውን በሚማፀንበት

ከታች ገዥዎችን ደጅ በሚጠናበት

በዚህ አስከፊ ወቅት

የሃይማኖት መሪዎች ከተለመደው ውጭ ምን አደረጉለት?

ታዲያ በዚህ ሁኔታችን

እውን ኩሩዎች ነን ?

እናም የሚሻለው ወይም የሚበጀው

ሃቅን በመቀበል ከወደቅንበቱ ፈጥኖ መነሳት ነው።

ፈጥነን በመነሳት ነፃ የወጣን እለት

ይነግሳል ኩሩነት

የኢትዮጵያዊነት!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share