ሃጫሉ፣ህግን የበላይ ያደርጋታል፣ፍትህንም ያነግሳታል። – ትህዳ ኃሣኤ ዘ ናዝሬት

እንደመግቢያ የፀጋዬ ገ /መድህን ቀዌሳን “ኢትዮጵያዊነት” የተሰኘ ግጥምን በጥቂቱ ላቅምሣችሁ።
ኢትዮጵያዊነት
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ቀዌሣ

ኢትዮጵያዊነት ማተብ ነው፣በአካልና መንፈስ ፅናት
በአብው ታሪክ አምኖ መኩራት።
ኢትዮጵያዊነትን መካድ፣ የፍቅር አምላክን ሲሳይ፣
መረገጥ ነው እንደ እኩይ ጠባይ
የአንድነትን አድባር ፣ ፈንግሎ ለመናፍቃዊ ግዳይ
በትውልድ ላይ ሰቆቃ፣የአካልና መንፈስ ሥቃይ
ማንገሥ ብቻ ነው ውጤቱ፣ በራሥም ለይ በህዘብም ላይ።
የኢትዮጵያዊነት መሥፈርቱ ነፃነት ነው፣ ለአንድ ዜጋ
መንፈሳዊ ነው እሴቱ፣ የማይዳሽቅ ለሥጋ
የማይበገር ለጠመንጃ፣የማይተመን በዋጋ
መንፈሱን ቆርሶ ለመሸጥ ፣ሳይሆን እነደ ባንዳ መንጋ።
ወይ እንደትላንትኖቹ፣ለዙፋን ባርነት ሳይሆን
ወይ ለጦርነት መኮንኖች ምርጥ፣ለማጎብደድ ለአንድ ሰሞን
ኢትዮጵያዊነት ክብር ነው፣ለኃያል ክንድ የማይዳር
ሕዝባዊነት ነው መሥፈርቱ፣የሕዝብ ወገን፣የሕዝብ አጋር።
እንጂ ፣ለዘረኞች፣ቁማር፣ለአንድ ጎሣ ቡድን ገባር
ሊሆን እንደሚጣል ዕጣ፣አይደለም ሎቶሪ ቢጋር።
የየጎሣው ክልል ጣኦት፣እፍ እንዳለበት ጭቃ ጡብ
የሚፍጠረጠር ለቀን ሩብ።
ጠዋት ተፈብርኮ ፣ማታ”ተገምግሞ” እንደሚሞት
አይደለም ኢትዮጵያዊነት የአሻጉሊት ሕይወት።
በኢትዮጵያዊነት ፅናቱ ፣”የአገር ልጅ” ሁሉን ቢካንም
የትላንት መነሻውን ሳያጤን በታሪክ አቅም
የነገ መድረሻ ግብን”ድንገት”መቀየሥ አይችልም።
መነሻውን ያላወቀ ፣መድረሻውንም አያውቅም።
ሥለዚህ ማወቅ ሢጀምር
የሰው ልጅ ልሣኑን በቃል፣ቃሉን በፊደል ሢቀምር
ያገሩንና የራሱን፣ከወገኑ ስም ሲያጣምር
በማጠናቆር ጀመረ፣የሆሄን ልሣናት ድምር።
የኢትዮጵያዊነት ምሥጢሩ ፣
ወንድምህን መጠላት ሳይሆን፣ራሥህን ማወቅ ነው ከሥሩ።
ሰው በወንድሙ ሲሳለቅ ፤ያው በራሱ እንደመሳለቅ
ነውና ከቅድመ ታሪክ፣”አሥቀድመህ ራስክን እወቅ”
መባሉ በጥላቻ ዚቅ፣ታውረህ ወንድምክን ሥትንቅ
ያው ራስህን ነው፣የናቅከው፣ከራስህ ጋር ነው ትንቅንቅ
የዘረኝነት በሽታ፣መልሶ ራሥህክን ሥለሚያንቅ
መነሻውን ያላወቀ ፣መድረሻ ግቡንም አያውቅ።
…………………..
ይህ ግጥም፣የጀግናው ፣የተወዳጁ የኢትዮጵያውያን ሁሉ ኩራት፣የደራሲ፣የተውኔት ፀሐፊ፣የባለቅኔ የክቡር ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ቀዌሣ ግጥም ነው። ሙሉውን ግጥም በጦቢያ መፅሔት አምሥተኛ አመት ቁጥር 10/1990 ታገኙታላችሁ።

ከእንግዲህ፣ “ አራተኛ ዕድል !“ብሎ ነገር፣ የለም።

ማንን ብንገድል ነው ይህቺን ሀገር የምናተራምሰው?በማለት ባንዶች አስበውና አቅደው፣እየተቀሳቀሱ መሆኑን፣የሦሥተኛው ሰኔ የሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያ ያሥረዳናል።መረዳታችንም ነገም ሌላ አሥደንጋጭ ግድያ ለመፈፀም ሰኔን እንደማይጠብቁም፣ያረጋግጥልናል።ከእንግዲህ የኢትዮጵያ ጠላቶች “አራተኛ ዕድል” አይሰጡንም።የሃጫሉ ግድያ ቀጣይ የግድያ ዕቅዳቸው ፣በተዋቂ ሰዎችም ጭምር ላይ መሆኑንንም የጭካኔ ድርጊታቸው ይጠቁማል።ለኢትዮጵያ የሚጠቅሙ በማንኛውም የሥራ መሥክ የተሰማሩ ምጡቅ እምሮ ያላቸው ፣የሀገራችንን ብልፅግና፣የሀገራችንን ከፍታ አብሳሪ ፣እንቅልፍ አልባ ሠራተኞች፣የመንግሥት ጥበቃ እንደሚያሥፈልጋቸው፣የሃጫሉ ግድያ ብርቱ ያሥገነዝበናል።
ሃጫሉ፣ ምጡቅ አእምሮ ያለው የኢትዮጵያ ልጅ ነበር። ሃጫሉ በፀረ ጭቆና ዘፈኖቹ በመላው ኢትዮጵያ የሚታወቅ ከመሆኑም በላይ ፣የኦሮሞን ቋንቋና ባህል ለማሳደግ እና ኦሮሞ በኢትዮጵያዊነቱ ከሚገባው ከፍታ ላይ እንዲቀመጥ በተግባር ከጨቋኞች እና ከከፋፋዮች ጋር የታገለ፤የኦሮሞ አርሶ አደር እንደልፋቱ እንዲጠቀም፣ወጣቱ የበይ ተመልካች እንዳይሆን በብርቱ የቀሰቀሰ ነበር።
ይህ ብቻ አይደለም የጀግናው፣ የደፋሩ፣ሊቁ፣ ተወዳጁ፣ የዓለም ሎሬት የፀጋዬ ገ/መድህን ደም ያለበት፣እንደጀግናው እና የእውነት ጠበቃው የዓለም ሎሬት፣ እውነተኛ ኢትዮጵያዊ መሆኑን ከማንም በፊት ለነፃነት በዘፈናቸው፣የፀረ-ጭቆና ዘፈኖቹ ያረጋገጠ ደፋር ኢትዮጵያዊ፣ከጀግናው የአንቦ ህዝብ መሐፀን የተገኘ የወንዶች፣ወንድ ነበር። ለአጠቃላዩ የኦሮሞ ህዝብ፣ ባህል፣ቋንቋ፣ እንዲሁም የብልፅግና…ከፍታ በተግባር የታገለ ፣የኦሮሞ ህዝብ ነፃነት፣መብት፣ፍትህ እና ብልፅግና የመላው ኢትዮጵያ ህዝብም፣ብልፅግና ነው። ብሎ የሚያምን እና ጨቋኞችን አምርሮ የሚጠላ ነበር። ደግሞም አንደበተ ርእቱ እና፣ባሳል ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ነው።ደሙ ውሥጥ እኮ የሎሬታችን የፀጋዬ ገ/መድህን ቀዌሣ ደም እኮ ነው ያለው።
የሃጫሉ ሁንዴሳ አሟሟት ያንገበግባል።ፈሪዎች፣ባንዶች፣አቡነ ጴጥሮስንም ” ተንበርከክና ስገድልን፣ገብርልን፣አሥገብርልን “ቢሏቸው እንቢ ፣እንደውም “ኢትዮጵያዊያን ለእናንተ እንዳይገብሩ፣ገዝቻቸዋለሁ።” ስላሉ፣ ገድለዋቸዋል።ዛሬም በመቀላመድ ፣በማደናገር፣በመሸንገል፣በሃሰት ፕሮፖጋንዳ የተካኑ፣”እሥሥት” ባንዳዎች ሃጫሉ፣ለምን ለባንዳ ተልኮ ዘብ አልቆመም፣ለምን “የመላው ሀገር ህዝብ ነፃነት፣እኩልነት ና ዴሞክራሲያዊ መብት ሲረጋገጥ፣ አብሮ የኦሮሞ ህዝብም ጥያቄ ይመለሳል”በማለት የባንዶችን፣”የገጣይና አሥገንጣዮችን” ተልዕኮ በመኮነን ከኢትዮጵያዊያን ጎን መሠለፉን በተግባር ሥላረጋገጠ ጭለማን ተገን አድርገው ገድለውታል።(ይህን ያልኩት ከአሟሟቱ ቀደም ብሎ፣ቁንፅል ንግግሩን ከአጠቃላይ ቃለምልልሱ በማውጣት ፣አፄ ሚኒልክን ለማኮሰስ ተናግሯል ያሉት ነው።ግን አይደለም።ለመሆኑ በአህያ መንጋ ማነው አዲስ አባ የገባው? ሃጫሉ እዚ ድረስ ባለቅኔ ነው።)
እነዚህ ፀረ ኢትዮጵያ ሃይሎች የሐሰት ቪዲዮ አሥደግፈው ፣ ይህንን እኩይ ድርጊት በጭለማ ለምን ፈፀሙ? ለምንሥ ብርሃን ቅፅፈት አሟሟቱን በሚዲያ ነዙ? ደግሞስ እየተቀባበሉ፣በአፋን ኦሮሞ ሳይቀር ፣የትግራይን ህዝብ በጠመንጃ አፍነው የያዙት ዛሬም ነፃ ያልወጡት ነፃ አውጪዎች፣ለምን የሃሰት ፕሮፖጋንዳ ነዙ?…በሦሥት ሰኔዎች ያዘጋጁልን የሞት ድግሥ ፣በጥልቅ ምርመራ ማሥተናገድ ባለመቻላችን ይሆንን ዛሬ ለየት ያለ ማለትም ከቀጥተኛ ፖለቲከኛ ውጪ ፣በህዝብ ተወዳጅ ወደሆነ ድምፃዊ ላይ ያነጣጠሩት?… ነገ፣ ከነገወዲያሥ ምን እኩይ እቅድ አዘጋጅተውልን ይሆን?…ከሞቱሥ ብርሃን ፍጥነት ፣አማራውን ፣ከኦሮሞው ለማጋጨት ፣የኢትርሃምዌ ቅሥቀሣ በግልፅ ጀመሩ። ደጋግመው “ በደርግ ግብአተ መሬቱ የተቀበረውን የነፍጠኛ ሥርዓት” (ዛሬ የነፍጠኛ ሥርዓት ያለው በትግራይ፣በህውሃት ሥም በሚነግዱት በጥቂት ቱጃር የፓርቲው ወራሾች ነው።) ለዚህ ወራዳ ጥፋት ሰበብ እንደሆነ የፈጠራ ወሬ በማውራት፣ በፍቅር የሚኖሩትን ህዝቦች ፣በጋብቻ የተጋመዱትን አንድ ቤተሰቦች ትላንት በየዩኒቨርሲቲው ተማሪውን እንዳጋደሉ፣ዛሬም ህዝብን ከህዝብ ጋር በመጋጨት፣ሀገሪቱን ወደማያባራ ጦርነት ውሥጥ ለመክተት እና የግብፅን መንግሥት ጥቅም ለማሥጠበቅ በባንዳነት ዛሬም የጥፋት ግንባር ፈጥረው የሞት የሽረት ትግል እያደረጉ እንደሆነ ፣ከመቸውም ጊዜ ይልቅ ዛሬ ግልፅ ሆኗል።
እነዚህ ጥቂት ቮድካና ውስኪ ያናወዛቸው ቱጃሮች፣ረብጣ ብር ሥላላቸው አንዳችም የሚሳናቸው እንደሌለና ቅጥር ነፍሰ ገዳዮችን ለመቅጠርም እንደሚችሉም ያምናሉ። ዛሬም ከባንዳ ጋር ተባባሪ ያልባነነ ቄሮ አለ ብለው ያምናሉ።ሁሉም ሰው የማያሥብ እነሱ ብቻም የማሰብ ተሰጥኦ እንዳላቸው የሚያምኑ ግብዞች ሆነዋል።ሞትን ሞትው ካላዩ የማያምኑም ናቸው።
ዛሬም በአንድ ለአምሥት ጠርንፈን ይህንን የልባነነ ህዝብ እንገዛዋለን ።በማለት ያሥባሉ።ዛሬም ያንን የሽወዳ እና የብዝበዛ “አብዮታዊ ዴሞክራሲ”በህዝቡ ላይ በግድ በመጫን በጎሳ እና በብሄር እየነገድን እንኖራለን በለው ያልማሉ።
እነሱም ሆነ የግብፅ ተላላኪዎች፣ ታሪካዊ ጠላቶቻችን፣ አንድ ድንቅ፣ምጡቅና ለሀገር ተቆርቋሪ ዜጋ ቢሞት በእሱ እግር ሚሊዮኖች እንደሚተኩ ከታሪካችን አልተረዱምን? ኢትዮጵያ ባለፉት ዘመናት ከብዙ ጀግኖች ለክብሮ እና ለብልፅግናዋ ሲሉ ተሠውተውላታል።በቅርብም እነሥመኘው፣አነ ጀነራል ሣኣረ እና እነ አንባቸው መኮንን ህይወታቸውን ሰውተውላታል።ይህ መሥዋትነት ግን ተድበሥብሶ የሚቀር መሆን የለበትም።ጉርጥን ደፍሮ ጉርጥ ማለት ያሥፈልጋል።ሰዎቹ፣ገንዘብ፣የጦር መሣሪያና ቅጥር ነፍሰ ገዳዮች እንዳሏቸው ይታወቃል።(…)
ከኢንጅነር ሥመኝ ጀምሮ በተከታታይ አሥደንጋጭ ግድያ ሲፈፅሙ ዝም የተባሉት ፣ከፍተኛ የገንዘብ አቅም ያላቸው በመሆናቸው ይመሥለኛል።ዛሬም የመንግሥትን የፀረ ሌብነት ትግል ለማኮላሸት፣የአባይን የውሃ ሙሌት ለማደናቀፍ በማሰብ ማንን ብንገድል የኢትዮጵያን ህዝብ እናሥቆጣለን፣ሀገሪቱንም ትርምሥና ብጥብጥ ውሥጥ እንከታለን ብለው በማሰብ ረብጣ ዶላር መድበው፣ ይህንን እኩይ ድርጊት ፈፅመዋል። እናም እነዚህ ፀረ ፍትህ፣ፀረ-ዴሞክራሲ ፀረ- እኩልነት፣ፀረ-ሰብአዊ መብት፣ ፀረ-ነፃነት፣ፀረ-መልካም ነገሮች ሁሉ ሥለሆኑ እና የሌሎችን ብልፅግና ሥለማይወዱ ዜጎች ሁሉ አምርረን ልንዋጋቸው ይገባናል።
ሃጫሉ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ልጅ፣ ና ወንድም ሥለሆነ ሞቱ ሁላችንንም አሳዝኖናል።አሥለቅሶናል ።ሃጫሉ በባንዳ ቅጥረኞች በጭካኔ ለሀገር እና ለኦሮሞ ህዝብ ከፍታ የሰራው ህያው ሥራው ግን ዘላለማዊ ያደርገዋልና በትውልዱ ፈፅሞ አይረሳም።
የሃጫሉ ሁንዴሳ ደም “ ደመከልብ ሆኖ ይቀራል ።” ብዬ ከቶም አላሥብም።ይህ ድርጊት መንግሥት በጥልቀት ያልፈተሸው፣ምናልባትም ሚሊዮን ገንዘብ የፈሰሰበት ሦሥተኛው የባንዶች የሰኔ ወር የጭካኔ ተግባር ነው።(ኢጂነር ሥመኘው፣የሰኔ 16 ቱ የመሥቀል አደባባዩ የጠ/ሚ የመግደል ሙከራ፣የነጀነራል ሠአረ እና የአማራ ክልል አመራሮች ግድያ(የነአንባቸው መኮንን ግድያ)፣ዛሬ ደግሞ የታዋቂው ና የተወዳጁ ድምፃዊ በጥይት፣ በዘግናኝ ሁናቴ መገደል ና በግድያው አሳበው ወይም ድብቅ አጀንዳቸውን ለመከወን፣ቀድሞ በተጠና እቅድ የተንቀሳቀሱት ፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ፣ መንግሥትን ካላባነነው እና ጉርጥ አደፈጠም ዘለለ ያው ጉርጥ ነው ብሎ፣”ማንም ከህግ በላይ መሆን አይችልም”በማለት ፈጣን የህግ ማሥከበር እርምጃ ፣በህግ ላይ በፈነጩት፣በቀለዱትና ባላገጡት ላይ ካልወሰደ ፣የመንግሥት ህልውና ብቻ ሳይሆን የሀገሪቱም ህልውና አደጋላይ መውደቁ አይቀሬ ይሆናል።
(ይህ ፅሑፍ በኢንተርኔት መቆረጥ ምክንያት በወቅቱ ለህትመት አለበቃም።የተፃፈው፣ሰኔ 23/2012 ዓ/ም ጠዋት ነው።በከፍተኛ ሐዘን እና ቁጭት ላይ ሆኜ።በሃሳብ መታገልን።በሃሳብ ማሸነፍን።ሌሎች ሃሳብ ክብር መሥጠትን።ለእውነት ግንባርን መሥጠትን።ነፍሰ ገዳዮችን አምርሮ መጥላትና ለሰው ሁሉ ክብር መሥጠትን።ንቀትን፣ጥላቻን፣ደርሶ ቆዳ ማዋደድን ፣ወዘተ።የሃጫሉ ነፍሥ ይዛ ትጓዝ ሥለነበር ጀግናውን አርቲስት እጅግ እወደዋለሁ።)

ተጨማሪ ያንብቡ:  በላተኛው አባ-መላ ከያሬድ አይቼህ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share