የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የአማራ የቁርጥ ቀን ልጆች በሆኑ፣ በአስር ሺዎች አባላት ተመስርቶ በሚሊዮን የሚቆጠሩ አባላት እና ደጋፊዎችን ማፍራት የቻለ፣ በተመሰረተ በጣም በአጭር ጊዜ ውስጥም በመላው አማራና በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች መዋቅሩን በመዘርጋት እና የሕዝባዊ ስብሰባዎችን በማካሄድ አማራውን ያነቃና ያደራጀ፣ በዚህም በአማራ ሕዝብ ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነትን ያገኜ አብሪ ኮከብ ንቅናቄ ነበር። በርካታ የንቅናቄው መሪዎችም በማሕበረሰባቸው እና በመላው የአማራ ሕዝብ ዘንድ ከፍተኛ ፍቅርና አክብሮትን ያተጎናጸፉበትን ዕድልም የፈጠረ ድርጅት ነበር።
አብን የአማራ ሕዝብ መብቶች፣ ፍላጎቶች እና ጥቅሞች እንዲከበሩ የአማራ ሕዝብ ጥያቄዎችን በመቅረጽና በመተንተን፣ ምልዓተ ሕዝቡን በማስተማር፣ ሰፊ የማንቃት እና የማደራጀት ስራ በመስራት እንዲሁም ከፍተኛ የአድቮኬሲ እና የዲፕሎማሲ ስራ በመስራት በአማራ ሕዝብ ውስጥ ጠያቂ (demanding) ማሕበረሰብ እንዲፈጠር እና በአማራ ጠል ኃይሎች የተደረተውን የሀሰት ጸረ-አማራ ትርክት እንዲነትብ ያደረገ ንቅናቄ ነው። አማራው ከሌሎች ኢትዮጵያዊያን ወንድም እህቶቹ ጋር በጠረጴዛ ዙሪያ የሠለጠነ ድርድር በማድረግ፣ በሰጥቶ መቀበል መርህ ተመስርቶ በኢትዮጵያ ውስጥ አማራውን እኩል ተሳታፊ እና ተጠቃሚ የሚያደርግ አዲስ ማሕበራዊ ውል፣ ፍትሐዊ የመንግስት ስርዓትና ስሪት እንዲተከል የታገለ፣ የአማራ ሕዝብ ከሌሎች ወገኖቹ ጋር በመሆን አገር የመሠረተ፣ ነጻነቷን እና ዳር ድንበሯን አስከብሮ የኖረ ህዝብ መሆኑን ተረድቶ አንገቱን ቀና እንዲያደርግ ከፍተኛ የማንቃት እና የማስተማር እንዲሁም የመቀስቀስ ስራ ሰርቷል።
ምንም እንኳ በወቅቱ የነበሩ አመራሮች ከብልጽግና ፓርቲ ጋር በነበራቸው የስልጣን ዳረጎት መግባቢያ (understanding) መሠረት ምርጫ 2013 በተጠናና በተቀናጀ መንገድ የአብን እጩ ተወዳዳሪዎች ምርጫውን እንዳያሸንፉ እና ያሸነፉባቸውም አካባቢዎች በግልጽ ውጤታቸው መገልበጡን በመረጃ ተሰንዶ ቢቀርብላቸውም ከፍተኛ አመራሮች ለቦርዱም ሆነ ለፍርድ ቤት የረባ አቤቱታ እና ክስ ሳያቀርቡ ተድበስብሶ እንዲታለፍ እና በአምስት ወንበር ብቻ እንዲወሰን ሸፍጥ ቢፈጸምበትም ቅሉ 5 የፌደራል፣ እንዲሁም 13 የአማራ ክልል ምክር ቤት ወንበሮችን በመያዝ በፌደራል ፓርላማም ሆነ በአማራ ክልል ምክር ቤት ከገዢው ፓርቲ ቀጥሎ ብዙ መቀመጫዎችን ያሸነፈ «ዋነኛ ተቃዋሚ» ሆኖ መቀጠሉም የሚታወቅ ነው።
ምርጫ 2013ን ተከትሎ የስልጣን ዳረጎት የተሰጣቸው የንቅናቄው አመራሮች የፓርቲው ምልዓተ-ጉባኤ (ስራ አስፈጻሚው፣ ብሔራዊ ምክር ቤቱም ሆነ ጠቅላላ ጉባኤው) ሳይመክርበት እና ሳይወስን በጓሮ በር በኩል በየተራ እየሾለኩ ስልጣን ተቀብለው ድርጅቱን ለብልጽግና በእጅ መንሻነት ማስረከባቸውም የቅርብ ጊዜ ትውስታችን ነው።
የንቅናቄው ብሔራዊ ምክር ቤትም ጉዳዩን ከመረመረ በኋላ ንቅናቄያችን ሳይወስን ስልጣን ከተቀበላችሁ ያላችሁ አማራጭ የተቀበላችሁትን የመንግስት ኃላፊነት ይዛችሁ ቀጥሉ፤ የፓርቲው ኃላፊነት ግን ከፍተኛ ጊዜ፣ ጉልበት እና ትኩረት የሚጠይቅ ስለሆነ የንቅናቄውን ስራ ደርባችሁ ማከናወንም የፓርቲውን ስራ ስለሚጎዳ የንቅናቄውን ኃላፊነት በሙሉ ጊዜያቸው ለሚሰሩ አዳዲስ አመራሮች አስረክቡና በብሔራዊ ምክር ቤት አባልነት ቀጥሉ ወይም ደግሞ የመንግስት ስልጣን ለቃችሁ በፓርቲ ኃላፊነታችሁ ቀጥሉ የሚል አማራጭ በብሔራዊ ምክር ቤቱ ቢቀርብላቸውም አሻፈረኝ ብለው የፓርቲው ስራ እንዲዳከም፣ በሕዝባችን ዘንድ የነበረው ቅቡልነት እንዲወርድ እና ፓርቲው በምርጫ ቦርድ አዲሱ አዋጅ ቁጥር 1162/2011 ዓ.ም መሠረት የሚጠበቅበትን ጉባኤ እንዳያደርግ እግር ከወርች ተጠፍንጎ 5 ዓመታትን እንዲያሳልፍ አድርጎታል።
የካቲት 12 ቀን 2012 ዓ/ም ከተካሄደው ሁለተኛ ጠቅላላ ድርጅታዊ ጉባኤ በኋላ በ2014 ዓ/ም በባሕር ዳር ጉባኤ ለማካሄድ ተሞክሮ ነበር። በዚህም የድርጅቱ ብሔራዊ ምክር ቤትም፣ በቀጣይ ቀን የተሰበሰበው ጠቅላላ ጉባዔም ከፍተኛ አመራሩ ከመንግስት ስልጣን አንልቅም ስላላችሁ የፓርቲ ስልጣን ለአዳዲስ አመራሮች አስረክቡ ብሎ ወጥሮ ሲይዛቸው፣ ከፓርቲ ኃላፊነት ከተነሳን ከመንግስት ስልጣናችንም ያነሱናል በሚል ስጋት፤ እንዲሁም በሚዲያ ስማችን እየተብጠለጠለ ባለበት ጊዜ እንድንለቅ መገደድ የለብንም፣ የ 3 ወር ጊዜ ይሰጠን እና በ3 ወር ውስጥ እንደገና ጉባኤ አድርገን አዲስ አመራር እንተካ የሚል ተማጽኖ አቀረቡ። በሌላ በኩል ደግሞ አንዳንድ የጠቅላላ ጉባዔ አባላት ዛሬ ካልወረዳችሁ ሙተን እንገኛለን በማለት በፈጠሩት እሰጣ ገባ ምክንያት ጠቅላላ ጉባዔው በአግባቡ ሳይቋጭ እንዲበተን በማድረግ የአብን ድርጅታዊ ሕልውና ከድጡ ወደ ማጡ እንዲገባ ተደረገ። ሁለቱን ጫፎች ለማስታረቅ እና ሦስት ወር ታግሰን የአመራር መተካካቱ የሚሳካ ከሆነ እንሞክረው በሚል በግሌ እንባ እያነባሁ ጭምር ጉባዔ ላይ ለምኛለሁ። የግል ፍላጎቶቻችን እና የተወጠረው egoችን ከህዝባችን ፍላጎት እንጻር ኢምንት መሆኑን ለማስረዳት፣ ያደረግነው ውትወታና ልመና ሰሚ አላገኘም።
ምርጫ ቦርድም 2014 ላይ ሳይጠናቀቅ የቀረው የጠቅላላ ጉባኤ እንደገና እንዲካሄድ፣ ያልተጠናቀቀው የአመራር ሪፎርም አጀንዳም ውይይት ተካሂዶበት እንዲቋጭ ቀነ-ገደብ አስቀምጦ ትዕዛዝ ቢሰጥም አሁንም ከፍተኛ አመራሩ «አብን ለኛ ካልሆነ ለማንም እንዳይሆን እናደርጋለን»፣ «ባልበላውም ጭሬ ልበትነው» በሚል እልህ ጠቅላላ ጉባዔውን በድጋሚ ማካሄድ ሳይችል እንዲቀርና ድርጅታዊ ሕልውናውን እንዲያጣ፣ በርካታ አመራሮች እና አባላትም ተስፋ ቆርጠው እንዲቀመጡ፣ አለፍ ሲልም ሌሎች አማራጮችን እንዲያማትሩ አድርጓል።
ከዚያ እንደገና በታህሳስ 3 እና ታህሳስ 10 ቀን 2015 ዓ/ም የብልጽግና ተሿሚው አንጃ ጠቅላላ ጉባኤ ለማድረግ ዝግጅት መጨረሱን ገልጾ ታህሳስ 22 እና 23 ጉባኤ እንደሚያካሂድ ለምርጫ ቦርድ አሳወቀ።
ቦርዱም በቁጥር አ-1162/11/812 በታህሳስ 15 ቀን 2015 ዓ/ም ለንቅናቄው በፃፈው ምላሽ በፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 12 (1) መሠረት የብሔራዊ ምክር ቤቱ 45 ቋሚና 13 ተለዋጭ አባላት ያሉት መሆኑን፣ ከቋሚ አባላቱ ከግማሽ በላይ የሆኑት ከተገኙ ምልዓተ ጉባዔ እንደሚሟላ፣ ስብሰባዎቹም የሚያልፉት ከግማሽ በላይ የሚሆኑት የምክር ቤቱ አባላት ሲገኙ መሆኑን የፓርቲውን ህገ ደንብ አንቀጽ 22 (1-2) መደንገጉን ጠቅሶ፣ ይሁንና የፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት ነሐሴ 7 ቀን 2014 ዓ.ም ተደረገ በተባለው የፓርቲው ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ከተገኙት 22 ተሰብሳቢዎች ውስጥ 8ቱ ብቻ የብሔራዊ ምክር ቤት አባላት መሆናቸውን ቦርዱ መረዳቱን ገልጿል።
በመሆኑም ታህሳስ 22 እና 23 ቀን 2015 ዓ/ም ይደረጋል የተባለው ጠቅላላ ጉባዔ እንዲካሄድ የፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት ውሳኔ የሰጠው የምክር ቤቱ ምልዓተ ጉባኤ ሳይሟላ መሆኑን ከፓርቲው ከቀረቡለት ሰነዶች መረዳቱን ቦርዱ ገልጿል። ስለዚህ ከላይ በዝርዝር በተገለጹት የፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ ድንጋጌዎች መሠረት ብሔራዊ ምክር ቤቱ ነሐሴ 7 ቀን 2014 ዓ.ም በወሰነው ውሳኔ መሠረት ይሄንን ጠቅላላ ጉባዔ መጥራትና ማካሄድ የሚችልበት የህግ አግባብ የሌለ መሆኑን በአክብሮት ልንገልጽ እንወዳለን ብሎ በጻፈው ደብዳቤ ጉባዔውን ከልክሏል። ከዚያ በኋላም ባሉት ሦስት ዓመታት ውስጥ ጉባኤ መጥራት ባለመቻሉ የፓርቲው ህልውና እንዲያከትም እና በምርጫ ቦርድ ልዩ ችሮታ ካልሆነ በስተቀር በህግ እስከአሁን ባይሰረዝም በተግባር ግን የመሠረዝ እጣ እንዲገጥመው ተደርጓል።
በኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፓለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ እና የምርጫ ስነ-ምግባር አዋጅ ቁጥር 1162/2011 ዓ.ም በግልጽ እንደተደነገገው፣ አዋጁ የወጣበት አንደኛው ዓላማ ዜጎች በሚመሰርቱት ወይም በአባልነት በሚቀላቀሉት የፓለቲካ ፓርቲ ውስጥ የሚኖራቸውን መብትና ግዴታ፣ እንዲሁም ፓርቲው ህጋዊ ሰውነት የሚያገኝበትን ሁኔታ እና በድርጅትነት ሲንቀሳቀስ መከተልና ማክበር ያለበትን መሠረታዊ መርሆዎች መደንገግ አስፈላጊ መሆኑን ይገልጻል።
በአዋጁ ጠቅላላ ድንጋጌ አንቀጽ 2 ንዑስ-አንቀጽ 13 ውስጥም በግልጽ እንደተመላከተው የፓለቲካ ፓርቲ ወይም የፓለቲካ ድርጅት ማለት ዜጎች ተደራጅተው የሚመሰርቱት፣ የፓለቲካ ፕሮግራም በማውጣት በሀገር አቀፍ፣ በክልል ወይም ከክልል በታች ባለ ደረጃ በምርጫ የፓለቲካ ስልጣን ለመያዝ በዚህ አዋጅ መሠረት ተመዝግቦ የሚንቀሳቀስ ተቋም ነው ይላል።
በአዋጁ ምዕራፍ ሁለት ስለ ፓለቲካ ፓርቲ ምዝገባ በሚደነግገው አንቀጽ 66/1 ላይ ደግሞ ማንኛውም የፓለቲካ ፓርቲ በኢትዮጵያ ውስጥ በፓለቲካ ፓርቲነት ለመንቀሳቀስ የሚችለው በአዋጁ መሠረት በቦርዱ ተመዝግቦ የሕጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ሲያገኝ ብቻ እንደሆነ ተደንግጓል።
በአዲሱ የፓለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ እና የምርጫ ስነ-ምግባር አዋጅ ቁጥር 1162/2011 ዓ.ም መሠረት ነባር ሀገራዊ ፓርቲዎች የሚጠበቅባቸውን 10 ሺህ አባላት ፊርማ፣ የተሻሻለ የፓለቲካ ፓርቲ ፕሮግራም፣ የተሻሻለ የፓርቲ ህገ ደንብ እንዲያስገቡ እና ከ500 ሰው በላይ (የመስራች ፈራሚዎች 5%) የጉባኤ ተሳታፊዎች በተገኙበት እንደገና ጉባዔ አድርገው እንዲመዘገቡ እና ሕጋዊ ሰውነት አግኝተው እንዲንቀሳቀሱ በተጣለባቸው የግዴታ የድጋሚ ምዝገባ መሠረት አብን በምርጫ ቦርድ በተደጋጋሚ መስፈርቱን እንዲያሟላ ቢታዘዝም ሁለተኛውን ጉባኤ ካደረገበት ከየካቲት 12 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ 3ኛውን ጉባኤ አደረግሁበት እስካለበት እስከ ትናንት መጋቢት 28 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ ለ 5 ዓመታት ከአንድ ወር ጊዜ ምንም አይነት በቦርዱ ተቀባይነት ያለው ጉባኤ አላደረገም፣ በአዲሱ አዋጅ መሠረትም ሕጋዊ የምዝገባ የምስክር ወረቀት አልተሰጠውም።
በአዋጁ አንቀጽ 74—ሸ ላይ በግልጽ እንደተመላከተው ደግሞ አንድ የፓለቲካ ፓርቲ በህገ ደንቡ ላይ ቢያንስ በሦስት ዓመት አንዴ የፓርቲው ጠቅላላ ጉባዔ መካሄድ ያለበት መሆኑን የሚገልጽ ድንጋጌ ማካተት ያለባቸው ሲሆን፣ በዚህ ድንጋጌ መሠረትም አንድ ፓርቲ የምዝገባ የምስክር ወረቀቱ ሳይሰረዝበት ለመቀጠል በሦስት አመት አንድ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ የግድ ማድረግ አለበት።
በአዋጁ ምዕራፍ 7 ስለ ፓለቲካ ፓርቲ መሠረዝ ወይም መፍረስ በሚደነግገው በአንቀጽ 96 ስር ደግሞ የፓለቲካ ፓርቲ ከሚከተሉት ሁኔታዎች በአንዱ ምክንያት ከፓለቲካ ፓርቲነት ሊሰረዝ እንደሚችል ተመላክቷል፦ እነሱም
1ኛ) በፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ መሠረት በራሱ ፈቃድ ከምዝገባ እንዲሰረዝ ሲጠይቅ፣
2ኛ) በዚህ አዋጅ መሠረት የፓለቲካ ፓርቲው በዚህ አዋጅና በመተዳደሪያ ደንቡ መሠረት የአባላት ጠቅላላ ጉባኤ ማካሄድ ከሚገባው ጊዜ በሦስት ወር የዘገየ እንደሆነ እና ከዚያ በኋላ ቦርዱ በሚሰጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ጉባኤውን ሳያካሂድ የቀረ እንደሆነ ቦርዱ ወስኖ ያፈርሰዋል፣
3ኛ) የፓለቲካ ፓርቲው ከምዝገባ እንዲሰረዝ በዚህ አዋጅ መሠረት ፍርድ ቤት ውሳኔ ሲሰጥ ይፈርሳል ወይም ይሰረዛል።
ስለዚህ ከላይ ከቀረቡት የአዋጅ ቁጥር 1162/2011 ዓ.ም ድንጋጌዎች፤ እንዲሁም ከአብን መተዳደሪያ ደንብ ድንጋጌዎችም አንጻር ከታየ አብን ከየካቲት 12 ቀን 2015 ዓ.ም በኋላ የነበረው ተጨማሪ የሦስት ወር ጊዜ ብቻ ሲሆን፣ ከግንቦት 12 ቀን 2015 ዓ.ም በኋላ ግን እስከ አሁን ድረስ ቦርዱ በይፋ ባይሰርዘውም በተግባር ግን ጉባኤ ማካሄድ ባለመቻሉ እንዲፈርስ ይገደዳል ወይም ፈርሷል ማለት ነው።
የሦስት ዓመት ከሦስት ወሩም ጊዜ አልፎ አንድ አመት ከአስር ወር ተጨማሪ፣ በጠቅላላው አምስት አመት ከአንድ ወር በቦርዱ ተቀባይነት ያገኘ ጉባኤ ሳያካሂድ የቆየን ፓርቲ ቦርዱ ሳይሰርዘው የቀረው በአራት ምክንያቶች ሊሆን ይችላል ብሎ ግምት መውሰድ ይቻላል።
1) በገዢው ፓርቲ ብልጽግና ትዕዛዝ ለቀጣዩ ምርጫ የተወሰኑት አመራሮቹ በአጃቢነት እንዲሳተፍ ተፈልጎ ከሆነ፣
2) የአብን ተመራጮች በፓርላማ ውስጥ ከገዢው ፓርቲ ቀጥሎ አብላጫ መቀመጫ ያለው በምክር ቤቱ የአሰራር እና የአባላት ስነ-ምግባር ደንብ እንደሚጠራውም «ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲ» የሚባለውን ፓርቲ መሠረዙ ቦርዱ የህዝብ ግንኙነት ጉዳት እና ጫና ያመጣብኛል ብሎ አስቦ ሊሆን ከቻለ፣
3) አመራሩ በሂደት ልዩነቶችን አጥብቦ ችግሩን ፈቶ መቀጠል ከቻለ በሚል የዋህነትም ሊሆን ይችላል።
4) የቦርዱ ተቋማዊ የማስፈጸም አቅም ማነስ ወይም በትኩረት እና ክትትል ማነስ ምክንያት ሊሆን ይችላል።
ማጠቃለያ፦ አብን በምርጫ ቦርድ በህግ ባይሰረዝም እንኳ በተግባር ግን ጉባዔ እንዳያካሂድ ተደርጎ ሰቆቃዊ ሞት እንዲሞት የተደረገ ፓርቲ ነው። ተሿሚው አንጃ ትላንት አካሄድሁት ያለውን ጉባዔ ለመጥራት የሚያስችለው አካል (ብሔራዊ ምክር ቤቱ ወይም ማዕከላዊ ኮሚቴው) ውሳኔ ያላሳለፈበት፣ ጉባዔ አዘጋጅ ያልሰየመበት፣ ማዕከላዊ ኮሚቴው ውሳኔ እንዲያስተላልፍም በአግባቡ ስብሰባ ያልተጠራበት፣ አብዛኛዎቹ የትላንቱ ጉባዔ ተሳታፊዎችም በፓርቲው መዋቅሮች የማይታወቁ እና ያልተወከሉ አዳዲስ ፊቶች መሆናቸውን ከወጡ ፎቶዎች ተረድቻለሁ። የፓርቲው አባል መሆን አለመሆናቸውን ግን ከጥርጣሬ በጸዳ መንገድ ማረጋገጥ አልቻልሁም። የተደረገው ጉባኤም ሆነ የአመራር ምርጫ ግን እንዳልተደረገ የሚቆጠር፣ ፓርቲውም ህልውናው እንደሌለ የሚቆጠር የጥቂት አመራሮች የስልጣን እና የጥቅማ ጥቅም (በተደጋጋሚ እንደምለው ከምግብ ዋስትና ማረጋገጫነት – Safety Net package) የዘለለ ፋይዳ የሌለው ድርጅት እንዲሆን በተጠና መንገድ ተደርጓል።
ብዙ ዋጋ በከፈልንበት ፓርቲያችን ላይ እንደዚህ ያለ የመረረ ግምገማ ለማሳረፍ ያስገደደኝ ጉዳይ አብን መስራት የሚችለውን በወቅቱ በአጭር ጊዜ የሰራና በጥቂት የከፍተኛ አመራሩ ስህተቶች የፓለቲካ ገበያውን (Political currency) እንዲያጣ የተደረገ፣ ከዚህ በኋላ ከመኖሩ ይልቅ ባለመኖሩ የአማራን ሕዝብ የሚጠቅም ፓርቲ ነው ስለማምን ነው። የአማራ ሕዝብን ባይጠቅም እንኳ የማይጎዳ ቢሆን ኑሮ የተሾሙት አመራሮች እንጀራ በልተው ቢያድሩበት በግሌ ችግር የለብኝም።
የፓለቲካ ምህዳሩ ሲፈቅድ ለአማራ ሕዝብ ከዚያም ባለፈ መላው ኢትዮጵያዊያንን ታግሎ ማታገል የሚችል ድርጅት እንዴት መመስረት እንደሚቻል፣ ማንቃት፣ ማስተማር፣ grass roots organizing፣ politicking፣ statesmanship፣ አድቮኬሲና ዲፕሎማሲ የተማርንበት ስለሆነ አንድ ቀን vibrant የሆነ ድርጅት መመስረታችን አይቀርም። ዛሬ በርግጥ ፓለቲካው የጠብመንጃ አፈሙዝ በሆነበት አገር የፓርቲ ፓለቲካ ከአጭር ጊዜ አንጻር ፋይዳው ዝቅ ያለ ነው።
ዘለዓለማዊ ክብር እና ሞገስ በአብን ውስጥ በተለያየ ደረጃ ተሳትፋችሁ ውድ ዋጋ ለከፈላችሁ ጓዶቻችን !
ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ