September 29, 2024
27 mins read

ሰላም ከባዶ ምኞት፣ ተስፋስ እና ስብከት ፈፅሞ አይወለድም!

September 30, 2024

ጠገናውጎሹ
 
የሰላም ( peace) ምንነትና እንዴትነት የሰላም እጦት ከፍተኛ መገለጫ የሆነው የለየለት ግጭትና ጦርነት ካለመኖር ሁኔታና እሳቤ  አልፎ የሚሄድ  እጅግ ጥልቅና ዘርፈ ብዙ  የመሆኑ እውነትነት የሚያጠያይቀን አይመስለኝም።

ለመሆኑ ወቅታዊና  ትክክለኛ መፍትሄ ካልፈለግንላቸው በስተቀር ወደ ለየለት የጠመንጃ (የጦር መሳሪያ) ፍልማያ የሚያስገቡንን ግዙፍና መሪር ሁኔታዎች ወደ ድርጊት (ወደ ተግባር) በሚተረጎም ተስፈኝነት፣ ምኞት እና ስብከት/አስተምህሮት መሠረታዊና ዘላቂ መፍትሄ ለማግገኘት ባልቻልንበት ግዙፍና መሪር  ሁኔታ ውስጥ እየጓጎጥን  ሰላም እንደሰፈነ አድርገን ራሳችንን ለምን እንደምናታልል ከምር ጠይቀን እናውቃለን?  ከምር ቢያሳስበንና ብንጠይቅ  ኖሮማ ለዘመናት የመጣንበትንና ከስድስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ ፈፅሞ ታይቶና ተሰምቶ በማይታውቅ ሁኔታ የቀጠለውን ጨካኝ የጎሳ ደምና አጥንት ስሌት ፖለቲካ ነጋዴዎች  አገዛዝ (brutal merchants of the  ethno-centric politics) በቃን በሚል የአርበኝነት ተጋድሎ የሰላም ዋስትና የሆነውን የነፃነት፣የፍትህ ፣ የእኩልነት፣ የመከባበር፣ የመተባበር እና የጋራ እድገት  ሥርዓተ ዴሞክራሲን መሠረት ለመጣል በቻልን ነበር።

በእውነት ስለ እውነት ከተነጋገርን ከአያሌ ዓመታት በኋላም በእንዲህ አይነት ለመግለፅ የሚያስቸግር የመከራና የውርደት ማንነት ላይ የተገኘነውና የዓለም ምፅዋዕት ለማኞችና መሳለቂያዎች ሆነን የቀጠልነው በዚህ አስከፊ ውድቀታችን ምክንያት መሆኑን ለማመን ብንቸገርም መሬት ከሆነውና በመሆን ላይ ካለው ግዙፍና መሪር ጋር ከመጋጨት እና የመከራውንና የውርደቱን ዘመን ከማራዘም ያለፈ ፋይዳ የለውም።

ወደድንም ጠላን በክፉዎች የግፍና የዝርፊያ አገዛዝ ምክንያት ሰብአዊ መብት በሚደፈጠጥበት ፣ ፍፁም የሆነ ድህነት በተንሰራፋበት  ፣ የአካልና የአእምሮ ጤንነት በእጅጉ በተጎሳቆለበት ፣ እጅግ አብዛኛው ህዝብ (ወገን) የድንቁርና ሰለባ በሆነበት ፣ አብዛኛው ተማርኩና ተመራመርኩ የሚለውም በመፍትሄ ሃሳብና በተግባር ድርቅ ክፉኛ በተመታበት ፣ የአድርባይነትና የምን አገባኝ ባይነት ደዌ በተንሠራፋበት፣ የትክክለኛ ሽምግልና እና አሸማጋይነት እሴት በእጅጉ በኮሰመነበት፣ አብዛኛው ኢንቨስተርነት/ባለሃብትነት የግፍና የዝርፊያ ፖለቲካ ሥርዓት ቫይረስ ተሸካሚ በሆነበት፣ ሦስቱ የመንግሥት አካላት (ህግ አውጭ፣ ህግ ተርጓሚ እና ህግ አስፈፃሚ) የእኩያን ገዥ ቡድኖች የፖለቲካ ክለብ (ፓርቲ ተብየ) ተጠርናፊዎችና አገልጋዮች በሆኑበት፣ በእኩያን ገዥ ቡድኖች መርዘኛ የፖለቲካ ቁማር (የጎሳ ደምና አጥንት ስሌት ፖለቲካ) ምክንያት በኢትዮጵያዊነት የትም  በነፃነት ሠርቶ መኖር ተረት በሆነበት  የዘመናችን የሃይማኖታዊ እምነት መሪዎችና እረኞች ነን ባዮች (የሁሉም አይነት ሃይማኖት) ወገኖችን ከወንጀለኛው የፖለቲካ ሥርዓት ካድሬዎችና ከሌሎች የርካሽ ፖለቲካ አሻንጉሊቶች ለመለየት በተቸገርንበት ፣ ራሳቸውን በእውቀትና በጥበብ አስታጥቀው እና የራሳቸውን ህይወት ከአገራቸው ህልውና ጋር አቆራኝተው ለራሳቸው ብቻ ሳይሆን ለመጭው ትውልዶች የሚተላለፍ ታሪክ ይሠራሉ ተብለው የተጠበቁትና የሚጠበቁት ህፃናትና ወጣቶች  እጣ ፈንታ በእጅጉ በጨለመበት ፣  በተፈጥሮ ሃብትና በመልካ ምድር አቀማመጥ የታደለች አገርን ከእኩያን ገዥዎች ነፃ በማውጣትና የሚበጀውን ሥርዓት አምጦ በመውለድ የተሳካለት ህይወት መኖር ሲችል በየአቅጣጫው አገር ጥሎ መሰደድንና በተለይ በነዳጅ ሃብት ላበደ የአረብ ባለሃብት  ከተራ እቃ የማይሻል አገልጋይ መሆንን እንደ ስኬት የሚቆጥር የዚህ ትውልድ አባል ቁጥር በአስደንጋጭ ሁኔታ እያሻቀበ በቀጠለበት  ወዘተ ግዙፍና መሪር እውነታ ውስጥ ሰላምን  መፈለግ ቅዠት (dellusion) እንጅ የሚጨበጥ ምኞት ወይም ተስፋ ወይም ትንቢት ሊሆን አይችልም። 

አስቸጋሪና ውስብስብ በሆነው  የሰው ልጅ ግላዊ  ባህሪና ማህበራዊ መስተጋር ምክንያት በየትኛውም ጊዜ፣ ሁኔታ እና ቦታ ፍፁም የሆነ ሰላምን (absolute peace) መጠበቅ እንደማይቻል  ብዙ የሚያጠያይቀን/የሚያወዛግበን አይመስለኝም። ፍፁምነት (absolutism) የሃይማኖታዊ እምነት ወይም የመለኮታዊነት ባህሪ እንጅ የገሃዱ ዓለም ተፈጥሮና ባህሪ አይደለምና።

ይህ ግን እውነታ ለእንደ እኛ አይነት ዘመን ጠገቡንና  እንኳንስ ለማመን ለማሰብም የሚከብደውን  ፖለቲካ ወለድ የሰላም እጦት (ሰቆቃና ውርደት) አምራችና አከፋፋይ የሆነውን የባለጌዎችና የጨካኞች ሥርዓት በዴሞክራሲያዊ  የሥርዓት ለውጥ ተጋድሎ  ማስወገድ ለተሳነው ትውልድ ምክንያት (execuse) ፈፅሞ ሊሆን አይችልም። ለዘመናት የመጣንበትና አሁን ደግሞ እጅግ አሰቃቂ እየሆነ የቀጠለው የአገራችን ሁኔታ (የሰላም እጦት) እንኳንስ ስኬታማ ነው  ለሚባል አንፃራዊ ለሚባል ማወዳደሪያነትና  ማነፃፀሪያ ነትም (compare and contrast) የሚበቃ አይደለም።

የጥይት ድምፅ አልባ ትውልድ ገዳይነትን እና በጥይት ገዳይነትን እንደ ትክክለኛ (ስሜት እንደሚሰጥ) ማወዳደሪያነትና ማነፃፀሪያነት እየተጠቀምን “አንፃራዊ ሰላም ስለ ተፈጠረ  ሁሉ ም ተረጋግቷልና ደስ ይበለን”  የሚል እጅግ ግርድፍና አሳሳች መልእክት ማላዘን ወደ እውነተኛና ዘላቂ ፍኖተ ሰላም (የሰላም መንገድ) ሊመራን የሚችለው በምንና እንዴት እንደሆነ ለመረዳት ይከብዳል። “የጥይቱ ቶሎ ይገላል ፣ ጥይት አልባውና ወደ ጥይቱ ግድያ ሊያመራ የሚችለው  የቁም ሞት ግን ጊዜ ይሰጣል” የሚል እና ከሰብአዊ ፍጡር በታች የሚያውል መከራከሪያ ካላቀረብን በስተቀር 

 ስለ እውነተኛ  ሰላም መኖር ስንነጋገር  ሰው ከመሆን አስቸጋሪ ባህሪ ማለትም ከፍላጎትና  ከጥቅም ተገዥነት   ከሥልጣን ጥማትና ዘራፊነት   ከባለሥልጣን አምላኪነት  የግል ፍላጎትን የአገርና የወገን ብልፅግና እና ደስታ አድርጎ ከማሰብ ጨካኝነት  በንፁሃን ደም እየተጨማለቁ የአዞ እንባ ከማንባት ፣ በእኩያን ገዥዎች ቤተ መንግሥትና ቢሮ ዎች ዙሪያ እየተልከሰከሱ ከፈጣሪ የተላኩ የሃይማኖት አባት/እረኛ ነኝ ባይነት  አስከፊና አሳፋሪ ከሆነው አድርባይነትና ምን አገባኝ ባይነት ፣ ወዘተ  የሚመነጩ እጅግ ክፉ ደዌዎችን አስቀድሞ ለመከላከል እና ካልሆነም  ከቁጥጥር ውጭ ሆነው ትውልድን እንዳይበክሉ ለማድረግ ስለሚቻልበት ሁኔታ  ነው የምንነጋገረው።

ቀደም ሲል እንደጠቀስኩት ይህንን ሆኖና አድርጎ ለመገኘት ደግሞ ባዶ (ድርጊት አልባ) ተስፋን፣ ምኞትንና ስብከትን ተግባራዊ  ወደ ሆነ የለውጥ ሃይልነት (መሣሪያነት) መለወጥን ወይም መተርጎምን ይጠይቃል።

እኢአ 2016 “አሮጌ ሆኖ  አዲስ የሆነውን 2017ን” መቀበላችንን አስመልክቶ የእንኳን በሰላም አደረሰንና እና የመልካም ይሁንልን መልእክቶችን ተለዋውጠናል። በመለዋወጥም ላይ እንገኛለን።

በዚህ ሰሞን ደግሞ  በዓለ መስቀሉን አስመልክቶ ተመሳሳይ መልክትና ምኞት ተለዋውጠናል።  በመለዋወጥም ላይ እንገኛለን።

የዘመን መለወጫንም ሆነ ሌሎች በዓላትንና የመታሰቢያ ቀናትን  አክብረን ወይም አስበን ስንውል የእንኳን በሰላም አደረሰንና የመልካም ምኞት መልእክቶችን መለዋወጣችን ያለውን በጎ  ማህበራዊ፣ ባህላዊ፣ መንፈሳዊ ፣ ሞራላዊ እና  ሥነ ልቦናዊ ትርጉም (እሴት) ለመገንዘብ/ለመረዳት ከቅንና ከሚዛናዊ ህሊና የተለየ ምጡቅ እውቀትን (ሊቀ ሊቃውንትነትን) አይጠይቅም።

የርዕሰ ጉዳዬ መነሻና ማጠንጠኛም ዘመን ጠገብና በጎ የሆነውን የእንኳን በሰላም አደረሰንና የመልካም ምኞት መለዋወጥ  ችግር  ወይም ፈታኝ ሁኔታ  ወይንም ከዚህ አልፎ እንደ ሄደው የእኛ አይነት ፖለቲካ ወለድ ግዙፍና መሪር  ሁኔታ እያጋጠመን ስለሆነ  ፈፅሞ አያስፈልግንም የሚል ደምሳሳ  አመለካከት (እሳቤ) አይደለም።

የሂሳዊ አስተያየቴ መነሻና ማጠንጠኛ በጎ እና ዘመን ጠገብ የሆነውን የእንኳን በሰላም አደረሰንና የመልካም ይሁንልን ምኞት መልእክት ለዘመናት ተዘፍቀን ከመጣንበትና ከስድስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ ለማመን በሚከብድ አኳኋን ተዘፍቀን ከቀጠልንበት ግዙፍና መሪር የውድቀት እኛነታችን ጋር እያስተያየን ወይም እያመሳከርን  ወቅታዊና ውጤታማ ከሚሆን  የጋራ ጥረት (ትግል) ጋር ካላስተናገድነው ከፖለቲካ ወለድ የመከራና  የውርደት ክፉ አዙሪት ሰብረን ለመውጣት ፈፅሞ አይቻለንምና ከምር ሊያሳስበን ይገባል የሚል ነው።

ጥቂት ባለጌና ጨካኝ የጎሳ አጥንትና ደም ስሌት ፖለቲካ ነጋዴዎች እና ቁጥሩ ቀላል ያልሆነ ለከርሱ (ለሆዱ) አዳሪ የካድሬ ሠራዊታቸው በመሠረቱትና  በሚቆጣጠሩት ሥርዓተ መከራና ውርደት ሥር እየተርመጠመጥን  የዘመን ግሥጋሴን ፣ የልዩ ልዩ በዓላትን እና መታሰቢያ ቀናትን ቀመር እያሰላን የእንኳን በሰላም አደረሰንና የመልካም ይሁንልን መልእክትና መግለጫ መለዋወጣችን የሰላምንና የመልካም ነገርን ሰፊና ጥልቅ ትርጉም እያበላሸብን ነውና ከክስተቶች ጊዜያዊ ሙቀት ጋር በስሜት መጋለቡን ተቆጣጥረን ከምር ልናስብበትና ትክክለኛውን መስመር ልናስይዘው ይገባል።

እንኳን በሰላም አደረሰን እና የሰላምና የብልፅግና ዘመን ይሁንልን በሚል ስሜቶቻችንን የምንገልፅባቸው  እጅግ ሰፊና ጥልቅ ቃላት (ፅንሰ ሃሳቦች) ለዘመናት የመጣንበትንና አሁንም እጅግ ለማመን በሚያስቸግር ሁኔታ ተዘፍቀን የምንገኝበትን ፖለቲካ ወለድ የመከራና የውርደት እኛነታችንን በእውን የመግለፅ አቅማቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ በእጅጉ እየኮሰመነ የመሄዱ አስቀያሚ እንቆቅልሽ ከምር ሊፈተሽ ይገበዋል ። ይህንን አይነት ሂሳዊ ትችት ከምር ተረድቶና በአግባቡ ተቀብሎ ማስተናገድና ትክክለኛውን እርምት ማድረግ የምንመኘውንና የምንሰብክለትን ሰላም የዘልማድ ቃል (ፅንሰ ሃሳብ) ሆኖ እንዳይቀጥልና እና እኛም የሸፍጠኛና ሴረኛ ገዥ ቡድኖች ሰለባዎችና መሳለቂያዎች ሆነን እንዳንቀጥል ይረዳናል።

በእውነት ስለ እውነት ተናግረንና ተነጋግረን አስከፊውንና አሳፋሪውን  ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚዊ፣ ማህበራዊ፣ ሞራልዊ፣ ባህልዊ፣ ሥነ ልቦናዊ እና መንፈሳዊ ውድቀታችንን በፅዕናትና በጥበብ ከመጋፈጥ ይልቅ የሰበብ ድሪቶ እየደረትን ዙሪያውን መዞር ክፉ ልማድ  ሆኖብን እንጅ የእንኳን በሰላም አደረሰንና የመልካም ምኞት መልእክቶቻችን እና መሬት ላይ የኖርነውና የምንኖረው (መኖር ከተባለ) ዘመን ጠገብና እጅግ መሪር እውነታ ተለያይተው ከወደቁ አያሌ ዓመታት (ዘመን መለወጫዎች) ተቆጥረዋል።

በተለይ ደግሞ ከስድስት ዓመታት  ወዲህ የሥልጣነ መንበሩን የበላይነት ከፈጣሪያቸውና ከጠርናፊያቸው ህወሃት ነጥቀው አገርን ምድረ ሲኦል በማድረግ ላይ ካሉት ባለጌና ጨካኝ የጎሳ ደምና አጥንት ስሌት ፖለቲካ ቁማርተኛ ገዥዎች አንፃር ሲታይ የሚያሳድረው የህሊና ህመም በእጅጉ ከባድ ነው።

እናም ይህ የጀመርነው 2017 ግዙፍና መሪር የሆነውንና የትኛውም አይነት ምክንያት ፈፅሞ ሊገዳደረው የማይችለውን  የመኖር ወይም ያለመኖር/የመሆን ወይም ያለመሆን ጥያቄን በማያወላውል አኳኋን እልባት ለመስጠት በሚያስችሉ ታሪካዊ ድሎች ታጅቦ መጭው 2018  ከዘልማድ የእንኳን  በሰላም አደረሰንና የመልካም ይሁንልን መልእክትና ምኞት ለምድሩም ሆነ ተስፋ ለምናደርገው ከሞት በኋላ ህይወት የምትመች  ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን እውን ለማድረግና ለማስደረግ የሚችሉ ሥራዎች የሚከናወኑበትና መሠረት የሚጣልበት መሆን ይኖርበታል ።

በሥልጣነ መንበር ላይ በሚፈራረቁ እኩያን ገዥዎች ምክንያት በዘመን ርዝማኔም ሆነ በአስከፊነቱ ለማመን  በሚያስቸግር የመከራና የውርደት ቀንበር ተሸካሚነት ሥር እየማቀቅን  የዘመን መለወጫና ሌሎች በዓላት ጊዜያቸውን ጠብቀው በመጡ ቁጥር ፈጣሪን ጨምረን ባዶ ተስፋችንንና ምኞታችንን ወደ የህይወት ፍሬነት እንዲለውጥልን  ተስፋ ማድረግና መመኘት ትርጉም አልባ እንደሆነ ከእኛው ከራሳችን ዘመን ጠገብና እጅግ መሪር ተሞክሮ የበለጠ አስረጅ ፈፅሞ ሊኖር አይችልም።

ለዘማናት በሥልጣነ መንበር ላይ እየተፈራረቁ የመቃብር እና የቁም ሙቶች ያደረጉንና እያደረጉን ያሉትን እኩያን ገዥዎችን እብደት ለመጋፈጥና ለማስቆም የሚያስችል የፖለቲካና የሞራል ልእልና በማጣታችን ምክንያት አሮጌ የምንለውን ዓመት እንዳልኖርነው አውቀንና ከዚህ ክፉ አዙሪት እስካለወጣን ድረስ መጭውንም (“አዲሱንም”) እንደማንኖረው ከምር ተገንዝበንና ተዘጋጅተን  ከአሁን በኋላ የምናከብራቸውንና የምናስባቸውን ሃይማኖታዊና ሌሎች በዓላት  እውነተኛ የእንኳን አደረሰንና የመልካም ይሁንልን አውዶች ማድረግ ይኖርብናል።

ይህንን ሆኖና አድርጎ ለመገኘት ደግሞ ይህ ወርቃማ ዓላማና ግብ እውን ይሆን ዘንድ  ለዘመናት የመከራና የውርደት ዶፍ ያወረዱብንንና አሁንም ከምንጊዜውም በከፋ ሁኔታ እያወረዱብን የቀጠሉትን እኩያን የጎሳ ደም  ስሌት ፖለቲካ ቁማርተኞች  በዴሞክራሲ አርበኝነት ተጋድሎ ሲሆን ተገደው የሽግግር ፍትህ ሥርዓትን መሠረት በሚያደርግ ጠረጴዛ ዙሪያ እንዲቀርቡ በማድረግ እና ይህ ካልሆነ ግን መነሻ ምክንያቱ እጅግ ግዙፍና ትክክለኛ የሆነውን የፋኖን እና የተባባሪ ወገኖችን እልህ አስጨራሽ ትግል አጠናክሮ በመቀጠል የመከራና የውርደት ማምረቻና ማከፋፈያ ከሆነው ሥልጣነ መንበራቸው አውርዶ ወደ ፍትህ አደባባይ በማቅረብ ለሁሉም ዜጎቿ የምትመች ኢትዮጵያን እውን የማድረጉ ታሪካዊ ተልእኮና ሃላፊነት ተፈፃሚ መሆን ይኖርበታል።

ጦርነት ሰላምን የማያመጣው ሀ) መነሻ ምክንያቱ (root cause) ፍትህና ነፃነት ሳይሆን የሥልጣን ጥማት ከሆነ ለ) የትግሉ መሪዎችና ደጋፊዎች ይህንኑ መሠረታዊና ፍትሃዊ  መነሻ ምክንያት ተጠቅመው የትግሉን ትክክለኛ ዓላማና ግብ ወደ ተሳሳተ አቅጣጫና ሁኔታ የሚወስዱት  ከሆነ ሐ) በሥልጣን ላይ ያለው ገዥ ቡድን ለዘመናት ለፈፀመውና ላስፈፀመው ፖለቲካ ወለድ ወንጀል ሃላፊነቱን ወስዶ ወደ የድርድር ጠረጴዛ ከመምጣትና ገንቢ ሚና ከመጫወት ይልቅ የነፃነት ተጋዮችን መሣሪያችሁን  አስቀምጣችሁ በእኔ አጀንዳዎችና ቅድመ ሁኔታዎች (terms and conditions) ሥር የሚል ከሆነ  መ) ከየራሳቸው ብሔራዊ ጥቅም አንፃር ጣልቃ የሚገቡ የውጭ መንግሥታትና ሌሎች አካላት ብዙውን ጊዜ ሊያሸንፍ ይችላል ብለው የሚያስቡትን ሃይል ወደ መደገፍ ስለሚያደሉ (ብዙውን ጊዜ ሥልጣን ላይ ያለውን) ይህንን የፖለቲካ ጨዋታ በጥንቃቄና በጥበብ መጫወት ካልተቻለ ነው።እነዚህን ለማሳያነት ጠቀስኩ እንጅ እነዚህ ብቻ ናቸው ማለት አይደለም።

በየሚዲያውና በየአጋጣሚው የፋኖና የሌሎች የትግሉ ተጋሪ ወገኖች ትግል ሰላምን እንደማያመጣ ተደርጎ የሚነገረው እጅግ አጠቃላይና ደምሳሳ አባባል በቅጡ መፈተሽ ያለበትም ለዚህ ነው። የመከራና የውርደት ሥርዓትን በትጥቅ ትግል ማሸነፍ ሲባል አስገድዶ ወደ የድርድር ጠረጴዛ ማምጣትንም የሚጨምር እንጅ የግድ በጦርነት ካልሆነ የማለት ጉዳይ አይደለም።

ይህ ካልሆነ ግን እየጠረነፍኩ፣ እያሰርኩና እየገረፍኩ፣ እየፈነቀልኩና እያያፈናቀልኩ ፣ እየገደልኩና እያስገደልኩ ፣ በሃሰት ክስ ንፁሃንን የግፍ ሰለባ እያደረኩ ፣ ጀኖሳይድ እየፈፀምኩ፣ እና በአጠቃላይ አገርን ምድረ ሲኦል እያደረኩ እቀጥላለሁ የሚልን ፈሪና ጨካኝ አገዛዝ ከላይ ለማሳያነት የጠከስኳቸውን ሁኔታዎች ግምት ውስጥ ባስገባ ሁኔታ በጦርነት አሽመድምዶ አስተማማኝና ዘላቂ ሰላምን እውን ማድረግ የማይቻልበት አሳማኝ ምክንያት የለም።

ያኔም ነው ከዘልማድ የእንኳን አደረሰንና የመልካም ይሁንልን ምኞት፣ ተስፋና ስብከት ወጥተን (ተላቀን) ለምድራዊውም ሆነ ለሰማያዊው ህይወት የምትመች ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን እውን ማድረግ የምንችለው።

እናም ልብ ያለው ልብ ይበል!!!

 

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

193785
Previous Story

ለመላው አምሃራ ወቅታዊ ጥሪ – ከፋኖ አደረጃጀት

193794
Next Story

በአማራ የክልሉ አመራች ታሰሩ | በጎንደር ለመጀመሪያ ጊዜ በሂሊኮፍተር የታገዘ ው*ጊያ ተከፍቶብናል

Latest from Blog

blank

“መነሻችን እዚህ መዳረሻችን እዚያ” የሚለው የዲያስፖራ ከንቱ አታካራ! – ክፍል ሁለት

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com) በአንዳንድ ስብሰባዎችና የሕዝብ መገናኛ መድረኮች የሚታየው የአንዳንድ ዲያስፖራዎች  “መነሻችን እዚህ መዳረሻችን እዚያ” የበከተ ከንቱ አታካራ በልጅነታችን ወላጆቻችን ትምህርት እንዲሆነን ይተርኩልን የነበረውን ከጫጉላ ወጥተው ጎጆ ለመመስረት የታከቱ ሁለት ያልበሰሉ ባልና ሚስትን ታሪክ
blank

መነሻችን አማራ መድረሻችን አማራ እና ወያኔያዊ መሠረቱ

የማይወጣ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል። የዛሬን አያድርገውና የትግሬ ልሂቆች “ትግራይ የጦቢያ መሠረት ናት ።  ጦቢያ ያለ ትግራይ፣ ትግራይ ያለ ጦቢያ ሊታሰቡ አይችሉም” በማለት ጦቢያዊ ከኛ ወዲያ ላሳር እያሉ አለቅጥ ይመጻደቁ፣ ይኩራሩ፣ ይታበዩ ነበር። ወያኔ
blank

ከ”ችርቻሮ” ድል አልፎ ለመሄድ የአንድነት አስፈላጊነት – ግርማ ካሳ

በአሁኑ ጊዜ ሁለት የፋኖ አሰላለፎች አሉ:: መኖር ያልነበረበት:: አንከር ሜዲያ ከሁለቱም አሰላለፎች፣ ሁለት ፋኖ መሪዎች ጋር ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡ ሁለቱን አደመጥኩ፡፡ በሰማሁት ነገር ተደስቻለሁ:: ትልቅ ተስፋ እንድሰንቅም አድርጎኛል:: የአማራ ህዝባዊ ድርጅት የፖለቲካ
Go toTop