June 22, 2019
6 mins read

ኢዜማ የሚወዳደረው አሜሪካና ካናዳ ነው እንዴ? – ሰርፀ ደስታ

ይሄን ጥያቄ የማነሳው መሠረታዊ ነገሮችን እንዳናስብ በቲፎዞ እያደነዘዙ  አገርንና ሕዝብን ቀጥሎ ለመዝረፍ እየተፎካከሩ በሚመስል ሁኔታ የፖለቲካ ቡድን ነን የሚሉት ነገር በየትኛውም መለኪያ እድል ቢያገኙ አደገኛ እንደሆኑ ለሕዝብ መጠቆም ግዴታ ስለሆነብኝ ነው፡፡  ኢዜማ አንዱ ማሳያ አደረግኩት እንጂ ኢትዮጵያ ላይ እየተሰራ ያለው የፖለቲካ ቁማር በዋናነት ኢሕአዴግ የተባለ የዘረፋ ቡድን ነው የሚከውነው፡፡ አሳዛኙ ነገር ግን ተፎካካሪ ነን ከሚሉት አንዳቸው እንኳን  የአገርና ሕዝብ ጉዳይ ሊሰማቸው የሚችል ሆነው አይታዩም፡፡ እንግዲህ አገራችንን በቅብብል ወንበዴዎች ላይለቀቋት ሁሉም እንደ አንድ ቡድን ይሰራሉ፡፡ አሁንማ እርስ በእርስ እየተሞከሻሹ የሚቀጥለውን የዘረፋ ምእራፍ በጋራ ሊያደርጉት የተዘጋጁ ነው የሚመስለው፡፡

የሰሞኑን የኢዜማ ለዲያስፖራ እቅዱን ለማስተዋወቅ ጉዞ እንደሚያደርግ በየ ፌስቡኩ ተሰራጭቶ ያለውን ማስታወቂያ ሳይ ብዙ ነገር ወደ አእምሮዬ መጣ፡፡ አገርን በቡድን ተደራጅቶ ለመዝረፍ እንጂ ለአገርና ሕዝብ በቁጭት የሚሰራ አንድም እንኳን አለመኖሩ እጅግ ያሳዝናል፡፡ እንግዲህ ይሄ የኢዜማን እንቅስቃሴ እንደማሳያ ልጠቁማችሁ፡፡ መራጩ ሕዝብ ያው ኢትዮጵያ ውስጥ ነው፡፡ ራሱን ማስተዋወቅ ከአለበት እቅዱን እዛው ለሚመርጠው ሕዝብ ማስተዋወቅ ግድ ይላል፡፡ የሽርሽር ፖለቲካን ሁሉም የተካነበት ይመስላል፡፡ አሜሪካም ሆነ ካናዳ አብዛኛው የአበሻ ዘር የሆነ በዜግነት እንኳን ኢትዮጵያዊ አደለም፡፡ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ግን ዜጋ ሳይሆኑ በቀጥታ የፖለቲካ ቡድን ውስጥ በዋናነት የሚሳተፉ ቢያንስ አንዳርጋቸው ጽጌና ኤርሚያስ ማዴቦን እንደማሳያ መውሰድ ይቻላል፡፡ እንግዲህ የዜግነት ክብርን እንኳን ጠንቅቆ የማያውቀው ዛሬ ራሱን ኢዜማ በማለት የዜጎች ፖለቲካ ብቸኛ አራማጅ ነኝ የሚለው ቡድን አሁን ደግሞ በአብዛኛው ዜጋም ባልሆኑ ቢሆኑ አንኳ በመራጭነት ለመሳተፍ ትንሽ እድል ላላቸው በዋናነት ፕሮገራሜን አስተዋውቃለሁ እያለን ነው፡፡

ኢትዮጵያውያንን ማን ከቁም ነገር ይቆጥራል? ምጽዋትና ቲፎዞ የሚሆኑትን ማሳመን እንጂ፡፡ ዜጋ ላልሆነው ዲያስፖራ ራሴን አስተዋውቃለሁ የሚለው በዜግነት የሚቀልደው 100 ሚሊየን ዜጎች አብዛኛው ከነመኖሩም አያውቅም፡ ዜጎች ሲፈናቀሉ፣ ሕዝብ ግልጽ የሆነ የውንብድና ሴራ ሲሰራበት ዝም ማለታቸው ሳያንስ የዜጎች ራሳቸውን ከወሮበሎች እንዲከላከሉ የሚቀሰቅሱትንም ሲያወግዙ የነበሩ ናቸው እንግዲህ ዛሬ ስለዜጋ ከእኛ ውጭ የለም የሚሉን፡፡ አንዱ እስክንድር ለዜጋ እያደረገ ያለውን ማየት በቂ ነው ዜግነት ማለት ከገባን፡፡ ዛሬ በእስክንድር ላይ ሁሉም በትብብር የሚዘምቱበት ግልጽ የሆነ የፍትህና የዲሞክራሲ መርህ ላይ ቆሞ የእነሱን ነገር እያበላሸባቸው ስለሆነ ነው፡፡ እንጂማ በምን መስፈርት ቤት እያፈረሰ ዜጎችን ሜዳ ላይ የሚጥል ወንበዴ ቡድን ሳይወገዝ፣ በጠራራ ጸሐይ ዜጎች ስንት አመት ለፍተው ያገኙትን ቤት በጉልበት አይሰጥም ያለን ትንፍሽ ሳይሉ እነዚህ ወሮበሎች ለመከላከል ራስህን አደራጅ ብሎ ሕዝብን እየቀሰቀሰ ያለውን ያወግዛሉ፡፡ በየትኛው አመክንዮ ነው ይሄ ትክክል የሚሆነው?

የዜግነት ክብር ይከበር! ሥርዓት ይከበር! መንግስታዊ አደረጃጀት እንዲመጣ እንጂ ከአንዱ ቁማርተኛ ወደሌላው ለመሸጋገር አደለም፡፡ ሕዝብን የንግድ እቃ ማድረግ ይቁም! ኢትዮጵያ ቁርጠኛ ልጆች ትሻለች፡፡ ገንዘብና በቲፎዞነት የሚደግፉትን በማሳመን በሕዝብ ላይ ዳግም ሸክም ለመሆን ለሚጥር ቡድን እደል ሊሰጠው አይገባም እላለሁ፡፡ ሁሉም ራሱን ይመርምር፡፡ ጊዜ የለም! ተሳስቼ ከሆነ እታረማለሁ፡፡ ገብቶናል የምትሉ ልሰማችሁ ዝግጁ ነኝ፡፡ በደንብ ማሰብን ይጠይቃል! በሆያሆዬ ሕዝቡን እያደነዘዙ አገር እየወደመች ነው!

ቅዱስ እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይባርክ! አሜን!

6 Comments

  1. ትግሉ ኢትዮጵያ ውስጥ ነው ወይስ አሜሪካ ካናዳ? መራጩን ህዝብ ስለ ኢዜማ የትግል አቅጣጫ ሳያስተዋውቁና ሳያስተምሩ እሮጦ ወደ ውጪ መውጣት የሚያስመስግን ሳይሆን የሚያሳፍር ነው:: ከውጪ ካለነው ገንዝብ ነው የሚገኘው ያንንም እዛው ሆኖ መጠየቅና ማግኘት ይቻላል:: ከገንዝብ በላይ ግን ህዝብ ነው ባይ ነኝ:: ህዝብን ንቆ ገንዘብ ለማግኘት በየ አገሩ መዞር ትግል አይደለም እንደውም ነውር ነው ኢዜማ ከእስክንድር ቡዙ መማር አለበት እንደሚታወቀው እስክንድር በከተማ ህዝብ ያሰባስባል ያስተባብራል ኢዜማ ህዝብን ትቶ በየአገሩ በመሄድ ገንዘብ ይሰበስባል ለኢዜማ መሪዎች ያለኝ ጥይቄ ህዝብ ወይስ ገንዘብ ይበልጣል?

  2. የእስክብድርን ትግል የሚያደንቅ ለሚያቋቁመው ሳታላይት ቴሌቭዥን ሼር ይግዛ::

  3. የተሰራን መተቸት ቀላል ነው፡፡ መስራት ግን እጅግ አስቸጋሪ ነው፡፡ አንተ ብትሆን የታዩህን ጉድለቶች አርመህ በየወረዳና በየቀበሌ ወርደህም ይሁን የተሻለ በምትለው አደራጃጀት አንድ የተሻለ ድርጅት አምጣልን፡፡ ልቃወምህ ብዬ ሳይሆን፣ እኔ ብሆን ብዬ ሳስብ እጅግ ከባድ ስለሚሆንብኝ የሚሰሩትን አደንቃለሁ፡፡ አንዳርጋቸው ጽጌ የመን ላይ የታፈነው፣ ሶስት መቶ ዶላር ለመቆጠብ ብሎ እንደ ነበር ገልጾልናል፡፡ አንዳርጋቸው የግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይልን መስርቶ መጀመሪያ እንደ አሜሪካ እንደመጣ በተደረገ ስብሰባ ላይ ገንዘብ የማሰባሰብ ስራ እዚያው ስብሰባ ላይ ሲጀመር፣የሰጠው መልስ እኛ ገንዘብ አንፈልግም፡፡ የኤርትራ መንግስት ከአለው አቅም አንጻር እየሰጠን የሚገኘው ድጋፍ፣ በዘመናዊ ሆቴል ውስጥ አንደላቆ እንደ ማኖር የሚቆጠር መሆኑን ገልጾ ነበር፡፡ አሁንም እነኝህ የኢዜማ አመራሮች በድርጅት ገንዘብ ነው የመጡት ወይስ በእራሳቸው ወጪ ነው? ይህንን ቀድሞ ማጣራቱ ተገቢ ይመስለኛል፡፡ ህዝብ ስትጠራው ከመጣ ስለወደደ እንጂ ተገዶ አይደለምና የግል ጥላቻን ለአገር አሳቢ በመምሰል ብዙ መስዋእትነት የከፈሉ ሰዎችን ከመዝለፍ፣ ምክረ ሃሳብ መስጠት የሚሻል ይመስለኛል፡፡ ካልሆነም እንዳልኩ ከቻልክ የተሻለ ሰርተህ እነሱን ማስናቅ ነው፡፡

    • ምንድነው አዲስነቱ በተለይ ወደ ካናዳ መምጣቱ ከገንዘብ ለመሰብሰብ ብቻ ነው፡፡በማስረጃ የማውቀው በመሆኑ፡፡ከእዚህ በፊት በግንቦት 7 ስም ሲሰበሰብ ምን ያህል እንደተሰበሰበ ወዴት እንደተላከ ማን እንደተጠቀመ የትኛው ኪስ ምን ያህል እንደቀረ የሚታወቅ ነገር የለም፡፡ከዚያም በላይ ተደራጅቶ ካናዳ በየትላልቅ ከተማዎች ባሉ የኢትዮጵያ ማኅበረሰብ በመግባት ገንዘብ መዝረፍ አዲስ ነገር አይደለም፡፡በግንቦት 7 ስም ማኅበረሰቦች ተዘርፈዋል፡፡ተከፋፍለዋል፡፡በኢትዮጵያውያን ኅብረት ላይ መተማመን እንዳይኖር በአያሌው ተሰርቷል፡፡በተለይም በካሊገሪው ካናዳ የተሰራው ወንጀል የጠቅላይ ግዛቱ መንግስት የሚያውቀው ብቻ ሳይሆን፡ በሂሳብ ምርመራ ያረጋገጥው ነው፡፡እንዲህ ያለው ድርጊት አዲስ የሚሆነው የዋህ ለሆነ በስመ ኢትይጵያዊነት ኪሱ ለሚራቆተው ብቻ ነው፡፡አገርን መርዳት ሕዝባችንን መደገፍ አገራዊ ግዳያችንም ቢሆን፡በአትዮጵያዊነት ስም መታለሉ ተገቢ አይደለም፡፡ ዛሬ ዛሬ በአንዳድ የካናዳ ከተማዎች በኢትዮጵያ ፖለቲካ ስም ገንዘብ መሰብሰብ ቀላል አይደለም፡፡በመታለል ማታለልን የተማሩ ስለበረከቱ፡፡

Comments are closed.

Previous Story

ኢትዮጵያ 2011 ዓመታትን ወደ ኋላ ተጉዛ ዘመነ ሄሮድስ ደረሰች! – ነፃነት ዘለቀ

95733
Next Story

አስቀያሚው የኢሕአዴግ ድራማ የሽፍጥ ፖለቲካ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop