የሕወሓት ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ አስመላሽ ወልደ ሥላሴ ከጥቂት ሳምንታት በፊት በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ደብዳቤ ከፓርላማ የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትርነት መባረራቸው ይታወቃል፡፡
https://www.youtube.com/watch?v=t3iQJJTX8eQ&t=357s
ይሁንና አሁን በኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት በአማካሪነት እንደተመደቡ ሪፖርተር ጋዜጣ ዘግቧል፡፡
የሕወሓትና የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ አስመላሽ ወልደ ሥላሴ፣ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትር በመሆን እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ሲሠሩ እንደነበር ይታወሳል። በቅርቡ ተካሂዶ በነበረው የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ አቶ አስመላሽ በኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት በአማካሪነት እንዲያገለግሉ ስምምነት መደረሱን ያወሳው ጋዜጣው በአሁኑ ወቅት ሥራ መጀመራቸውን አስታውቋል፡፡
በአቶ አስመላሽ ምትክ የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትር እስኪሾም ድረስ፣ ቀደም ሲል በፓርላማው የመንግሥት ረዳት ተጠሪ ሆነው የተሾሙት የኦዴፓ አባል አቶ ጫላ ለሚ የመንግሥት ተጠሪ ኃላፊነትን በውክልና እንዲሠሩ መወሰኑን የሪፖርተር ምንጮች ተናግረዋል። አቶ አስመላሽ በመንግሥት ተጠሪነት ኃላፊነታቸው ምክንያት በፓርላማው ቅጥር ግቢ ውስጥ ይጠቀሙበት የነበረውን ቢሮ አስረክበው እንደወጡ፣ ከፓርላማው ሕንፃ ፊት ለፊት በሚገኘው የኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት ቢሮ መያዛቸውን ለማወቅ ተችሏል። በአሁኑ ወቅት በፓርላማው የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትር ሆኖ የተሾመ ባይኖርም፣ ላለፉት በርካታ ዓመታት የመንግሥት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር ዴኤታ ሆነው ሲሠሩ የነበሩ አራት የፓርላማ አባላት ተነስተው በምትካቸው ሌሎች ተሹመዋል።
ኦዴፓን በመወከል የመንግሥት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር ዴኤታ የነበሩት አቶ ጌታቸው በዳኔ ተነስተው በአቶ ጫላ ለሚ ሲተኩ፣ ደኢሕዴንን በመወከል የመንግሥት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር ዴኤታ በነበሩት አቶ አማኑኤል አብርሃም ምትክ ደግሞ አምባሳደር መስፍን ቸርነት ተተክተዋል።
ሕወሓትን በመወከል የመንግሥት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር ዴኤታ በነበሩት አቶ አፅብሃ አረጋዊ ምትክ አቶ ገብረ እግዚአብሔር አርዓያ የተተኩ ሲሆን፣ አዴፓን በመወከል የመንግሥት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር ዴኤታ በመሆን ለረዥም ዓመታት ሲያገለግሉ በነበሩት አቶ መለስ ጥላሁን ምትክ ደግሞ አቶ ጫኔ ሽመካ መተካታቸውን ለማወቅ ተችሏል። እንደሪፖርተር ዘገባ ላለፉት በርከት ያሉ ወራት ሕወሓትን የሚወክል ሰው በኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት ውስጥ አለመኖሩን የጠቆሙት ምንጮች፣ የአቶ አስመላሽ በኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት መመደብ ይኼንን ክፍተት እንደሚሞላ ጠቁመዋል።