የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ለማ መገርሳ “ኢትዮጵያ እንዳትበተን ለኢትዮጵያ የሚቆም መከላከያን ማጠናከር አለብን፡፡” ሲሉ አሳሰቡ::
https://www.youtube.com/watch?v=t3iQJJTX8eQ&t=357s
ዛሬ 7ኛውን የመከላከያ ሰራዊት ቀን በአዳማ ሲከበር የተካሄደው ህዝባዊ ስብሰባ ላይ ንግግር ያደረጉት አቶ ለማ መገርሳ እንዳሉት ” ለአንድ ሰራዊት የደንብ ልብሱ መለያውና ክብሩም ነው፡፡ ይሄ የደንብ ልብሱ በማንም ሸማቂ የሰፈር ወንበዴ መጠቀሚያ ሲሆን የሰራዊታችንን መልካም ስምና ክብር የሚያጎድፍና ጉዳት የሚያመጣ በመሆኑ መስተካከል አለበት፡፡ ይሄ የመከላከያ ደንብ እንጂ የማንም አይደለም፡፡ ስለዚህ ይህን ወንጀል መከላከል የመከላከያ ሀላፊነት ብቻ አይደለም፡፡ ሁላችን ኢትዮጵያውያን ይህንን ድርጊት ማውገዝና መከላከል አለብን፡፡ ጉዳቱ የአገር በመሆኑ መከላከሉም የሁላችን ሊሆን ይገባል፡፡”
-” መከላከያ የማንም ሀይል አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ነው፡፡” ያሉት አቶ ለማ ” ሰራዊታችን ጀብደኛና እብሪተኛ አይደለም፡፡በትልቅ ወኔና ጥበብ የሚሰራ ሀይል ነው፡፡አንድ ሀገር ጠንካራም ሆነ ደካማ ለመባል አንዱ መስፈርት የመከላከያ ሀይሉ ጥንካሬ ነው፡፡ጠንካራ የመከላከያ ሀይል የሌለው አገር እንደ ደሃ አጥር ማለት ነው፡፡ ውሻውም ሌባውም እንዳስፈለገው የሚገባና የሚወጣበት ክብር የሌለው ነው፡፡ ለኛ ኢትዮጵያውያን ሰራዊታችን ጠንካራ አጥራችን ነው፡፡” ብለዋል::
ንግግራቸውን ቀጥለውም” ግልፅ መሆን ያለበት መከላከያ ፍፁም ነው ማለት አይቻልም፡፡ ድክመቶች ይኖሩታል፡፡ ፓርቲዎችና ፓለቲከኞች ግን አንዳንዴ መከላከያን የፓለቲካ ዕዳችን ማወራረጃ መደረጉ ነው ትልቁ ችግር፡፡ ሰራዊታችንም በዚህ ሲቸገር ይታያል፡፡ እዚህ ላይ ቆም ብለን የችግሩን ባለቤት ማወቅ አለብን፡፡ መከላከያን ከመክሰስና ከመውቀስ የችግሩ ባለቤት ማነው ብለን ማወቅ ይገባናል፡፡ መከላከያ በዚህ ተጎድቷል ዋጋም ከፍሏል፡፡ ይህንን መገንዘብ ይኖርብናል፡፡ ” ያሉት አቶ ለማ ” መከላከያ ክብራችንና መጠጊያችን መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡ የመጨረሻ ምሽጋችንን በላያችን ላይ ማፍረስ የለብንም፡፡ ለመከላከያ ሰራዊታችን የምንሰጠው ክፍያ ሞራልና ክብር ነው፡፡ አለበለዚያ ጉዳቱ ለኢትዮጵያ ነው፡፡ የደህንነት ስጋታችን እየጨመረ ነው፡፡ ሽብርተኝነት አክራሪነት የወሰን ግጭቶች ይታያሉ፡፡ ለብዙ አደጋ ልንጋለጥ እንችላለን፡፡ ስለዚህ የመጨረሻ ምሽጋችን የሆነውን መከላከያ ማጠናከር አለብን፡፡ ኢትዮጵያ እንዳትበተን ለኢትዮጵያ የሚቆም መከላከያን ማጠናከር አለብን፡፡ ነገን ማየት ካልቻልን አስቸጋሪ ነው፡፡ እንደሌሎች አገሮች አሽከርና ሎሌ የሆነ ሰራዊት ቢሆን ኖሮ ባለንበት ደረጃ አንኖርም ነበር፡፡ እናም ይህ ሀይል የመጨረሻ ምሽጋችን አማራጭ ስናጣ የሚያድነን ሀይል ነው፡፡” ሲሉ መል ዕክታቸውን አስተላልፈዋል::