“በቤተክርስቲያን ውስጥ አፈና አለ” – አቡነ መቃርዮስ

ከ22 አመታት የአሜሪካ የስደት ህይወት በኋላ ወደአገራቸው ተመልሰው በገዛ ፈቃዳቸው በቅርቡ አደጋ በደረሰባት የኢትዮጵያ ሱማሌ ጅግጅጋ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የሆኑት አቡነ መቃርዮስ ህዝቡ የተጎዱትን የጅግጅጋ አብያተ ክርስቲያናት መደገፍ እንዳለበት አሳሰቡ፡፡

https://www.youtube.com/watch?v=p8iBU5RCUVc&t=50s

ዛሬ ለንባብ ከበቃው ኢትዮጲስ ጋዜጣ ጋር ቃለምልልስ ያደረጉት አቡኑ ሲናገሩ በጅግጅጋ ለተቃጠሉት ቤተክርስቲያናት መልሶ ማቋቋሚያ የኢትዮጵያ ህዝብ ሊረባረብ እንደሚገባ ያሳሰቡት እስካሁን በአብዛኛው እየተረባረበ ያለው በውጭ አገር ያለው ምእመናን በመሆኑ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ውስጥ አሁን ስላለው ሁኔታ የተጠየቁት አቡነ መቃርዮስ ሲመልሱ ‹‹በቤተክርስቲያን ውስጥ አፈና አለ፡፡ ከስራ አባርርሀለሁ፣ ይህን አደርግሀለሁ የሚል ፉከራ ስላለ ቤተክርስቲያኗ መያዝ የሚገባትን በተለይ ወጣቱን መያዝ አልቻለችም፡፡›› ብለዋል፡፡

ጨምረውም ‹‹አማኙ ህዝብና የሀይማኖት አባቶች ተራርቀውና ተለያይተው ይገኛሉ፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አንጋፋ ሀዋሪያት ቤተክርስቲያን ብትሆንም በአስተዳደሯ ብዙ ችግሮች አሉ፡፡ መንግስትን በመገሰፅ ቀዳሚ መሆን ሲገባት ራሷ ተመካሪ ሆናለች፡፡ ከዚህ አዘቅት በአስቸኳይ መውጣት አለባት›› በማለት አስረድተዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በጅጅጋ በእሳት ከተቃጠሉት 10 አቢያተ ክርስቲያናት አንዷ የነበረችዉ የቀብ ዲሀር ማርያም እድሳቷ ሙሉ በሙሉ መጠናቀቁን ከስፍራው የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  በምስራቅ ጎጃም አርሶ አደሮች በፖለቲካ አመለካከታቸው የተነሳ ማዳበሪያ እየተከለከሉ ነው ተባለ
Share