ተጨማሪ ሚስጢራዊ የማሰቃያ እስር ቤቶች ተገኙ

 የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት በተለያዩ ሀላፊነት ሲሰሩ በነበረበት ወቅት የተሰጣቸውን ስልጣን ወደጎን በመተው በዋና ወንጀል አድራጊነት  በመሳተፍ የጌታቸው አሰፋን ትዕዛዝ በማስፈጸም ሕዝብን ሲያሰቃዩ ነበር በሚል ተጠርጥረው የታሰሩት ማእሾ ኪዳኔ እና ሃዱሽ ካህሳይ ዛሬ ፍርድ ቤት ሲቀርቡ  መርማሪ ፖሊስ የስብዓዊ መብት ጥሰት ሲፈፀምበት የነበረ ተጨማሪ ሚስጥራዊ የማሰቃያ እስር ቤቶችን ማግኘቱን ለፍርድ ቤት ገለጸ::

1ኛ ተከሳሽ ማእሾ ኪዳኔ  ተጠርጣሪው አሁን ካልተያዙት የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት የቀድሞ ሀላፊ አቶ ጌታቸው አሰፋ ጋር በመመሳጠር በህገ ወጥ መንገድ በወቅቱ በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር የነበሩ ግለሰቦች ላይ ድብደባና ስቃይ እንዲሁም አስነዋሪ ተግባራትን በመፈፀም እንዲሁም በኬተሰቦቻቸው ጋር እንዳይገናኙና ፍርድ ቤት እንዳይቀርቡ አድርገዋል በሚል ተከሰዋል: እንዲሁም ከሚያገኙት ገቢ በላይ ምንጩ ያልታወቀ ከፍተኛ ሀብት አፍርተው መገኘታቸውም  በሌብነት ወንጀል እንዳስጠረጠራቸውም በክሱ ላይ ቀርቧል::

2ኛ ተጠርጣሪ አቶ ሀዱሽ ካህሳይ የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ሲሰሩ በቁጥጥር ስር ባሉ ተጠርጣሪዎች ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት ወንጀሎች እንዲፈፀሙ በማድረግ፣ወንጀሉ መፈፀሙን እያወቁ ለህግ አካል ባለማቅረብ እና ከሚያገኙት ገቢ በላይ ምንጩ ያልታወቀ ከፍተኛ ሀብት አፍርተው ተገኝተዋል በሚል በሌብነት ወንጀል ጭምር መጠርጠራቸው ከፖሊስ ክስ ለመረዳት ተችሏል::

በዛሬው የችሎት ውሎ ፖሊስ ከዚህ ቀደም በተሰጠው የምርመራ ጊዜ ወቅት ያከናወናቸውን ስራዎችም ለፍርድ ቤቱ ያስረዳ ሲሆን፥ በዚህ ወቅትም ከአምስት ሰዎች ተጨማሪ የቃል ምስክር መቀበሉን ገልጾ ሲሰሩበት ለነበሩበት መስሪያ ቤትም የነበሩበትን የስራ ሀላፊነት ለመለየት ደብዳቤ ልኮ ውጤት መቀበሉንም ለፍርድ ቤቱ ነግሯል::

ተጨማሪ ያንብቡ:  ብሔራዊ ቡድናችን ለብራዚሉ የዓለም ዋንጫ የሚያደርገውን ጉዞ እያሳመረ ነው

በተጨማሪም ከዚህ በፊት ከተጠቀሱት ሚስጥራዊ የማሰቃያ እስር ቤቶች በተጨማሪ አንድ አዲስ ሚስጥራዊ የማሰቃያ እስር ቤት ማግኘቱንም የገለጸው  መርማሪ ፖሊስ ተጨማሪ የምስርክ ቃል መቀበል፣ የተጎዱ ዜጎችን የህክምና ውጤት መቀበል፣ ለመስሪያ ቤቶች የተጻፉ ደብዳቤዎችን ማሰባሰብ እና የምርመራ ቡድን በማቋቋም በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች ከሚገኙ ተጎጂዎች የቃል ምስክርነት መቀበል እንደሚቀረው ገልጾ 14 ቀን ተጨማሪ ጊዜ ቢጠይቅም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 10ኛው የወንጀል ችሎት  10 ቀን ብቻ ፈቅዷል::

https://www.youtube.com/watch?v=rcbWeNfbu_o&t=32s

Share