ኢትዮጵያዊነትን ማን ነካክሶ አቆሰለው (ክፍል ሁለት) – ያየያየ ይልማ

ኢትዮጵያዊነትን ከነማቀፊያዎቹ የማፈራረስ ፤ በአንፃሩ እራሳቸውንም ቢሆን የፈጠረ በንድፈሃሳባዊ አስምህሮት ድምዳሜ እና ከርሱ ውስጥ በተጨመቀ ጥላቻ የተፈጠሩ ፓርቲዎች ግንባር አበጅተው፤  በተለየ መልኩ ጎጠኛ እና በጠባብ ደርዝ የተበጀ ጎራና ፅንፈኛ የብሄር-ማንነትን ብቻ የሚረዱ አዲስ አገር ተረካቢዎችን የማፍራት ራእይ ይዘው ከተነሱ ፓርቲዎችን ትልምን የተወለደ ነው፡፡ ይህ በእውነት ላይ የተመሰረተ የድምዳሜ መግለጫ ፤ እነኚህ ከላይ የጠቀስኳቸው ፣ በህዳር 29 1987 ህዝብ መርጦናል ብለው እራሳቸውን በሚገልፁ ፓርቲዎች ሰነድ ላይ ግልፅ አድርገው ያሰፈሩት ሃቅ ነው፡፡

በአሁኑ ሰአት ኢትዮጵያን እያስተዳደረ ያለው መንግስት በህዳር 29 ፣ 1987 አ.ም. ቀርፆ በሚጠቀምበት ህገመንግስት ላይ (የኢትዮጵያ ብሔሮች ብሔረሰቦች መርጠው በላኳቸው ተወካዮቻቸው አማካኝነት)በሚል ግልፅ የስምምነት ተዋዋይ አካላት ማንነትን በመጥቀስ፡ ከዚያም ለዚህ መንግስትን የመመስረት አቅም በተሰጠው ህግ ውስጥ ውል ተዋዋይ ሆነው የቀረቡት ተስማሚዎች በተፈረጀ የብሄር ኪስ ውስጥ ያሉ እንጂ፤ ኢትዮጵ የምትባለውን አገር ክልል ሳይጠሩ የሞቱላት፤ ብሄር ሳይለዩ ተዋልደው ለደባለቋት፤ አንድ በመሆናቸው ፈርጣማ የምእራባዊያንን ጡንቻ ያፈረሱት አንድነት፤ ይህንን ሁሉ ትውፊት እና እውነት በዜጎች – ኢትዮጵያዊነት የሚል ስያሜን እያንፀባረቀ ዛሬ ድረስ ይዞ የመጣውን የአንድን ግለሰብ ህብረ-ብሄራዊ ማንነት ፤ በብሄረሰብ ተወካይ ነን ባዮቹ እና የዚህ ህገመንግስት ቀራፂዎች፤ በኢትዮጵያዊነት ላይ ባላቸው ቁርጠኛ አቋም ምክንያት ምንም አይነት ውክልና ሳይሰጥ ከመግቢያው ጀምሮ፤ በህገ-መንግስቱ አንቀፅ 8 ላይ የዚህ ህግ አገልጋይነት በገሃድ የተፃፈ ነው፡፡

ከዚህ በፊት ፡ በዚህ አርእስት ስር በፃፍኩት የመጀመሪያ ክፍል ውስጥ የጠቀስኩት አንቀፅ 39 በዚህ ገሃዳዊ የኢትየጵያዊነት ክህደት ውስጥ የተወለደ ርቢ አንቀፅ እንጂ ፣ ዋነኛ ኢትዮጵያዊነትን የማቁሰል ስራ ከተሰራባቸው መርዛም ጥርሶች የመጀመሪያው አልነበረም፤ ነገር ግን በኢትዮጵዊነታችን ላይ ከባድ ስንጠቃ እና ቁስለት ያደረሰ ነው፡፡ በተጨማሪ ግን በዚሁ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ህብረ-ብሔራዊ ኢትዮጵያዊያንን እንደ ሌሉ ቆጥሮ የተፃፈ ህገመንግስት መነሻነት ብዙ አስገራሚ በደሎችን ኮትኩቶ አፍርቷል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኤርትራና ሲንጋፖር - አብራሃም ለቤዛ

ይህ በህዳር 29 ፣ 1987 አ.ም. ህግ ተደርጎ በፓርቲ ውክልናቸው ኢትዮጵን የሚወክሉ ተደርገው በተስማሙ ፅንፈኞች ተበጅቶ ባደላደላቸው መሬቶች የረቡ እጅግ ብዙ ተጨባጭ ንክሻዎች ኢትዮጵያዊነትን ሲያቆስሉት በዚህ ሁለት ከግማሽ አስርተ አመታት ጊዜ ውስጥ መጠኑ እና አደጋው የደረሰበት ስፍራ ይለያይ እንጂ ሁሉም ያጠቁት ረቂቁን ኢትዮጵያዊነትን፣ በዚህም ገፈቱን የተቀበለው ይኸው ኢትዮጵያን እንደ አገር እንድትኖር የማድረግ አቅም ያለውን ህብረብሄራዊ ህዝብ ነው፡፡ ለዚህ ማስረጃዎች ለመጥቀስ ያክል የበደኖ እና የአርባጉጉ አሰቃቂ እውነት በቂ ናቸው፤

የኢትዮጵ ታሪክ በመጀመሪያ የሶስት ሺህ መሆኑ ቀርቶ እስከ መቶ አመት ድረስ ነው ተብሎ ተተረከ፤ ከዚያ ደግሞ ያው የመቶ አመት ታሪክ ብቻ ነው ያለን የተባለው ኢትዮጵያ የምትባል ሃገር ታሪክ እንደ አዲስ ሊተረክ ተሞከረ፡፡ ከዚያም ታሪክን ለእንጀራ መጋገሪያነት በሚፈጥሩ፣ በሚቆርጡና በሚቀጥሉ፡ ውሾች ታሪክ- እንደ ተፈለገው ተስተካክሎ፤  የኢትዮጵያ ታሪክ የሃያ አምስት አመት እውነት ብቻ ያለው ታሪክ ሆኖ አስገራሚ ሃውልቶች ቆሙለት- (የጨለንቆ፣ የአኖሌ፣ የጀጎል) ከብዙ በጥቂቱ፡፡

በአንፃሩ ማደግ የሚገባቸው ከተሞች ከነ ህብረ ብሄራዊ ህዝባቸው ሞቱ( ድሬዳዋ፣ ጅማ፣ አዲስ አበባ ደሴ) እንዲሁም አብሮአቸው ከብሄርተኝነት ውጪ የነበረው ረቂቁ ኢትዮጵያዊ ማንነት፣ ስሜቱ ፣ ኩራቱ፣ ውበቱ፣ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ የሆነውን የቀለማት ህብር ሲይ እና ሲያስብ የሚወክላቸው ፣ አስገራሚ ሃይል ይይዙ የነበሩት የኩራት ውርሶች በግርድፍ የጭቆና ጥቀርሻ ተለውሰውና ተሸፍነው መልክ እንዲያጡ ተደረገ፡፡ እናም አድዋን ጨምሮ ፤ ከቅርስ እስከ ስነቋንቋ እና ተፈጥሮአዊ ግርማችንን ለኢትዮጵዊያን የሚሰራ መንግስት ይመሰርታል በተባለ ህግ ፈር ቀዳጅነት ተነጠቅን፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  በግሎባል የምሁራን መድረክ ላይ የምዕራቡን ካፒታሊዝም የፖለቲካ አስተሳሰብና አካሄድ በሚመለከት በፕሮፌሰር መሳይ ከበድና በዶ/ር ዮናስ ብሩ ኢ-ሳይንሳዊ በሆነ  መልክ የተሰነዘረውን አስተሳስብ የሚቃወም ትችታዊ አቀራረብ!

ኢትዮጵዊነት ብቻ የኔ ሊላቸው የሚቻሉ ግዙፍ ብሄራዊ እሴቶቻችን ሞራላዊ ወራሽ አጡ እና ዛሬ ኢትዮጵዊነትን የሚጠየፉ፣ ከስም ከክብሩ ጋር መደመርን የሚንቁ ፣ የመከኑ ልጆች ሃያ አመትና ከዚያ በላይ እድሜ ሞልቷቸው የአባቶቻቸውን ታሪክ ካዱ፡፡ ከዚያም ለልጆቻቸው እና ለልጅ ልጆቻቸው የፀብ መጫሪያ ፣ በፈጠራ ታሪክ ላይ የተመሰረቱ የቁርሾ ድንጋዮችን አቁመው፤ ኢትዮጵያዊነትን አቆሰሉት፤ ቁስሉንም የሚሸትት አደረጉት፡፡

በምኒሊክ እና በአሚር አብዱላሂ መካከል የተደረገ አንድ ጦርነት፣ ሁለት ብሄረሰቦችን በተለያዩ መንገዶች እያስለቀሰ የበደል ታሪክ ተደርጎ ይነገራል! የሚገርመው ግን ይሄ አይደለም፡ ይህ በደል በኦሮሞም በአደሬም የይገባኛል ጥያቄ ቀርቦበታል፡፡ አደሬዎች ሃረር ላይ ለጉብኝት ለሚመጣ ጎብኚ የሚስገርም ዝርዝር የጥላቻ እና የቂም በቀል የጉብኝት ፕሮግራም አዘጋጅተው፣ መድሃኒአለም ቤተክርስቲያን ፊት ለፊት የተሰራውን ሃውልት እያሳዩ ያስረዳሉ፡ በእንዳንዱ የአደሬ ቤት ውስጥ የሚነጠፈው ቀይ ምንጣፍ ሳይቀር ይህንን አህመራ ብለው በመጥራትም ጭምር ግልፅ ጥላቻን እንደ መስህብ እያስጎበኙ ገንዘብ ሲሰበስቡ፣ የአደሬን ህዝብ ቁጥር አናሳ መሆን ሳይቀር በአፄ ምኒሊክ ላይ አሳብበው፡ ታሪኩ ሌላ ሆኖ ሳለ! ለስራ ጉዳይ የመጣ የቻይናዊን ቁጥር እንዲበልጠን ያደረገው ምኒሊክ ነው ብለው በፈጠራ ታሪክ የኢትዮጵ አካል እንዲሆኑ ኦሮሞን እንወክላለን በሚል ድምፅ የሚያሰሙትም እንዲሁ ጨለንቆንና ጦርነቱን በዝርዝር ውሸት አሽገው እንዲሁ በየሜዳው የአዞ እንባ እያነቡ ይሄንኑ መጀመሪያም በውሸት እንዲፈራርስ የተቀረፀን የክፉዎችን እቅድ ለማሳካት የራሳቸውን አስተዋፅኦ ይጫወታሉ፡፡

ይህ በህገመንግስታዊ ርችት የተጀመረው ኢትዮጵያዊነትን የማጥፋት እና የማዳከም ስራ ይኸው ሃያ አምስት አመታትን ተሻግሮ ዛሬ ነገሮች ጥግ ላይ የደረሱበት እጅግ ክፉው ጊዜ ነው፡፡ ሁሉም ሰው ሊኮራባቸው የሚገባቸው ውብ ውርሶቻችን በሙሉ ጥያቄ ውስጥ ገብተው ፤ ኢትዮጵያዊነት ለሁሉም ሰው ከሚመስጥ ረቂቅ ቁም ነገርነት ፡ ደብዛው ወደ ሳሳበት ስሙም ሆነ ኩራቱ ደብዝዘው እንቆቅልሽ የመሆን ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ ሰዎች ኢትዮጵያዊነት ሲያወሩ በማታቀሻ ውስጥ ካልሆነ በስተቀር ኢትዮጵያዊነት የሚለው ማንነታችንና መገለጫችን መሆኑ ቀርቶ የልዩነት ማሳያ ገላ ሆኖ  በአየሩ ሁሉ ተቀርፆ ይገኛል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኢትዮጵያ አፈር የጠራው ጠቢብ፣ የድሆች አባት ዶ/ር በርናርድ ተለየን ! -ነቢዩ ሲራክ

በአንድ ወቅት ከአለም ታላላቆቹ አራት ተጠቃሽ መንግስታት አንዱ የነበረውን የታለቋ የኢትየጵያን የማንነት ጥሪት ፤ በጥላቻ አስምህሮት አስገራሚ ሊቅነትን የተጎናፀፉት ሟቹ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ማንም እንዳይኮራበት በንግግራቸው ሲሰብኩ እነኚህንም ኢትዮጵያዊያን የጋራ የሚሏቸውንም ሃብቶች ለብሄር ብሄረሰቦች ለቅርጫ በሚሰጥ ሃሳብ ተጠቅመው ነበር፤ ላሊበላ ለወላይታ ምኑ ነው ብለው የህገመንግስቱን ግልፅ ኢትዮጵያዊነትን የማጥፋት ራእይ በንግግራቸው ፈንትው አድርገው አሳይተው የቋጩት፡፡

ይህ ከላይ የተጠቀሰው ኢትዮጵያዊነትን ማን ነከሰው እና ኢትዮጵያዊነትን ማን ነክሶ አቆሰለው በሚል ርእስ (በክፍል አንድና ሁለት) የቀረበው እጅግ ባጭሩ በኢትዮጵያዊነት ላይ የተደረገን ጥቃት ለማስቀመጥ የሚሞክር ፅሁፍ መሰረቱ በአሁኑ ሰአት ስራ ላይ ባለው ህገ-መንግስት ላይ መነሻውን ያድርግ እንጂ፣ ከዚህ ህገ መንግስታዊ የጥፋት መንደርደሪያነት በኋላ እለት እለት ላለፉት ሃያ አመታት በኢትዮጵያዊነት ላይ የተደረጉ ጥቃቶችን በዝርዝር አስቀምጦ የማስታወስ፣ የማስተማር እና የመፍትሄ እርምጃ ከእያንዳንዱ ከሚገደው ኢትዮጵያዊ ዜጋ እንዲነሳ የማበረታታት ፍላጎት ያለው ነው፡፡ ስለሆነም እጅግ ብዙ አርእስቱ በተጨባጭ የሚመለከታቸው ዜጎችን በሚመለከት ዝርዘር ሃሳቦችን ከከተማ እስከ ገጠር ዜጎች ማንነታቸው በምን አይነት መንገድ በዚህ ክፉ ራእይ ምክንያት እየተጠቃ እንዳለ  እናያለን! ቸር ሰንብቱ!!

1 Comment

  1. Yanten Ethiopia latimeles ashelibalech.be amara maninet yemitigeletsi ethiopia kengidihi atinormi etmihin awuta.yededeboch zemen tarik lerasih adirgew.
    shintun enkuan yemayitateb neftegna dagim liyastedadiregn ayichilim.

Comments are closed.

Share