December 21, 2016
6 mins read

በሞሮኮ የሚገኘው የአላሙዲ የነዳጅ ማጣሪያ በታክስ ማጭበርበርና በገንዘብ እጦት እንዲፈርስ ተወሰነ – ሼህ አላሙዲ ወዴት?

ሼህ መሐመድ አላሙዲ ሕወሓት በሚመራው መንግስት ከታክስ ማጭበርበር ጋር ስማቸው ሲነሳ ሰንብቷል:: አሁን ደግሞ ከወደ ሞሮኮ የተሰማው ዜናም ተመሳሳይ ነው:: ሪፖርተር ጋዜጣ እንዳስነበበው የሞሮኮ መንግሥት ሼኩ የሚመሩት ድርጅት 1.34 ቢሊዮን ዶላር የታክስ ዕዳ እንዳለበት አስታውቋል:: ሼኩ ወዴት እየሄዱ ነው? – የሪፖርተር ዘገባን ያንብቡ::

የሼክ መሐመድ ሁሴን አል አሙዲ ኩባንያ የሆነው ኮራል ፔትሮሊየም ሆልዲንግስ 67 በመቶ ድርሻ በመያዝ የሚያስተዳድረውና በሞሮኮ ብቸኛው የነዳጅ ማጣሪያ እንደሆነ የሚነገርለት ሳሚር ግሩፕ፣ በፍርድ ቤት ትዕዛዝ ይፍረስ የተባለው ባጋጠመው የገንዘብ ቀውስ ምክንያት መሆኑ ታውቋል፡፡

በቀን 200 ሺሕ በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ የማጣራት አቅም ያለው ሳሚር ግሩፕ ባጋጠመው የፋይናንስ ቀውስ ሳቢያ፣ ካለፈው ነሐሴ ወር ጀምሮ ሥራ ለማቆም ተገዷል ያለው የሮይተርስ ዘገባ ሲሆን፣ የሞሮኮ ፍርድ ቤትም ቀውሱን ተከትሎ ኩባንያው እንዲፈርስ ወስኗል፡፡ ኩባንያውን የማፍረስና በሽያጭ ወደ ሌሎች የማስተላለፍ ሒደት እንዲመሩ የንብረት ጠባቂ ግለሰብ በመሰየም ሽያጩ እንዲከናወን አዟል፡፡

የንብረት ጠባቂ ሆነው በፍርድ ቤት የተሰየሙት መሐመድ አል ከሪሚ ፍርድ ቤት ከዚህ በፊት ሰጥቶ የነበረው የሽያጭ ትዕዛዝ ላይ ማራዘሚያ መጠየቃቸውንና ፍርድ ቤቱም ጥያቄያቸውን መቀበሉን ለዜና አውታሩ ገልጸዋል፡፡

በሦስት ወራት ውስጥም ነዳጅ ማጣሪያውን የሚገዙ አካላት የግዥ ጥያቄ የሚያቀርቡባቸውን ሰነዶች በማስገባት፣ ደህና ዋጋ ለሰጠ ኩባንያ በሽያጭ እንደሚተላለፍ አል ከሪሚ አስታውቀዋል፡፡

ነዳጅ ማጣሪያው እስኪሸጥ ድረስ ለጊዜው ሥራ እንዲጀምር ለማድረግ ቢሞከርም እንዳልተሳካ ታውቋል፡፡ ይህም የሆነው ድፍድፍ ነዳጅ የሚያቀርብለት በመጥፋቱ እንደሆነ ከሞሮኮ የወጡ ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡

ኩባንያው እንዲፈርስ ትዕዛዝ ከወጣበት ካለፈው ዓመት ጀምሮ በሞሮኮ ፍርድ ቤት ሀብትና ዕዳው እየተጣራ እንደሚገኝ ሲታወቅ፣ ኩባንያውን ከመፍረስ ለመታደግ ከገንዘብ አበዳሪዎች ፋይናንስ ለማግኘት ሲደረጉ የነበሩ ጥረቶች ሳይሳኩ መቅረታቸውም ተሰምቷል፡፡ ባንኮችን ጨምሮ በነዳጅ ንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ አካላት ለሳሚር ግሩፕ ገንዘብ እንዲያበድሩ ኮራል ሆልዲንግስ ሲያደርግ የነበረው ጥረትም እንዲሁ መና ቀርቷል፡፡

የሞሮኮ መንግሥት ሳሚር ግሩፕ ያልከፈው የ1.34 ቢሊዮን ዶላር (የ13 ቢሊዮን የሞሮኮ ድርሃም) የታክስ ዕዳ እንዳለበት አስታውቋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከአራት ቢሊዮን ዶላር በላይ አጠቃላይ ውዝፍ ዕዳ ስላለበት እንዲሸጥ ተወስኖበታል ተብሏል፡፡

ሼክ መሐመድ አል አሙዲ በሳዑዲ ንጉሣውያን በኩል የሞሮኮ ንጉሥን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ ባለሥልጣናትን በተደጋጋሚ በማነጋገር፣ የሞሮኮ መንግሥት ውሳኔውን እንዲለውጥ መጣራቸውን ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡ ቢሊየነሩ ያደረጓቸው ሙከራዎች ባለመሳካታቸው ኩባንያቸው ተሸጦ ዕዳውን እንዲከፍል ሞሮኮ በመወሰኗ ገዥዎች እየተጠበቁ ይገኛሉ ተብሏል፡፡

በሼክ አል አሙዲ ዳይሬክተርነትና የቦርድ ሊቀመንበርነት የሚመራው ኮራል ፔትሮሊየም ሆልዲንግስ ኩባንያ 67.25 በመቶ ድርሻ እንዳለው የሚነገርለት ሳሚር ግሩፕ፣ ከዚህ ቀደም የሞሮኮ ፍርድ ቤት ያስተላለፈበትን ውሳኔ በመቃወም ይግባኝ ቢልም ውድቅ እንደተደረገበት ተዘግቧል፡፡ ፍርድ ቤቱ ከኩባንያው የሚፈልገው ውዝፍ ታክስና ሌሎች ዕዳዎችን ለማስከፈል የይፍረስ ውሳኔ ባሳለፈበት ወቅት፣ የኩባንያው የባንክ ሒሳቦችም እንዳይንቀሳቀሱ አግዶ እንደነበርም ታውቋል፡፡

Previous Story

የጥንታዌት ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን  አጭር ታሪክና ሥርዓት

welkayet satenaw
Next Story

በጐንደር ክፍለ ሀገር ከወልቃይት ጠገዴና ጠለምት የአማራ ማንነት አስተባባሪ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ!!

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop