Sport: ፑቲንና የሩሲያ እግር ኳስ

በራሺያ እግርኳስ ተፅዕኖ ፈጣሪ ናቸው የሚባሉት የክለብ ባለስልጣናት ለአንድ ጉዳይ ያስፈለገው በቅርቡ ወደ ራሺያ የተቀላቀለችውን የክሬሚያ የእግርኳስ ክለቦች እጣ ፈንታ ለመወሰን ነው፡፡ በባለስልጣናቱ ድምፅ ውስጥ ግን ፍርሃት ይሰማል፡፡ ጭንቀታቸውንም መታዘብ ይቻላል፡፡ ሶስቱን የክሬሚያ ክለቦች ወደ ራሺያ ሊግ መቀላቀል ሊያመጣ የሚችለው አስከፊ ውጤት አሳስቧቸዋል፡፡ የራሺያ ክለቦች ከአውሮፓ ውድድሮች ሊታገዱ እንደሚችሉ በማሰብ ደንግጠዋል፡፡ ሀገራቸው ከ2018 የዓለም ዋንጫ አስተናጋጅነት ልትሰረዝ እንደምትችል በመገመትም ጭንቀት ወጥሮ ይዟቸዋል፡፡ ከሁሉም በላይ ያሰጋቸው ግን ሌላ ጉዳይ ነበር፡፡ ሶስቱን ክለቦች ወደ ራሺያ ሊግ አለመቀላቀል ሊያስቆጣው የሚችል አንድ ሰው አለ – የራሺያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን፡፡

የእነዚህ ሰዎች ስብሰባ ተቀርጿል፡፡ ቅጃ ደግሞ በአንድ የራሺያ ጋዜጣ ላይ ወደ ፅሑፍ ተቀይሮ ወጥቷል፡፡ የራሺያን እግርኳስ የሚቆጣጠሩት ባለስልጣናት ሊግ እንዲወዳደሩ ቢፈቅዱ ከምዕራባውያኑ ሊደርስባቸው የሚችለውን ማዕቀብ በሌላ በኩል ይህን ባያደርጉ ደግሞ ከፑቲን የሚደርስባቸው አፀፋ ወጥሮ ይዟቸው ለመወሰን ተቸግረዋል፡፡ በቅጂው ላይ ከፑቲን መመሪያን ለመቀበል በመወሰን መፍትሄ ላይ ደርሰዋል፡፡ ይህ ደግሞ የሀገራት እግርኳስ ማህበራት ከማንኛውም ፖለቲካዊ ተፅዕኖ ነፃ መሆን እንዳለባቸው የሚያዘውን የፊፋ ህግ የሚጥስ ነው፡፡ ብዙዎች ተቀርፆ በወጣው ካሴት ላይ ጥርጣሬ ቢኖራቸውም አንድ የስብሰባው ተሳታፊ ለሞስኮ ራዲዮ ውይይቱ እንደተካሄደ ገልፀዋል፡፡

ስብሰባው ከፍተኛ ባለሀብት የሆኑት ተሳታፊዎቹ የራሺያ መንግሥት ምን ያህል እንደሚፈሩ ያሳየ ነበር፡፡ ፑቲን ያላቸው ተፅዕኖ እስከምን ድረስ እንደሆነም ያመለከተ ነው፡፡ የምዕራባውያኑ ሀገራት ማዕቀብ ሀገሪቱ ላይ ያሳረፈውን ተፅዕኖም እስከየት ድረስ እንደደረሰ በስብሰባው ተሳታፊዎች መነፅር መመልከት ይቻላል፡፡ ከውይይቱ ተሳታፊዎች መካከል የሀገሪቱ ትልልቅ ባለሀብቶች ይገኙበታል፡፡ ከእነዚህ መካከል ሱለይማን ኬሪሞቭ አንዱ ናቸው፡፡ የሰውዬው ሀብት በዓለም 72ኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧቸዋል፡፡ የሀገሪቱ ትልልቅ ክለቦች ዜኒት ሴንት ፒተርስበርግ እና ሲኤስኬኤ ሞስኮው መሪዎች በስብሰባው ተሳትፈዋል፡፡ የራሺያ መንግሥት የምድር ባቡር ኃላፊ እና የፑቲን የቅርብ ጓደኛ የሆኑት ቭላድሚር ያኩኒንንም በውይይቱ ተገኝተዋል፡፡ የእግርኳሱ ባለስልጣናት በክሬሚያ ክለቦች እጣ ፈንታ ላይ ተሰባስበው እንዲወስኑ የታዘዙት በራሺያ እግር ኳስ ማህበር ነው፡፡ የዩክሬን ግዛት የነበራቸው ክሬሚያ ራሺያን የተቀላቀለችው ባለፈው ማርች ነበር፡፡ ባለፈው ሳምንት የራሺያ የስፖርት ሚኒስቴር ሶስቱ የክሬሚያ ክለቦች ሲምፌሮፓል፣ ሴባስቶፖል እና ያልታ የሀገሪቱን የታችኛውን ዲቪዚዮን እንደሚቀላቀሉ አስታውቆ ነበር፡፡ በዚህ የተነሳ የዩክሬን እግርኳስ ፌዴሬሽን ‹‹ክለቦቼን ተሰርቄያለሁ›› ሲል ቅሬታውን አሰምቷል፡፡ ባለፈው ማክሰኞ ግን ሶስቱ ክለቦች በራሺያ ዋንጫ የመክፈቻ ጨዋታቸውን አድርገዋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኦምሃጅር ከተማ ቀን እየወጣላት ነው

በስብሰባው የተሳተፉ አብዛኞቹ ባልጣናት ማዕቀብ ቢያስከትልም ውሳኔ ላይ መድረስ እንዳለባቸው አውቀውታል፡፡ ባለስልጣናቱ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነበሩ፡፡ የክሬሚሊንን መንገድ ከተከተሉ ከምዕራባውያኑ ማዕቀብ ይጠብቃቸዋል፡፡ ይህን ካላደረጉ ደግሞ የፑቲንን አይን ለማየት አይደፍሩም፡፡ ሰርጌ ስቴጋሺን የቀድሞ የራሺያ የደህንነት ሚኒስትር እና የሀገሪቱ እግርኳስ ማህበር ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል ናቸው፡፡ በድብቅ በወጣው ካሴት ላይ በስብሰባው ‹‹ችግር ውስጥ ነን›› ማለታቸው ተደምጧል፡፡

የሲኤስኬኦ ሞስኮው ፕሬዝዳንት ኤቭጌኒ ጊነር ድምፅ በመስጠታቸው እነርሱ ባልተሳተፉበት ውሳኔ የመጣ መዘዝ ገፈት ቀማሽ እንደሆኑ በመናገር ቅሬታ አቅርበዋል፡፡ ጊነር ‹‹እኛ ያልተሳተፍንበት ውሳኔ›› ያሉት የክሬሚያን በራሺያ መጠቅለል ነው፡፡ ‹‹ተመለከቱ! እርሱ ምንም የሚያጣው ነገር የለም›› ብለው የእግርኳስ ማህበሩን ፕሬዝዳንት ኒኮላይ ቶልስቲይክ ሲተቹ ተደምጠዋል፡፡ ‹‹እኔ ግን የምመራው ክለብ አለኝ፡፡ (ክለቦቹ እንዲቀላቀሉ በመወሰናችን) የ2018 ዓለም ዋንጫ አስተናጋጅነታችንን ይነጥቁናል፡፡ ለምን? ምክንያቱም በፕሬዝዳንቱ ስም የተሸፈኑ ጥቂት ብልጥ ሰዎች ‹‹እደግፋለሁ›› ወይም ‹‹አልደግፍም›› የሚለው ላይ ምልክት እንድናስቀምጥ በማስገደዳቸው ነው››

አሜሪካ እና የአውሮፓ ህብረት ራሺያ ላይ በተከታታይ ማዕቀብ ጥለዋል፡፡ ሀገሪቱ በምስራቅ ዩክሬን በተከሰተው ቀውስ ላይ ቤንዚን እያርከፈከፈች እንደሆነ ማመናቸው ደግሞ ምክንያታቸው ነው፡፡ በዚያ ላይ አፍቃሪ ራሽያ የሆኑትንና የዩክሬን መንግሥት ጋር ጦርነት የሚያደርጉትን ቡድኖች ትደግፋለችም ይሏታል፡፡ የመጀመሪያው ዙር ማዕቀብ ኢላማ ያደረገው ሉፑቲን ቅርብ የሆኑ ሰዎችን ነው፡፡ የምድር ባቡር ኃላፊ ያኩኒን አንዱ ናቸው፡፡ በስብሰባው የሥራ ጓደኞቻቸውን ‹‹አርበኞች አይደላችሁም›› ሲሉ እንደዘለፏቸው ተሰምቷል፡፡ ከዚያ በኋላ የተጣሉት ማዕቀቦች የራሺያ የፋይናንስ ተቋማትን ኢላማ ያደረጉ ናቸው፡፡ ‹‹ምንም ብታደርጉ ማዕቀቡ አይቀርም›› ብለው ያኩኒን ጓደኞቻቸውን እንዳስፈሯሯቸው የስብሰባውን ቅጂ በፅሑፍ ያተመው ጋዜጣ አስነብቧል፡፡ ‹‹ተንበርክካችሁ ብትለምኗቸው እንኳን ማድረጋቸው አይቀርም፡፡ ይገባችኋል? ስለዚህ ወይ ከሀገሪቱ ውጡ አልያም እንደ ዜጋ አስቡ›› ማለታቸውም ተሰምቷል እንደ ጋዜጣው ዘገባ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ወታደሮች ተላልፈው ተሰጡ፣300 ሰዎች ራሳቸውን ስተው ተገኙ፣ቄሮ የዘጋው መንገድና መንግሥት ያገደው አካውንት"72 ሰዓት ብቻ"ጠቅላይሚንስትሩ

በስብሰባው የእግርኳሱ ባለስልጣናት በክሬሚያ ጉዳይ ላይ ድምፅ የማይሰጡበትን መላ ሲያፈላልጉ ነበር፡፡ የስፖርት ሚኒስትሩ ክለቦችን ወደ ራሺያ ሊግ የመቀላቀል ውሳኔ ከክሬሚሊን ቤተ መንግሥት በቀጥታ የተላለፈ ትዕዛዝ መሆን አለመሆኑንም ተጠያይቀዋል፡፡ የእግርኳሱ መሪዎች ለክሬሚያ ክለቦች ብለው በአውሮፓ መድረክ በመሳተፍ የሚያገኙትን ጥቅም ላለማጣት ቢያንገራግሩም በቢሊዮነሮቹ እንኳን የፑቲን ቃል ምን ያህል ኃይል እንዳለው በስብሰባው ታይቷል፡፡ ሴርጌይ ጋሊትስኪ ቢሊዮኔር እና የራሺያው ክለብ ክራስኖዳር ቺፍ ኤግዜኪዩቭ ናቸው፡፡ ‹‹ከላይ የመጣ (ከፑቲን) ትዕዛዝ ከሆነ ጥያቄ ማንሳት የለብንም›› ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ የእግርኳስ ማህበሩ ፕሬዝዳንት ቶልስቶይክ የስፖርት ሚኒስትሩ ቪታሊ ሙትዋ የክሬሚያን ክለቦች ጉዳይ እንደፈቱት ሲናገሩ የስብሰባው አንድ ተሳታፊ ‹‹ሚኒስቴሮቹ ምንም ነገር አያገባቸውም›› ብለዋል፡፡ ዋናው የፑቲን ትዕዛዝ እንደሆነ ለማሳየት የተናገሩት ይመስላል፡፡

የስብሰባው ተሳታፊዎች ሊያደርጉ የማይፈልጉት አንድ ነገር ቢኖር የፑቲንን ቃል አለማክበር ነው፡፡ የዜኒት ሴንት ፒተርስበርግ ክለብ ፕሬዝዳንት የሆኑት አሌክሳንደር ዴይኮቭ ብዙ ገንዘብ የሚያስገኝላቸውን የቻምፒዮንስ ሊግ ቦታ ለማጣት መዘጋጀታቸውን በስብሰባው ተናግረዋል፡፡ የፕሬዝዳንት ፑቲንን ቃል ለማክበር ማለት ነው፡፡ ‹‹ያለ አውሮፓ መኖር እንችላለን፡፡ ስለ ዓለም ዋንጫው የምናወራ ከሆነ ግን ጉዳዩ ፖለቲካዊ ጥያቄ ነው›› ይላሉ ዴይኮቭ፡፡ ባለስልጣናቱ በእጅጉ የተጨነቁት ራሺያ በ2018 ዓለም ዋንጫን ከማስተናገድ የሚያግዳት ውሳኔን ላለማስተላለፍ ነው፡፡ የብሪታኒያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ኒክ ክሌግ የራሺያን የ2018 ዓለም ዋንጫን አስተናጋጅነትን ማንሳት የማዕቀቡ አካል እንዲሆን እቅድ አቅርበው ነበር፡፡ ቢያንስ ለጊዜው ሰሚ አላገኙም፡፡ ራሺያውያኑ ግን ተጨንቀዋል፡፡
‹‹የዓለም ዋንጫ አስተናጋጅነቱ ለእንግሊዝ ይሰጣል›› ሲሉ የሲኤስኬኤ ፕሬዝዳንት ጊነር በስብሰባው ላይ ተናግረዋል፡፡ ‹‹የዚያን ጊዜ ፑቲን የሚያሳድደው የእግርኳስ ማህበሩ ሊቀመንበር ቶልስቲይክን አይደለም፡፡ እኛ እዚህ የተቀመጥነውን እንጂ›› ብለው ውሳኔያቸው የሚያመጣውን መዘዝ ለጓደኞቻቸው አስረድተዋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የፋኖ ጉዳይ እና መፍትሔዎች

ይህ በድብቅ የወጣው የስብሰባው ተሳታፊዎች የተቀረፀ ድምፅ ‹‹ነፃ ናቸው›› የሚባሉትን አካላት ሳይቀር የክሬሚሊን መንግሥት እንዴት እንደፈለገ እንደሚያደርጋቸው ያሳያል፡፡ የስብሰባው ተሳታፊ ባለስልጣናት የመንግሥት ከፍተኛ አመራሮች ከእነርሱ ምን እንደሚፈልጉ ስላላወቁ ግራ ገብቷቸው ተስተውለዋል፡፡ ‹‹በአሁኑ ሰዓት ኃይለኛ ፖለቲካዊ ጨዋታ እየተካሄደ ነው›› ይላሉ የክሮስኖዳሩ ቺፍ ኤግዚኪዩቲቭ ጋሊትስኪ፡፡ ‹‹የሀገሪቱ የመጀመሪያ ሰው (ፑቲን) ይህን ነገር ላይፈልገው ይችላል? እርሱን ሳንጠይቅ ውሳኔ ላይ ብንደርስ አያመሰግነንም፡፡ በመጨረሻ ተሰብሳቢዎቹ በውሳኔያቸው ፑቲን ምን ይሉ ይሆን? ብሎ ከመጨነቅ ከበላይ አካል መመሪያ እንዲመጣላቸው ጠይቀዋል፡፡ እፎይ ማለታቸውን ያወቁ ጋሊትስኪ ውሳኔያቸው ምክር መጠየቅ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ‹‹ፖለቲካዊ ምክር››

Share