May 14, 2013
23 mins read

ሰውየው – ክፍል 1

Pen 4
ከይገርማል ታሪኩ 

ሰውየው

መካከለኛ ቁመና አላቸው: ሰውነታቸው ሞላ ደልደል ያለ ወንዳወንድ:: እድሜአቸው ወደ 70 አመት የሚጠጋ ቢሆንም የሰውነት አቋማቸውና ጥንካሪያቸው ሲታይ ሀምሳም የደፈኑ አይመስሉም:: የእግር መንገድ ይወዳሉ:: በውትድርና ያሳለፉት ዘመን ጥንካሪያቸው ላይ አሻራውን አሳርፏል:: እና አሁንምንቁ: ቀልጣፋ: ደፋርና ጠንካራ ናቸው:: ለሽርሽር ብሎ አብሯቸው የወጣን ሰው በላብ እስኪጠነፍር ድረስ ያሽከረክሩታል:: ደከመኝን ብዙም አያውቁም:: ቁጥብ አንደበት አላቸው:: በቁም ነገር ጊዜ ቁምነገር መናገር በቀልድ ጊዜም መቀለድ ይችላሉ:: ቁምነገራቸው ከመሬት ጠብ አይልም:: ጨዋታቸውአይጠገብም:: ካገኙት ጋር ሁሉ አፍ የሚካፈቱ ግን አይደሉም:: ከማን ጋር መዋልና ምን መስራት እንዳለባቸው ጠንቅቀው ያውቃሉ:: ውለታ መዋል ይችላሉ:: ለተቸገረ ደራሽ: አሳቢና ተቆርቋሪ ናቸው:: ቤታቸው የሄደን እንግዳ ጠብ እርግፍ ብለው ያስተናግዳሉ:: ሰው በልቶ የጠገበ አይመስላቸውም:: አንድነገር ብቻ አይወዱም “ጥቃት”:: ጥቃትን ከምንም በላይ: ከራሱ ከሞትም ቢሆን አብልጠው ይጠላሉ:: ያላግባብ ጥቃት የፈጸመባቸውን ሰው ልኩን ሳያሳዩ አይለቁም:: ያም ሆኖ አጥቂው ጥፋቱን አውቆ ይቅርታ ከጠየቃቸው ሁሉንም ነገር እርግፍ አድርገው ወደቀድሞው ለስላሳ ማንነታቸው ይመለሳሉ::የቤተክርስቲያን ሰው ስለሆኑ ይቅርታን የእግዚአብሄር መቅረቢያ መንገድ አድርገው ይወስዳሉ:: “ሽህ ጊዜ ኧረ ከዚያም በእጅጉ ለሚበልጥ ጊዜ ጥፋት እያጠፋን: ከፈቃዱ እየወጣን: በእብሪትና በትእቢት ስንት በደል ከፈጸምን በኋላ ‘በመጥፎ ስራችን ተጸጽተናል ማረን’ ብለን እግዚአብሔርን ይቅርታስንጠይቀው ይቅርታ ያደርግልናል አይደል? ይቅርታ እየለመንንና ይቅርታ እየተደረገልን እያለ በድያለሁና ይቅርታ አድርጉልኝ ብሎ የሚመጣን ሰው አይ አይሆንም ብለን እንዴት ልንገፋው እንችላለን:: ይቅርታ ካላደረግን ይቅርታን መጠየቅ የለብንም:: ይቅርታ የእግዚአብሔር ነው” ይላሉ ከዚህ ጋርየተያያዘ ጉዳይ ሲነሳ ከሰሙ::

ወደውትድርናው የገቡት በቀዳማዊ ሀይለስላሴ ዘመነ መንግስት ነው: በ1950ዎቹ መጀመሪያ አካባቢ:: ትውልዳቸው ከደህና ቤተሰብ ቢሆንም አስተዳደጋቸው ግን እንደማንኛውም ተራ ኢትዮጵያዊ ነው:: ማንኛውም ህጻን ሆኖ ያደገውን ሆነው ነው ያደጉት:: ትምህርት ቤት ገብተው ተምረዋል:: ወጣትነትሁሉን አስፈሪ ነገር ለመድፈር ያስችላል:: ውትድርና ቀላል ነገር አይደለም:: ጨዋታው ከህይወት ጋር የተያያዘ ነው:: በዚያን ጊዜ የነበረ ወታደር ደረቱን ለጦር ግንባሩን ለጥይት ለመስጠት የቆረጠ እንደባህታዊ በየበረሀው በቀበሮ ጉድጓድ ለመኖር: ራሱን አሳልፎ አገርንና ህዝብን ከጥቃት ለመከላከል የተሰለፈነበር:: ኢትዮጵያ ሀገራችን የጠላት ችግር የለባትም:: ከአሁኑ የሶማሊያ ክልል አልፎ እስከ አዋሽ አርባ ድረስ ያለውን መሬት ከኢትዮጵያ በሀይል ነጥቆ ታላቋን የሶማሊያ ግዛት ለመመስረት ያለመው የዚአድባሬ መንግስት: ኤርትራን ከኢትዮጵያ አስገንጥለው የአረቡ ዓለም አካል ለማድረግ በግብጽፊታውራሪነት የተሰለፉት የአረብ ሀገሮች: የኢትዮጵያን ሰላምና እድገት የማይፈልጉት ሁሉ ጀብሀንና ሌሎች ሀገር በቀል አፍራሽ ሀይሎችን አሰልፈው ዙሪያ ገባውን የሚያቆስሉበት ዘመን ነበር:: ያኔ ነው ሰውየው ይህን ራስን ለመሰዋእትነት አሳልፎ በመስጠት ሀገርንና ህዝብን ለመታደግ የሚል አላማአንግበው ወደ ውትድርና የገቡት::

እኒህ ሰው ሻለቃ ሀይለየሱስ እጅጉ ይባላሉ:: ብዙ የሀገር አውራወች ከበቀሉበት ደቡብ ጎንደር ነው ትውልዳቸው:: የያኔው የ1950ዎቹ ወጣት ሀይለየሱስ ፈጣንና ቀልጣፋ ነበሩ:: በልጅነታቸው ከእኩዮቻቸው ጋር ሲጫወቱ ሮጦ የሚቀድማቸው: ታግሎ የሚጥላቸው አልነበረም:: ሽንፈትን አይወዱም: እናይታገላሉ ታግለውም ያሸንፋሉ:: በዚያን ወቅት የነበረው ይህ ለጥቃት ያለመንበርከክ ስሜት: ከራሳቸው አልፈው ለህዝብና ለሀገር እንዲሰለፉ አስገደዳቸውና ትምህርታቸውን አቋርጠው ወደውትድርናው ገቡ:: በተራ ውትድርና ለአመታት ካገለገሉ በኋላ ለምክትል መቶ አለቅነት ተወዳድረው ከጓደኞቻቸውየተሻለ ውጤት አምጥተው በማለፋቸው ሆለታ የመኮንኖች ማሰልጠኛ ተቋም ገብተው በምክትል መቶ አለቅነት ተመረቁ::

የምክትል መቶ አለቅነት ማእረግ ካገኙ በኋላ በተለያዩ የጦር አውድማወች ከጓድ መሪነት እስከሻምበል አዛዥነት አገልግለዋል:: ያን ያገጠጠ የኤርትራ ተራራ እንደዝንጀሮ እየቧጠጡ በመውጣት ሻቢያንና ጀብሀን እያሳደዱ አይቀጡ ቅጣት ቀጥተዋል:: ወታደሮቻቸው በበሰለ አመራራቸውና ወታደራዊስልታቸው ያደንቋቸዋል:: ለሀገርና ለወገን ባላቸው ፍቅር ያከብሯቸዋል: በጀግንነታቸው ይመኩባቸዋል:: ዘመድ ወዳጆቻቸው እንዲሁም ጓደኞቻቸው ይኮሩባቸዋል:: የኤርትራን ደጋና ቆላ መሬቶች ጀብሀንና ሻቢያን ሲያሳድዱ ረጋግጠውታል:: ከተሰነይ እስከናቅፋ: ከአከለጉዘይ እስከምጽዋ ቆንጥሩንእየመነጠሩ አሜካላውን እየጠረጉ: ረሀብና ጥምን ተቋቁመው ድካም ሳያዝላቸው ተመላልሰውበታል:: በተደጋጋሚ በደረሰባቸው የመቁሰል አደጋ ምክንያት በምድር ጦር መምሪያ ውስጥ እንዲሰሩ ሲደረግ ደስተኛ አልነበሩም:: እኒያ በኤርትራ መሬቶች ከጠላት ጋር አንገት ለአንገት እየተናነቁ ጥለውየሚወድቁት የትግል አጋሮቻቸው ሁኔታ በምናባቸው እየታያቸው ወደዚያው ሂድ ሂድ የሚል ስሜት ይተናነቃቸዋል:: ግን ምንም ማድረግ አልቻሉም: የበላይ ውሳኔ ነዋ!

የኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ጸር የሆነው ወያኔ መራሹ ኢህአዴግ ስልጣን ሲቆጣጠር ሻለቃ ሀይለየሱስ ለተሀድሶ ከጓደኞቻቸው ጋር ወደጦላይ ተወሰዱ:: በጦላይ ቆይታቸው ብዙ አሳዛኝና አሳፋሪ ድርጊቶች አይተዋል:: በአንድ ወቅት አንቱ ተብሎ ይፈራና ይከበር የነበረ የጦር መሪ ባልሰለጠነ የዘር ሰራዊትከፍ ዝቅ ሲደረግ ማየትና መስማት ከምንም በላይ ያማል:: እንዳይቻል የለምና ይህም ታለፈና ሀይለየሱስ ከማጎሪያ ካምፑ ተሰናብተው ወያኔ ባስቀመጠው የእድሜ ገደብ ተጠቅመው የጡረታ መብታቸውን አስከብረው ኑሯቸውን ከአዲስ አበባ ወደባህርዳር አዙረው ቤት ሰርተው ልጆቻቸውን እያሳደጉመኖር ጀመሩ:: ወቅቱ እንዲህ እንዳሁኑ አልከፋም ነበርና ሻለቃው በጡረታ በሚያገኙት 400 ብር የማይሞላ ገንዘብ ልጆቻቸውን ለማሳደግ ብዙም አልቸገራቸውም::
ይህ በእንዲህ እንዳለ የወያኔ የጫካ ፖሊሲ በከፋ መልኩ መተግበር ጀመረ:: “አማራ የትግራይ ጠላት ነው:: አማራ መጥፋት አለበት” ብለው ወያኔዎች በመተዳደሪያ ደንባቸው ያስቀመጡትን ፖሊሲ በተግባር መተርጎም ጀመሩ:: አማሮች ቡና ለቅመው: እህል ሰብስበው: ወይም በማንኛውም የጉልበት ስራተሰማርተው ያገኟትን ጥሪት ለዘመመ ጎጇቸው ማቃኛ ለኑሮ መደጎሚያ ለማድረግ እግር ወደመራቸው አሊያም ስራ ይገኛል ብለው ተስፋ ወደአደረጉበት አካባቢ እንደሄዱ ሳይመለሱ በዚያው ወድቀው ቀሩ:: ነፍጠኛ መጣብህ እየተባሉ ብሄር ብሄረሰቦች እየተቀሰቀሱ በየአካባቢው አማሮች እየታደኑእንዲገደሉ ተደረገ:: አንገታቸው ተቆረጠ ሆዳቸው በሳንጃና በገጀራ ተቀደደ:: በደህናው ጊዜ ሁሉም አገሬ ብለው ከቦታ ቦታ መርጠው ለጤናቸው ወይም ለስራቸው የሚስማማ ነው ብለው ባመኑበት የሀገሪቱ ክፍል ካካባቢው ህዝብ ጋር ተዋልደውና ተስማምተው የኖሩት አማሮችና የአማራ ዝርያያለባቸው ሰዎች ሁሉ ይህ ቀረ የማይባል ግፍ ተፈጸመባቸው:: ም/ጠ/ ሚኒስትር የነበረው ታምራት ላይኔ በጅጅጋ ተገኝቶ ‘እዚህ ያሉት አማሮች ሊገዟችሁ: ሊዘርፏችሁ: ሊገድሏችሁ የመጡ ናቸው:: ለምን ዝም ብላችሁ ታይዋቸዋላችሁ:: ዱላው በእጃችሁ ጠላቶቻችሁ በደጃችሁ’ አይነት ንግግር አደረገናየአማሮችን የስቃይ ደረጃ በእጅጉ አናረው:: በአሶሳ: በወተር: በበደኖ (የየአካባቢውን ሰለባ እግዜር ይቁጠረው) አማሮች ከነነፍሳቸው በገደል ተጣሉ: እንደበግ ታረዱ:: አዛውንቶች: ህጻናት: ወንዶች ሴቶች: ሁሉም ተረሸኑ:: አማራነት ብቻውን ለሞት ዳረገ:: አቅም ያገኙ ሀብት ንብረታቸውን ሳይይዙነፍሳቸውን ለማትረፍ የተወለዱበትና ያደጉበትን: ሀብት ንብረት አፍርተው ይኖሩ የነበረበትን አካባቢ ጥለው ባዶ እጃቸውን ተሰደዱ:: ‘አማሮች ወደመጡበት ሲመለሱ ምንም ነገር እንዳያንጠለጥሉ:: ባዶ እጃቸውን ነው የመጡት: መመለስ ያለባቸውም ባዶ እጃቸውን ነው:: ቤታቸውን: ድርጅታቸውንእንዳትገዟቸው:: ምን ያደርጉታል:: ይዘውት አይሄዱ ተብሎ በየሰፈር ተሿሚወች እንዲለፈፍ ተደረገና አማሮች ባዶ እጃቸውን ‘በለው በለው’ እየተባሉ የወደቁት ወድቀው የተረፉት እንዲሰደዱ ተደረገ::

ኢትዮጵያ የምትባለዋ ሀገር ታሪክና ስም የሚያንገሸግሻቸው ወያኔወች ኢትዮጵያን ለማጥፋት በቅድሚያ አማራውን ማጥፋት ብለው ወስነው የጥፋት ዘመቻውን አጧጧፉት:: አማሮች በየቦታው የጣእር ድምጽ አሰሙ:: በረጅም ዘመን የሞት የሽረት ትንቅንቅ ያቆያትን: በጥቁሮች ታሪክ ያልታየ ገድል ፈጽሞ ከነጮች ጋር ድንበር ተካሎ በደምና በአጥንቱ መሰረት የገነባትን ኢትዮጵያን ያወረሰ ኩሩ ኢትዮጵያዊ እየታደነ ታረደ:: ለደርቡሾች: ለግብጾች: ለቱርኮች: ለሶማሊያወች: ለጣሊያኖችና ለእንግሊዞች ያልታጠፈ ክንድ በገዛ ልጆቹ ዛለ:: የወራት የእግር መንገድ እየተጓዘ ደረቅ ዳቦቆሎና እንጎቻ እየገመጠ በዚያመንገድ ባልነበረበት ዘመን እባቡ እየነደፈው: ወባው እየጣለው: የዱር አውሬው እያጠቃው: ይኸ ሁሉ የሚያጎድልበት ሳይበግረው ረሀብና ጥሙን ችሎ በጦር በጎራዴ ከዳር ዳር እየዞረ: የሀገር ትርጉም ቀደም ብሎ ገብቶት ‘እኔ ለሀገሬ’ ብሎ ከጠላት ጋር ተናንቆ በደምና በአጥንቱ አስከብሮ ባቆያት ኢትዮጵያላይ የተቀመጡ የጊዜው ሰዎች የዚያን አንበሳ ኢትዮጵያዊ ልጆች እየለቀሙ በመፍጀት ውለታውን ከፈሉ:: ከኢትዮጵያዊነት ደረጃው ዝቅ ብሎ የማያውቀው አማራ ሀገሬ እንዳለ የሀገር ትርጉም ባልገባቸው ርጉም ልጆቹ ሀገሩን አጣ:: ‘የአማራው ሀገር የት ይሆን?’ ሲልም ጠየቀ:: አማራ ተብለው በብአዴን ስርየተሰባሰቡ ከንቱወች ‘ከክልላቸው የወጡት አማሮች ጉዳይ አይመለከተንም’ አሉ:: በዚህ ጊዜ ነበር ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ እያለ የሚወተውተውን አማራ ‘እስቲ መጀመሪያ ለራሳችን እንሁን- እያጠፉንኮ ነው’ በሚል መልክ እንደራጅ ብለው ጥቂት መሰሎቻቸውን ይዘውመዐሕድን የመሰረቱ::

ሻለቃ ሐይለየሱስ እጅጉ ጡረታ የወጡት ከትግል አይደለም:: በዚያም ላይ እየተጠቃ ያለው ወገናቸውና በደም እየታጠበች ያለች ሀገራቸው ጉዳይ ሰላም ነስቷቸዋል:: እናም የወያኔን ወደስልጣን መምጣት ተከትሎ ጠበንጃቸውን የሰቀሉት ሻለቃ ጠበንጃቸውን አውርደው ና ወልውለው በሚያውቁበትናወያኔን በሚገባው መንገድ ሊያነጋግሩ አልፈቀዱም:: የአለም ሁኔታ ለእንደዚህ አይነት ትግል አመች አይደለም:: ወያኔና ሻእቢያ ደርግን አሸንፈው ስልጣን እንዳልነጠቁ አሳምረው ያውቃሉ:: ‘ኢምፔሪያሊዝም ይውደም’ እያሉ የሰው ምስል ቀርጸው በእሳት ሲያቃጥሉ የነበሩትን ደርጎች ለመበቀል: በምትኩምየራሷን ተላላኪወች ለማንገስ አሜሪካ በነደፈችው መርሀ ግብር መሰረት የጦር ጀኔራሎች እንዳያዋጉ በተለያየ ነገር በመደለል ውጊያውን እንዳበላሹትና ሁሉም ነገር በወያኔና በሻእቢያ የበላይነት እንዲደመደም እንዳደረጉ ያውቃሉ:: የኢትዮጵያ ጦር ‘ይህንን ቦታ አጥቅተህ ያዝ’ ይባላል:: ጦሩ የተባለውን ቦታአጥቅቶ ሲይዝ ምክንያቱን በማያውቀው ሁኔታ ወደኋላ አፈግፍግ ይባልና እንደገና ሌላ ትእዛዝ ይመጣበታል:: በዚህም ምክንያት በስንት መስዋእትነት የያዘውን ምሽግ እንደቀላል ነገር ለቆ እንዲመለስ ይደረጋል:: ብዙም ሳይቆይ ‘ተለዋጭ ትእዛዝ’ ተብሎ አጥቅተህ ይዘኸው የነበረውን ምሽግ በአፋጣኝመልሰህ በእጅህ አድርግ ይባላል:: ይህ ሲሆን ግን የሻእቢያ ጦር በውጊያ ተሸንፎ ለቆት የነበረውን ምሽግ ቀድሞ እንዲገባበት ተደርጎ ነው:: ከጠላት ማስለቀቁን እንጅ ተመልሶ በጠላት እጅ መውደቁን ያልጠረጠረው የኢትዮጵያ ሰራዊት ወደምሽጉ ሲመለስ የመሸገው የጠላት ጦር በሩምታ ተኩስ ይቀበለዋል-በዚህ አይነት የተበላሸ አመራር የሰራዊቱን የውጊያ ፍላጎት አሟጠው አጠፉት:: ይህን ሀይለየሱስ ጠንቅቀው ያውቃሉ:: ሶሻሊስት ርእዮተአለምን ይከተሉ የነበሩ ሀገሮች ሁሉ እጣ ፈንታ ይኸው ሆኗል:: የሶቭየት ህብረትን መፈራረስ ተከትሎ ‘ኢምፔሪያሊዝም ይውደም’ እያሉ ኢምፔሪያሊዝምን ይወክላልብለው ሆዱ የተንዘረጠጠ: ጥርሱ ያገጠጠ: የዶላር ምልክት በተነፋ ሆዱ ላይ የተለጠፈበት የካርቶን ስእል እየሰሩ ሲያቃጥሉና ኢምፔሪያሊዝምን ያጠፉ ያህል በደስታ ሲቃ በእሳቱ ዙሪያ ክብ እየሰሩ ሲጨፍሩ የነበሩትን ሶሻሊስቶች አሜሪካ በአካል ተበቀለቻቸው- ብትንትናቸውን አወጣቻቸው- ሀገራቸውንጭምር:: የኢትዮጵያም ታሪክ ያው ይህንን የተከተለ ነው:: ይህ ለሀይለየሱስ እንግዳ ነገር አይደለም:: ሶሻሊዝም እንደስርአት ካከተመ በኋላ ሁሉም ነገር በአሜሪካ በጎ ፈቃድ ስር ወደቀ:: ወዲያ ወዲህ ማለት አልተቻለም:: ችግር አለብኝ የሚል ወገን ሁሉ በሰላማዊ ሰልፍ የአሜሪካና የአውሮፓ ሀገሮችኤምባሲወች ባሉባቸው ከተሞች ‘እግዚኦ’ ብሎ በደልን ማሰማት ብቸኛ አማራጭ ሆነ:: በስሜት ተነሳስቶ ‘ዘራፍ’ ብሎ ጫካ የሚገባ ሰው ቢኖርም ትርጉም የለውም:: የያዘውን ጥይት አስጨርሰው ካስተኮሱ በኋላ በዱላ አባሮ መያዝ ይቻላል:: ውጊያ ለመጀመር የሎጀስቲክስ ተከታታይ አቅርቦት: የስልጠናናየቴክኒክ እርዳታ: የመረጃና የነጻ መሬት መኖር ወሳኝ ነው:: ያንን ማግኘት እጅግ ከባድ ነው:: አንደኛ ወያኔ ማንኛውንም የኢትዮጵያ ጥቅም አሳልፎ በመስጠት ከበፊት የኢትዮጵያ መሪወች ሁሉ በተለየ ለጎረቤት ሀገሮች ተመችቷል:: ሁለተኛ ወያኔ የአሜሪካ ተላላኪ በመሆኑ ሁለንተናዊ ድጋፍ ይደረግለታል-መረጃን ጨምሮ:: ስለዚህ የተሻለው መንገድ በደልን በእግዚኦታ ማሰማት ነው:: ይህንን የተረዱት ሻለቃ የአማራውን ጩኸት ለመጮህ መዐሕድን ተቀላቀሉ::

ይቀጥላል

4 Comments

  1. ይገርማል፣ ፅሁፍህ በጣም አሪፍ ነው። በተለይም የውጭ ሀይሎችን ሚና ከትናንት እስከዛሬ የተነተንክበት መንገድ አርክቶኛል። ዛሬ የምዕራቡ አለም ወያኔን የሚያንቆለጳጵሱበት ቃላት አጥተው ሲቸገሩ የምናያቸው፣ መለስ በሕይወት በነበረበት ዘመን ከፍተኛ ትኩረት ይሰጡት የነበረው፣ አሁን ካሉት ርዝራዦች ጋር አሸሸ ገዳሜ ሲሉም የምናያቸው፣ ሀገሪቱ ላይ ላላቸው የአንድዮሽ ጥቅም እንደወያኔ ካለ ለሀገሩ ቅንጣት ታክል ፍቅር ከሌለው የባንዳዎች ስብስብ የተሻለ ሊያገኙ እንደማይችሉ ስለሚያወቁ ብቻ ነው። መጀመሪያም ስልጣን ላይ ለመውጣት የበቁት ከዚያም ይህን ያህል ዘመን ስልጣን ላይ መቆየት የቻሉት የአሜሪካና የጥቅም አጋሮቿ ድጋፍ ስላልተለያቸው ነው። የሚያሳዝነው ግን አብዛኛው ሀበሻ ይህን የምዕራቡ ዓለም ሴራ አለመረዳቱ ነው።

  2. ይገርማል አንድ ያልተመቸኝ ነገር አለ::በሰላማዊ መንገድ ወያኔን መሞከር ማለት ከግንብ ጋር መጋጨት ነው የሚሆነው::እንዳልከው በተለያየ መንገድ የተለያዩ ነገሮች እጥረት ሊያጋጥም ይችላል::የሁሉንም ምንጭ ራሱን ወያኔን ማድረግ ይቻላል::በዘረኝነት ያልተንካካ በር የለም::ወታደሩም ፖሊሱም በዘረኝነት ተማርዋል::በነዚህ ክፍሎች ደግሞ ሰማይ ነክትዋል::መስዋዕትነት የሚፈራ ታጋይ ቤቱ ይቀመጥ::

Comments are closed.

habtamu
Previous Story

Hiber Radio: የስዬ አብርሃ ወንድም ዳግም በሙስና ታሰረ

EYNM New Logo
Next Story

የኢትዮጵያ ወጣቶች ብሄራዊ ንቅናቄ የሰማያዊ ፓርቲን የሰላማዊ ሰልፍ ጥሪ ደገፈ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop