May 12, 2013
12 mins read

የ2012/2013 የእንግሊዝ ፕሪምየር ሊግ አስሩ መጥፎ የተጫዋች ዝውውሮች

piremier legue

ከይርጋ አበበ
በ2012 ክረምት የተጫዋቾች ይዝውውር መስኮት ከተከናወኑ ዝውውሮች መካከል ለአዲሱ ክለባቸው ተገቢውን አገልግሎት መስጠት ያልቻሉትን አስር ተጫዋቾች የእንግሊዙ ዘሰን ጋዜጣ ለአንባቢያን አቅርቧል። እኛም ይህንኑ ለአንባቢያን በሚመች መልኩ አሰናድተን አቅርበናል ።
1. ክርስቶፎር ሳምባ (ከአንዚማካቻክላ ወደ ኪው ፒ አር 12ነጥብ5 ሚሊዮን ፓውንድ)
ብላክ በርን ሮቨርስ ወደ ታችኛው ሊግ መውረዱን ተከትሎ ወደ ምስራቅ አውሮፓው ሀብታም ክለብ የሩሲያው አንዚ ማካቻክላ የስድስት ወር ጊዜ ቆይታ ያደረገውን የኮንጎ ብሄራዊ ቡድን አምበል ሳምባ በጥር ወር የተጫዋቾች ዝውውር ነበር ከለንደኑ ክለብ ጋር የፈረመው። የመውረድ ስጋት ፊቱ ላይ የተደቀነበት ኪው ፒ አር አሰልጣኙን ሲቀይር እግረ መንገዱን ተጫዋች ግዥ ፈፅሞ ነበር። ክልባችንን ይታደግልናል ብለው ያሰቡት አፍሪካዊ ተከላካይ የታሰበውን ያህል መስራት ሳይችል ክለቡንም ከመውረድ ሳይታደግ በመቅረቱ የዓመቱ ቀጥር አንድ መጥፎ ግዥ ለመባል የቀደመው አልተገኘም ።
2. ጃቢ ጋርሽያ ( ከቤነፊካ ወደ ማንቸስተር ሲቲ 16 ሚሊዮን ፓውንድ)
ጉልበተኛው ነይጂል ዲዮንግ ወደ ጣሊያኑ ታላቅ ክለብ ኤሲ ሚላን መሰደዱን ተከትሎ ወደ ሀብታሙ ክለብ ዝውውር ያደረገው የቤኒፊካ ተጫዋች ሌላኛው ያልተሳካ ዝውውር ተብሏል። ከፖርቹጋሉ ታላቅ ክለብ ወደ ሀብታሙ የማንቸስተር ክለብ ሲዘዋወር በያያ ቱሬ እና እንግሊዛዊው ጋሬት ባሊ የተያዘውን የሰማያዊዎቹን የመሃል ሜዳ ክፍል የግሉ ለማድረግ ከባድ ፈተና የገጠመው ጋርሺያ ለ22 ጊዜያት ብቻ ለሰማያዊዎቹ መጫወት የቻለ ቢሆንም በነዚህ ጨዋታዎቹ የደጋፊዎቹን ፍላጎት ማሟላት ባለመቻሉ የሳምባን እግር ተከትሎ የመጥፎ ዝውውሮችን የፊት መስመር ሊቆጣጠር ችሏል።
3.ጆ አለን(ከስዋንሲ ሲቲ ወደ ሊቨርፑል 15 ሚሊዮን ፓውንድ)
ዌልሳዊው ኮከብ በ2011/12ለብሬንዳን ሮጀርስ ቡድን ቁልፍ ሰው ነበር። ይህንን ችሎታውን የተገነዘቡት አየርላንዳዊው አሰልጣኝ ከስዋንሲ ወደ ሊቨርፑል ሲዘዋወሩ ጆንም አብሯቸው እንዲጓዝ የ15 ሚሊዮን ፓውንድ ቼክ ከአሜሪካውያኑ የሊቨርፑል ባለቤቶች አስከፍለው ነበር ያዘዋወሩት። ጅማሬው ጥሩ የነበረው ዌልሳዊ ኮከብ ውድድሩ ወደ ወሳኝ ምዕራፍ ሲሸጋገር ብቃቱን ጠብቆ አለመዝለቁ ሌላኛው ያከሰረ ተጫዋች የሚል ስያሜን ዘሰን ሰጥቶታል።
4.ማርኮ ማሪን ( ከቬርደር ብሬመን ወደ ቸልሲ 6 ሚሊዮን ፓውንድ)
ጀርመናዊው ጥበበኛ ወጣት ችሎታውን ማንም አይጠራጠርም። ነገር ግን እሱ ሮማን አብራሞቪቹ ክለብ ከመፈረሙ በፊት የፈረሙት ኦስካር እና ኤዲን ሃዛርድ ከሁዋን ማታ ጋር የፈጠሩትን የተዋጣለት ጥምረት ሰብሮ መግባት ባለመቻሉ የመጥፎ ዝውውሮችን ስም ዝርዝር ከያዘው የዘሰን ማስታወሻ ላይ የሱም ስም ከሶስት ተጫዋቾች ቀጥሎ በአራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
5. ኢማኑኤል አዲባዬር (ከማንቸስተር ሲቲ ወደ ቶተንሃም ሆትስፐርስ 5 ሚሊዮን ፓውንድ)
በማንቸስተር ሲቲ እና ሪያል ማድሪድ ከተንከራተተ በኋላ በቶተንሃምም አንድ የውድድር አመት የተሳካ የውሰት ውል ያሳለፈው ማኑ በቋሚነት ለኋይት ሃርትሌኑ ክለብ ሲፈርምም የመጀመሪያ አመት ብቃቱን እንዲደግም በማሰብ ነበር። ነገር ግን የሃሪ ሬድናፕን መሰናበት ተከትሎ ክለቡን የተረከቡት አንድሬ ቪያስ ቦአስ ለቀድሞው የአርሴናል ተጫዋች የሚመች የአጨዋወት ፍልስፍና ይዘው አለመምጣታቸው አዴ ለተቀያሪነት ተዳረገ። ዕድሉን አግኝቶ በተሰለፈባቸው ጨዋታዎች ጥሩ ግልጋሎትን ቢሰጥም ብዙ ጊዜ አለመሰለፉ እንደ ድክመት ተቆጥሮ አምስተኛው መጥፎ ዝውውር ከመሆን አላዳነውም።
6.ዳኒ ግርሃም(ከስዋንሲ ሲቲ ወደ ሰንደርላንድ 5 ሚሊዮን ፓውንድ)
አሜሪካዊው አጥቂ በስዋንሲ ቆይታው የግብ ሪከርዱ ጥሩ የሚባል ነበር። ነገር ግን ዴንማርካዊው ቴክኒሽያን ብሬንዳን ሮጀርስን ተክተው ክለቡን ሲረከቡ ከስፔን የገዙት ሚጉኤል ሚቹ ዳኒን ወደ ተጠባበቂ ወንበር እንዲያወርደው ተደረገ። 90 ደቂቃ ሙሉ ተቀያሪ ወንበር ላይ መቀመጥ ያልተመቸው ግርሃም ወደ ጥቋቁር ድመቶቹ በጃንዋሪ የዝውውር ወቅት ይሄዳል ። በሰንደርላንድ የመሰለፍ እድል ቢያገኝም የግቡን መስመር ማግኘት አለመቻሉ መጥፎ የግብ ሪከርዱ ያልተሳካለት ተዘዋዋሪ እንዲሆን አድርጎታል።
7. እስቴባን ግራኔሮ ( ከሪያል ማድሪድ ወደ ኪው ፒ አር 9ሚሊዮን ፓውንድ)
የቀድሞው የብላክ በርን እና ማን ሲቲ አሰልጣኝ የነበረው ዌልሳዊው ማርክ ሂውዝ በሪያል ማድሪድ የተሰላፊነት ዕድል በማጣቱ የተሰላቸውን ስፔናዊ 9 ሚሊዮን ፓውንድ ክፍያ ከፍለው ወደ ለንደን ያመጡት ታላቅ ተስፋ ሰንቀው ነበር። ዳሩ ግን ክለቡም ሆነ ግራኔሮ የኋልዮሽ በመጓዛቸው በአመቱ መጨረሻ ክለቡ ወደ ታችኛው ዲቪዚዮን ልጁ ደግሞ የአመቱ ሰባተኛው ደካማ ዝውውር ለመባል ቻሉ።
8. አሉ ዲያራ ( ከኦሎምፒክ ማርሴይ ወደ ዌስትሃም ዩናይትድ 2 ሚሊዮን ፓውንድ)
አወዛጋቢውን እንግሊዛዊ አማካይ ጆይ ባርተን ከኪው ፒ አር በውስት ያገኘው የፈረንሳዩ ክለብ ጠንካራውን አማካዩን ለዌስትሃም ሲሰጥ የቋሚ ተሰላፊነት ቦታውን እንደማያገኝ አስቦ አልነበረም። ነገር ግን ዲያራ በለንደን የጠበቀው ያልታሰበው ሆነ። እሱም የመዶሻዎቹ አሰልጣኝ ሳም አላርዳይስ ከአሉ ዲያራ ይልቅ ሴኔጋላዊውን ዲያሚን በማስቀደማቸው ተጠባባቂ መሆን የሰለቸው ፈረንሳዊው በጥር ወር ወደ ፈረንሳይ ተመልሶ ለትውልድ ከተማው ክለብ ሬን ፊርማውን አኖረ።
9.ስኮት ሲንክሌር ( ከስዋንሲ ሲቲ ወደ ማን ሲቲ6 ሚሊዮን ፓውንድ)
በዚህ ስም ዝርዝር ውስጥ የሚበልጠውን ድርሻ የያዙት የቀድሞ የስዋነሲ ሲቲ ተጫዋች እንደሆኑ የቀድሞው የቼልሲ ተጫዋች ስኮት ሲንክሌር አስተዋጽኦ አድርጓል። ስኮት በቼልሲ የተደበቀውን ችሎታውን በዌልሱ ክለብ መልሶ ማግኘት ቢችልም ወደ ማንቸስተር ሲቲ ያደረገው ዝውውር ራስን ከተራራ ላይ ወደ መሬት እንደ መወርወር ያስቆጠረውን ስህተት የፈጸመበት ነበር። በሮቤርቶ ማንቺኒ ቡድን ውስጥ እንደ ሳሚር ናስሪ፣ ዴቪድ ሲልቫ እና ጄምስ ሚልነር ዓይነት ኮከብ ተጫዋቾች መኖራቸው የተጠባባቂ ወንበርን በመደበኛነት እንዲያዘወትር አድርጎታል።
10. ማይኮን ( ከኢንተር ሚላን ወደ ማን ሲቲ 3 ሚሊዮን ፓውንድ)
ማንቸስተር ሲቲ ያለፈውን የዝውውር መስኮት ብዙ የከሰሩ ዝውውሮችን የፈፀመ ክለብ ሆኗል። በኢንተር ሚላን ጉልበቱን የጨረሰውን ብራዚላዊ በዝቅተኛ ዝውውር ሰማያዊውን ማሊያ ማልበስ ቢችልም ያሰበውን ግልጋሎት ማግኘት ሳይችል ቀርቷል። በብራዚል ብሄራዊ ቡድን ውስጥ ቦታውን በባርሴሎናው ኮከብ ዳኒ አልቬስ የተወረሰው ግዙፉ ብራዚላዊ በእንግሊዝም የጠበቀው ከብራዚል የተለየ አልነበረም። ያለፉትን ሁለት ዓመታት በጥሩ አቋም ላይ ያሳለፈው አርጀንቲናዊ ፓብሎ ዛባሌታ ቦታውን የግሉ አድርጎት ስለነበር ከዛባሌታ ቀድሞ መሰለፍ ለማይኮን የሚቻል አልሆነለትም። እናም ዓመቱን ሙሉ ተጠባባቂ ወንበር ላይ ተቀምጦ የዛባሌታን ምርጥ እንቅስቃሴ ሲመለከት ከረመ። ከእንግሊዛዊው ሚካህ ሪቻርድስ መጎዳት በኋላ ማንም እንዳይቀማው አድርጎ ቦታውን ያስከበረው አርጀንቲናዊ ረፍት ሲያስፈልገው ብቻ በካፒታል ዋን ጨዋታዎች የሚሰለፈው ብራዚላዊ አንድ ያልተሳካ የውድድር ዓመት በእንግሊዝ ሲሰልፍ ዘሰን ጋዜጣም አስረኛው ያልተሳካለት የዓመቱ ፈራሚ የሚል ስም ሰጥቶታል።

Previous Story

ተገፊዎች የባህሪ ለውጥ ኣምጡ እንጂ! ከገለታው ዘለቀ

ካዬላ ዊህለር
Next Story

ሁለት እግርና አንድ እጅ አልባዋ የዋና ሻምፒዮን

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop