ለምንገኝበት እጅግ መሪርና አስከፊ እውነታ ተገቢውን ትኩረት እየሰጠን ካልተራመድን …

T.G

September 21, 2023

ማነኛውም ሰው ዘመን ያፈራውን የማህበራዊ መገናኛ ዘዴ በመጠቀም ከገሃዱ ዓለም አንፃር የሚታዘበውንና የሚረዳውን ጉዳይ ለህዝብ በማቅረብ እና ጠቀሚታ እንዲኖረው በማድረግ የድካሙን ዋጋ የማግኘቱ (የመጠየቁ) ተገቢነት አያጠያይቅም።

በዚህ ተጠቃሚ የሆነ ወይም የሚሆን ህብረተሰብም (ትውልድም) ይህንን መልካም አስተዋፅኦ ሰምቶና ታዝቦ የጊዜያዊ ስሜቱ ማርኪያ (amusement) ማድረግ ሳይሆን ይበልጥ እያዳበረ የሁለንተናዊ ሰብእናውና ደስታው (real sense of humanity and happiness) መሠረትና ዋልታ ሊያደርገው ይገባል።

በአሁኑ ጊዜ እየታዘብነው ያለነው ግን ይህንን አይነት አስተሳሰብና አካሄድ ሳይሆን በመሬት ላይ እየሆነ ያለውን እጅግ መሪርና አደገኛ የትውልድ ቀውስ እየሸሹ በየአዳራሹ፣ በየአደባባዩና በየሚዲያው የሚደረግን አያሌ ሚሊዮኖች ተከታዮችን (ያውም ከአድናቆት በስተቀር የራሳቸውን ነፃና ሚዛናዊ ህሊና ተጠቅመው ሂሳዊና ገንቢ አስተያየት የሌላቸውን ወገኖች) ለማፍራት የሚካሄድ “የታዋቂነት” ተውኔትን ነው።

በዚህ ረገድ ተጠቃሽ ከሆኑት የዚህ ትውልድ አባላት አንዱ የዶንኪ ቲዩቡ እሸቱ ነው። በተወሰነ ተሰጥኦና ችሎታ የህዝብ እውቅና ማግኘት በሁሉም ነገር አዋቂ መሆን ማለት እንደሆነ አድርጎ ከመቀበልና ከማስተጋባት በሚመነጭ እጅግ ደካማ ወይም እጅግ የተንጋደደ አስተሳሰባችን ምክንያት እሸቱና መሰሎቹ ለምንና እንዴት ተደፈሩ በሚል አካኪ ዘራፍ የሚሉ ወገኖች እንደሚኖሩ በሚገባ እረዳለሁና አይገርመኝም።

እሸቱን በሚዲያው ላይ በሚያቀርባቸው ማህበረሰባዊ ጉዳዮችን እና ሃይማኖታዊ እምነትን (ገዳማትን) በሚመለከቱ ዝግጅቶች እንጅ በአካል ወይም በሌላ አጋጣሚ አላውቀውምና ከግሉ ምንነት፣ ማንነት፣ ባህሪ፣ ህይወት፣ እምነት፣ አስተሳሰብ፣ ወዘተ ጋር ፈፅሞ ጉዳይ የለኝም።

አስተያየቴ ፖለቲካ ወለድ ከሆነው የዘመናት መከራና ፍዳ የመውጫ በር አጥቶ የመቃብር እና የቁም ሞት ሰለባ በሆነ ህዝብ መካከል እየኖሩ ምንም እንዳልተፈጠረ በሚያስመስል ሁኔታ በየአደባባዩ፣በየአዳራሹና፣ በየቤተ እምነቱ (በየገዳሙ) እና በየሶሻል ሚዲያው ድንቅ፣ አስገራሚ፣ ተአምረኛ፣ አስቂኝ፣ አዝናኝ፣ አስተማሪ፣ ሰማዕት፣ ቅዱሰ ቅዱሳን፣ ጥዑመ ልሳን፣ ፍኖተ ፅድቅ፣ ትንቢተ ፅድቅ ፣ ወዘተ በሚል በራስ ዓለም ውስጥ መሸሸግ ቢያንስ ከሞራላዊ እሴት አንፃር ፈፅሞ ትክክል አይደለም ከሚለው መሠረታዊ እሳቤና እምነት የሚነሳ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የቹ ግዛት ዝንጀሮዎችና አዲስ አበባ — ፊልጶስ

በየአዳራሹና በየአደባባዩ አጨብጭቦ፣ እልልታውን አቅልቶ፣ በአግራሞት ተደምሞ፣ ወዘተ ሲወጣ ምን ተማርክበት? ከነማን ተማርክ? ለምንና እንዴት ተማርክ? የምትኖርበትን ገሃዱ ዓለምክንና የአዳራሽ ውስጥ/ የአደባባይ ላይ አድናቆትክንና ፈንጠዝያህን እንዴት አነፃፀርከው?  ምንስ ልታደርግና ልትሆን አስበሃል? ወዘተ ተብሎ ሲጠየቅ ያንኑ የአዳራሽ ውስጥና የአደባባይ ላይ ስሜታዊነት የተጫነው እርሱነቱን መልሶ የሚተርክ ትውልድ ፈፅሞ የትም ፎቀቅ ለማለት አይቻለውም።

የዚህ ዘመን ወጣት ትውልድ የአገሩ ህዝብ በዘመን ጠገቡና ከአምስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ በባለጌና ጨካኝ ገዥ ቡድን አገዛዝ ምክንያት  ሰብአዊ ማንነቱና ክብሩ  መግለፅ በሚያስቸግር ሁለንተናዊ መከራና ውርደት ውስጥ በሚገኝበት በዚህ እጅግ አስከፊና አስፈሪ ወቅት ምንም እንዳልተፈጠረ  ወይም አገር በሰላም ውሎ በሰላም እንደሚያድር እና የእነርሱን የመድረክ ላይ ተውኔት በጉጉት እየጠበቀ “ዘመነ ፍስሃን” ማጣጣም እንደሚኖርበት  ሊነግሩትና ሊያሳምኑት የሚሞክሩ አባላቱን ቢያንስ አደብ ግዙ ሊላቸው ይገባል።  

በሰላም ተወልደው፣ አድገው፣ ተምረውና ተመራምረው ከራሳቸው ህይወት አልፎ ለአገራቸው (ለህዝባቸው) አያሌ ታላላቅ ሥራዎችን ሊሠሩ የሚችሉ በአያሌ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ህፃናት የፈጣሪ እና የወገን ያለህ እያሉ እጅግ ለመግለፅ የሚከብድ የሰቆቃ ድምፅ (ጩኸት) እና በአያሌ ንፁሃን የደም ጎርፍና የቁም ሞት ዋይታ በተከበበ አዳራሽ ውስጥ  እየተሰየሙ ምንም እንዳልተፈጠረ በሚያስመሰል ሁኔታ በአግባቡ ቢያዙ ከነድንቅነታቸው ሊያድጉ የሚችሉትን  ህፃናት በስሜት፣ በጭብጨባ፣ በእልልታ፣ በመውረግረግ እና በአጠቃላይ ለእነርሱ በማይመጥን የጥያቄና የትርክት ጋጋታ እያጀቡ የማህበራዊ ሚዲያ ንግድ መነገጃ ማድረግ ቢያንስ የሞራል ጎስቋላነት ነውውና ከምር ቆም ብለንና ትንፋሽ ወስደን ማሰብ ይኖርብናል።

ልብ በሉ ወገኖቼ! እንዲህ አይነት ህፃናት ከተገቢው የሙያ እገዛ ጋር ባልተያዙበት ሁኔታ በየአዳራሹ  እየሰየሙና እያሰየሙ በስሜታዊነት ማጨብጨብ፣  እንኳን እነርሱን አ ቂንም እጅግ በሚፈታተን ልክ የሌለው አድናቆት አዳራሹን ማናወጥ፣ በጭብጨባና በእልልታ ከሚቀልጠው አዳራሽ ውጭ ሌላ ዓለም የሌለና የሚኖር እስኪመስላቸው ድረስ ማደናገር፣ ወዘተ በወደፊት የእድገትና የሙሉ ሰብእና አቋማቸውና ቁመናቸው ላይ ሊያሳድር የሚችለውን አላስፈላጊ (አሉታዊ)  ተፅዕኖ (retardation) በእውን ልብ ማለት ያሻልና ልብ ያለው  ወገን ልብ ይበል!!

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአቶ አስገደ ልጆች ምን ወንጀል ሠሩ? (አሕለፎምና የማነ አስገደ) - ከፕ/ር መስፍን ወልደ ማርያም

የትኛውም የሙያ ተሰጥኦና ችሎታ ለዘመናት  የመጣንበትንና ከአምስት ዓመታት ወዲህ ደግሞ እንኳንስ ለማመን ለማሰብም በሚከብድ ሁኔታ ውስጥ የምንገኝበትን እጅግ  መሪርና አስፈሪ ሁኔታ ቢያንስ ግምት ውስጥ የሚያስገባ ካልሆነ  የእሴትነቱ ትርጉም ጎደሎ ነውና ሊያሳስበን ይገባል።

 

2 Comments

  1. በዚህ ሃገራዊ ቀውስ ወቅት በዘሩ ተመርጦ በክፉ የፖለቲካ ትርክት ነፍጠኛው አማራ በሚል ስያሜ ላለፉት 40 አመታት የቀጠለው ዘር ማጥፋት ሰማይ ጥግ በደረሰበት መዝናኛ የሚሉት ፈሊጥ እጅግ ነውርና ሃጢያትም ነው::
    ይህን አስመልክቶ አቡነ አብርሃም የሰጡት ማሳሰቢያ ተከትለው የፈንጠዝያ ፕሮግራም የሰረዙ ከያኒያንና የስፖንሰሩ ኮካኮላን ድርጊት አድንቄያለሁ::
    ኮሜዲያን እሸቱም ብላቴናዎችን በማቅረብ የሚደረገውን ግፍ ካንዴም ሁለቴ ስላቀረበ ወቀሳው አይመለከተውም ይልቅስ ከወያኔ ጀምሮ በክፉዎች አጫፋሪነት ለቀጠለው ለሰይፉ ፋንታሁንና መሰሎቹ ይህ ትችት ቢቀርብ ይሻላል::
    ፓስተር ዲጎኔ ሞረቴው

  2. ፓስተር ዲጎኔ;

    አስተያየተዎን በሚረዱትና በሚያምኑበት መጠንና አይነት ስለገለፁ አመሰግናለሁ ።

    አላስፈላጊ እሰጥ አገባ ውስጥ ለመግባት ሳይሆን ይበልጥ ግልፅ ለማድረግ የሚከተለውን ልበል፥
    አስተያየተዎን በሚረዱትና በሚያምኑበት መጠንና አይነት ስለገለፁ አመሰግናለሁ ።
    1)አዎ! በእኩያን የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ቁማርተኞች ምክንያት መግለፅ የሚያስቸግረው የህዝብ መከራ፣ ሰቆቃ እና በአጠቃላይ ከሰብአዊ ፍጡር በታች መሆን ጨርሶ ሳይገዳቸው በሚዲያ ነጋዴነትና አትራፊነት ከተሠማሩት መካከል ሰይፉ ፋንታን በጣም ግልፅና ቀጥተኛ ማሳያ መሆኑ አጠያያቂ አይደለምና አስተያየት ሰጭው የሰጡትን አስተያየት እጋራለሁ።

    2) በነገራችን ላይ የእነ መሸሻው ኢ.ቢ.ኤስም ከዚሁ አይነት የሸፍጥ ቢዝነስ (hypocritical business) ልክፍት ከቶ ነፃ አይደለም። በየበዓሉ የስጦታ ቁስና ሳንቲም ይዞ መረዳት ላለባቸው በየሰፈሩ እየዞሩ መስጠቱና ለማስታወቂያ የሚሆን ቪዲዮ መቅረፁ በቅንነት ሲታይ ተገቢ መሆኑ እንደ ተጠበቀ ሆኖ ከዚህ አልፎ ግን በርቀት ሳይሆን በዋና ከተማዋ (አ.አ) ዙሪያ በመቶ ሽዎች የሚቆጠሩ ወገኖች ታላቁን የኦሮሙማ ከተማ ለመመሥረት ሲባል ተፈናቅለው በገዛ አገራቸው የምድር ላይ ሲኦል ሰለባ ሲሆኑ አለመጠየቅና ሰቆቃቸውን ለማሳወቅ ወኔ ማጣት ፈፅሞ ከንፁህ ህሊና እና ከመልካም ዜግነት ጋር ጉዳይ የለውም።

    3) አዎ! እሸቱ አንድ ሰሞን ከቁም ነገርነቱ ይልቅ ተችቷቸዋል የምንላቸውን እኩያን ገዥዎች ሳይቀር በሚያስቅ አይነት አቀራረብ በመቅረብ የሚዲያ ላይ ታዋቂነቱን ሚዛናዊ ለማስመሰል ያልተሳካ ሙከራ ማድረጉን በሚገባ አውቃለሁ። እንዲህ አይነቱን በሸፍጥ (hypocrisy) የታጀበ አቀራረብን፣ ዲስኩርንና ትወናንማ በገዥው ቡድን ስብሰባዎችና ጉባኤዎች ወቅትም የምንሰማው ነገር ነው።

    4) እናም የነገሮችን አኳኋንና አካሄድ እየጠበቁ ሚዛናዊ ባለሙያ ወይም ዜጋ ለመምሰል የሚተወን ተውኔት የኢትዮጵያ ህዝብ ለዘመናት ከኖረበትና አሁንም በእጅጉ የባሰ መሪርና አስከፊ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ከሚገኝበት እውነታ አንፃር ጨርሶ እዚህ ግባ የሚባል አይደለምና የሚሻለው አካፋን በአግባቡ አካፋ ማለትና የባለጌና ጨካኝ ገዥዎችን ሥርዓት አስወግዶ ለሁሉም የሚበጅ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እውን ማድረግ ብቻ ነው።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share