ጉዞ ወደ ኢትዮጵያ ትንሣኤ! -nሲና  ዘ ሙሴ

እንኳን ለኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ መታሰቢያ ቀን አደረሳችሁ ። ኢየሱስ ክርስቶስ ህገ አራዊትን አሶግዶ  የኢትዮጵያን ትንሣኤ ያሳየን  ዘንድ ተግተን እንፀልይ ።  በነፃነት ልንኖር ክርስቶስ ነፃነት አወጣን እንግዲህ ፀንታችሁ ቁሙ ። እንደገናም በባርነት ቀንበር አትያዙ ።
( ገላትያ  ምዕራፍ 5 ፤  1 )

ሲና  ዘ ሙሴ

ሰው ፣ ሰውን እንዲጠላ የሚያደርግ አንቀፅ ያለው ህገ መንግሥት ሉሲ ፈራዊ ነው ። አንቀፅ 39 ከህብረት ይልቅ መለየትን ፤ ከአንድነት ይልቅ መበታተንን ፤ ከፍቅር ይልቅ ፀብን የሚያበረታታ ነው ። ምንም እንኳ የሰው ሥብሥብ የሆነው ህዝብ አጭር ህይወቱን በተቻለው አቅም ህብረትን፣አንድነትን ፍቅርን እጅግ ቢፈልግም በእኛ አገር ህገ መንግሥት አልተፈቀደለትም ።

ሰው ከፍጥረቱ ጀምሮ እየተባበረ ፣ እየተፋቀረ ፤ እየተጋባ እና እየተዋለደ ከእንሥሣ የተጠጋ ኑሮ ከመኖር ቀስ፣በቀሰ ወደ ሥልጡን እና በጥበብ የተሞላ ኑሮ መኖር መጀመሩን ከታሪክ እንረዳለን ። ሰው ፣ በጥረቱ እጅግ የሠለጠነ ኑሮ ላይ በጥበቡ ቢደርስም ፣ በእኛ አገር አሁናዊ ሁኔታ የሰው  የእግዚአብሔር ፍጡርነቱ  በገዢዎች የተካደ ሆኗል ። በጥቂት እናውቃለን በሚሉ ሆኖም ሁሉንም ነገር ከዘር ጥቅማቸው አንፃር በሚመለከቱ ፣ ጠመንጃን እንደ ሥልጣን ምንጭ በሚቆጥሩ ግለሰቦች በምትመራው አገራችን ሰዎች የሚታዩት እንደ ሰው ሳይሆን እንደ ቋንቋ ነው ። ሰው ሲፈጠር አንድ ሆኖ ሣለ ፣ በእኛ አገር ግን ሰው በዘሩ እንዲተያይ በመንግሥት እየተገደደ ይኸው ለ33 ዓመት በቅቷል ።

በዛሬዋ የትብብር ዓለም ውሥጥ ተጠቃሚ  እንዳይሆን በድንቁርና ዘራዊ ሥርዓት አደንዝዘው በህገ አራዊት ሥርዓት ለመግዛት የዛሬዎቹ ባለተራዎቹም ከትላንትናዎቹ ብሰው ህዝብን እርስ በእርሱ ለማጫረስ ያለማቋረጥ የጥፋት ቢላዋ በመሣል ለገዳዮች እያቀበሊ ነው  ።  ኢትዮጵያዊው በራሱ መንግሥታዊ የዘር ሥርዓት  እጅ እና እግሩ ታሥሯል ። እናም በጠመንጃ እየተነዳ የግዱን ሰው በሰውነቱ ሳይሆን ፈቅዶና ወድዶ ባልተወለደበት ዘሩ እየተፈረጀ  እየተፈጀ ነው ። …

ለመሆኑ ፣ እኔ የተለያየ ነገድ ደም ቢኖረኝ  ማነው በአማራ፣በትግሬ፣በሱማሌ፣በኦሮሞ፣በአፋርነት ወዘተ ። ሊመድበኝ የሚችለው ። አባቴ ከአፋርና ሱማሌ ፤ እናቴ ከኦሮሞ ፣ ከትግሬና አማራ ቢዛመዱ ፤  እኔን ይኽ የቋንቋ ፣ የነገድ ና የዘር  መንግሥት ማን ብሎ ይጠራኛል ?

 

ከቶ ወዴት እየሄድን ነው ?

በለው ! ምታው ! ጣለው  ! አሠቃየው ! ግደለው ! በማለት ሥልጣንን በምርጫ ሰጥቶ በህግ የበላይነት  አሥተዳድረኝ ያለውን የአንድ አገር   ህዝብ ፣ በነገድ ና ቋንቋ ፈርጆ ማሰር፣ማንገላታት ፣ መግደል ፣ ማሰቃየት   ሉሲፈራዊ ድርጊት አይደለም እንዴ ?

መንግሥት  ህዝብ በሰጠው  ሥልጣና ተጠቅሞ መልሶ እንዴት ህዝብን ያሰቃያል ? ይሄ ድርጊቱ ፕሮፌሰር መሥፍን እንዳሉት “ህገ አራዊትነት “ አይደለም እንዴ ? ህገ አራዊትነት ደግሞ በጠብመንጃ አሥገዳጅነት አገርን  የሚመሩ አምባገነን መንግሥታት ባህሪ  ነው ።

አምባገነኖች በህገ አራዊት ሥርዓተ መንግሥት ፤ ትላንት ለጥቅማቸው ቀጣይነት በመጨነቅ ብቻ    ንፁሐንን ያለርህራሄ ሲፈጁ ሲያስሩና ሲያሰቃዩ እንደነበር በታሪካችን በጥቁር መዝገብ መመዝገቡን እንዴት እንረሳለን ?

በህገ አራዊት የፖለቲካ ሥርዓት ከምንመራ ይልቅ ፣ “በህገ  ሰው የሚመራ መንግሥታዊ  ሥርዓት  “ ቢኖረን ኖሮ  በምንም ዓይነት መልኩ ዜጎችን በኢትዮጵያ ከሚኖሩበት ቀዬ ቤተሰቦቻቸው  ተገለውና ተዘርፈው እነሱ በሽሽት ተርፈው  ተፈናቅለው ቤት ተመፅዋች ምንዱባን አይሆኑም ነበር ?

በጥይት ዜጎችን ያለርህራሄ በዘረኝነት የተደራጀ ሽፍታ ዜጎችን በተዝናኖት የሚፈጅበት አንድ አገር  ኢትዮጵያ መሆኑ ዛሬ በዓለም ተረጋግጧል ።

በእኛ አገር   “ የክልሌ ልዩ ኃይል ከሌሎች ልዩ ኃይሎች ቀድሞ ወደ ህጋዊ አደረጃጀት አይዛወርም ። ከተዛወረም ወቅቱ አሁን አይደለም ። በኃይል ተወሥዶብኝ የነበረ መሬቴን በመሰዋትነቴ የራሴ አድርጌያለሁ ። ታሪክ የሚያረጋግጥልኝን ፣ መረጃና ማሥረጃ ያለውን “ የወልቃይቴ ና የራያን “ ህዝብ መኗሪያ ፣ ሥልጣንን መከታ በማድረግ ለትግራይ ክልል  መንግሥት መልሶ መሥጠት ህጋዊነት የለውም ። የወልቃይቴ ና የራያ ህዝብ መብት መጠበቅ አለበት ። በህገ መንግሥቱ መሠረት ። ሥለሆነም ራሱን ችሎ እንደ ሐረሪ ክልል ይሆናል እንጂ ተመልሶ ወደ ትግራይ ክልል አይገባም ። “ የሚለውን የአማራ ክልል ህዝብ በኃይል ጥያቄውን ለማዳፈን መግደልና መሰርን እንደመፍትሄ የሚቆጥር ህገ አራዊት መንግሥት ነው ያለው  ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አባይ፤ የኢህአዴግ አባል ነውን!? - ከአቤ ቶኪቻው

“ በህዝብ ብዛቴ     መጠን ታይቶ    የክልሌ ፖሊሥ ቁጥርም ከትግራይ ክልል  በ3 እጥፍ መብለጥ አለበት ። “ በማለት ህዝብ ጥያቄ ይዞ አደባባይ ሥለወጣ  ምላሹ ጥይት እና አሥር  ሲሆን እያየን ነው ።

ገዢው ፓርቲ ብልፅግና በህገ አራዊትነት አገርን እየመራ እንደሆነ   ፣  በራሱ ና በየክልሉ ያሉ ህግ አሥፈፃሚዎች በየቀኑ የሚፈፅሙት ህገ ወጥ ተግባር ይመሠክራል ። ጠ/ሚ አብይም “ እኛ ነን  ፤ አሸባሪ ። “ ብለው ገና ሥልጣን እንደያዙ ፣ ከ5 ዓመት በፊት የተናገሩትን ዛሬ ሳያሥቡት ዘው ብለው   በተግባር እየኖሩበት በመሆኑ ሥለ ህገ አራዊት አገዛዛቸው ዋቢ መጥራት አይጠበቅብኝም    ።

ዛሬ በኢህአዴግ ሰውነት ላይ ብልፅግና የሚል የህገ አራዊት  ቆዳ  አገዛዙ ለብሶል ፤ “ እበላ ባይ ካዲሬዎቸን ከቀበሌ ጀምሮ በማደራጅትም የሚቀጥለውን 13 ወይም 43  ዓመት ምርጫን በኮሮጆ ግልበጣ በማሸነፍ መንግሥት ሆኜ አገሪቱን እየበዘበዝኩ እቀጥላለው ብሎ ያሥብ ይሆናል ። “

እንዲህ አይነቱ የቀቢፀ ተሥፋ ህልመኝነት ምነጩ ፣ የነቃ እና የተደራጀ ህዝብ እንዳይኖር በማድረግ ፣ እሥርቤትን በማሥፋፋት  ኢትዮጵያን የዜጎቿ እሥር ቤት በማድረግ የሚሳካ ነው ። ለዚህም ይመሥላል  ለሥርዓት መከበር ፣ ለህግ የበላይነት ደንታ ቢስ የሆነው ጥቂቶችን በማበልፀግ ላይ በህቡ የሚሰራው መንግሥት ፣ ህዝብ ንቃተ ህሊናው የማያድግ ግዑዝ ፍጥረት እንደሆነ በማሰብ እሥር ቤትን እሥከ አዋሽ አርባ ያሥፋፋው ።

አበልፃጊ ነኝ የሚለው በተግባር ግን እያደኸየን ያለው መንግሥት   ያልተረዳው የዛሬ 50 ዓመት በፖለቲካው ንቁ ተሳትፎ የነበረው የዛን ጊዜው ወጣት ዛሬ በአብዛኛው ያለመኖሩን ነው ። ያለውም አርጅቷል ። ከፖለቲካው ጫዎታ ውጪ ሆኗል ። በእርሱ ምትክ እጅግ ምጡቅ ጭንቅላት ያለው ወጣት ትውልድ ተፈጥሯል ። ከጠቅላይ ሚኒስትሩ አሥር እጅ የሚበልጥ የአእምሮ ግዝፈት ያላቸው ሚሊዮን ወጣቶች  ዛሬ በአገራችን አሉ ። ይኽንን በቅንነት ተገንዝቦ ለእውነተኛ ለውጥ መነሳት ከብልፅግና ፓርቲ ይጠበቃል ።

አንዳችም ለውጥ ሳያመጡ ፣ ከቀድሞው ኢህአዴግ በባሰ መልኩ ፣ በአምባገነንነት ፣ በህገ አራዊት ሥርዓት  አገርን መምራት የብልፅግና ዘይቤ እየሆነ የመጣው ይምጣ ብሎ ብልፅግና ከኢህአዴግ ሰውነት ላይ ልብሱን ሳያወልቅ  መጓዙን ከቀጠለ ግን ጉዞው እጅግ አጭር እንደሚሆን የታወቀ ነው ።

የብልፅግናንን ቆዳ የለበሰው የቀድሞው የኢህአዴግ  መንግሥት  በህገ አራዊት ሥለሚመራ ነው ፣ በአገሪቱ ህገ መንግሥት መሠረት ክልሎች  ፖሊሥ ብቻ እንዲኖራቸው ያላደረገው ። በህገ አራዊት በሚመሩት ፣ የዛሬዎቹ ብልፅግናውች ናቸው የትላንትናዎቹ ኢህአዴጋዊያን ።  በሥልጣን ላይ  በነበሩበት አገዛዝ ወቅት በህገ መንግሥት የሌለ ልዩ ኃይል ተዋቅሯል ። ዛሬም  ፣   አገሪቱ ከዚህ “ ህገ አራዊት  የአገዛዝ መንገድ  “ ወጥታ “ በህገ  ሰው “  መንገድ በሥርዓት እየተጓዘች  እንዳልሆነ ከቤተመንግሥት ብዙም ሳይርቁ የሚፈፀሙ አፈናዎች ግድያዎች ና ዘረፋዎች ያሳብቃሉ  ።

ዛሬ አብይ መራሹ አበልፃጊው መንግሥት  ጥቂቶችን ለማበልፀግ ቆርጦ የተነሳው መንግሥቱ  ህገ አራዊትነቱን  ሥለተጠናወተው ነው     ።  የ 27 ዓመቱ  ህገ አራዊትነት እጅግ በገዘፈ ጭካኔ “ በልፅጎ “ ዳግም መከሰቱ ይኸንኑ ይመሰክርልናል   ። (  ነገሮችን ሁሉ ከባለሥልጣናቱ ጥቅምና ምቾት አንፃር    በማየት በከፋ ጨቋኝነት  እና ሰልቃጭነት  ሀገን በአውሬነት “ ብልፅግና ተብየው “ እየገዛት ነው  ። )

በተለይም በኦሮሚያ ክልል ሥርዓተ አልበኝነት በእንስሳዊ መልኩ   ነግሶ አንገት  እየቀላ ፤ ዜጎችን እንደ እንሥሣ በማየት አውሬው እየሰለቀጣቸው  ነው ። አማራ እንደ ታዳኝ እንሥሣ ተብይ ሆኗል ። ሰው ላልሆኑት አራዊት ባለሥልጣናት ። ከዚህ አንፃር አማራው አሁን ካሳየው የትግል አንድነት እጅግ የጠነከረ ትግልና ተጋድሎ ይጠበቅበታል ። የሰው ባህሪ ያልተፈጠረባቸው ፣  በህገ አራዊት አገራችንን የደም ምድር እያደረጓት ያሉትን  ሉሲፈራዊያንን  ለማሶገድ ግን የአማራው ክልል ህዝብ ትግል ብቻ በቂ አይደለም   ። …

ተጨማሪ ያንብቡ:  ‹‹ትንሹ›› ተስፋዓለም (ከጽዮን ግርማ)

ማንኛውም ዜጋ የቋንቋ መጠሪያውን ይዞ ይጠራ፣ አማራ ይሁን ኦሮሞ ፤ ትግሬ ይሁን አፋር ፤ ደቡብ ይሁን ሱማሌ ፤ ቤንሻጉል ይሁን  ጋምቤላ ፤ ሲዳማ ይሁን ሐረሬ …። በኢትዮጵያዊ ዜግነቱ ታፍሮና ተከብሮ ለመኖር ከፈለገ እነዚህን ጥቂት   እጃቸው በደም የጨቀየ ሉሳፈራዊያን  ከጫንቃው ላይ ማሶገድ ይጠበቅበታል  ።

በዚች አገር ህገ አራዊት በከፍተኛ ሁኔታ  በመንሰራፋቱ ዜጎች የመብላት ሳይሆን የመበላት እጣ ፈንታ ወድቆባቸዋል ። በየጊዜው እንደከብት እየተነዱ ዛሬወደ አምባገነኖች ማጎሪያ ካምፕ ይጓዛሉ ። ዛሬ በኢትዮጵያ ገደብ በሌለው ቸበር ቻቻ “ አለም በጎኔ አሐፈች “ እያሉ በየቀኑ የሚደሰቱት በፊደራልም ሆነ በክልል በሥልጣን ላይ ያሉት እና ጋሻ ጃግሬዎቻቸው ብቻ ናቸው ።

ከገበሬው እሥከ ወታደሩ የተጎሳቆለ ኑሮ ነው የሚኖረው ። ከላብ አደሩ  እሥከ የመንግሥት ሲቪል ሠራተኛው ኑሮን መቋቋም አቅቶት ለእንዲህ ዓይነቱ የኑሮ ውድነት ያበቃውን ህገ አራዊቱን አገዛዝ ሌት ተቀን እየረገመ ኑሮን በተአምር እየኖሩ ነው ።

በህገ አራዊትነት ተመርተው ፣ በማንአህሎኝነት ና   በእብሪት ግለሰቦች ሥልጣናቸውን መከታ በማድረግ የሚፈፅሙት ኢ ሰብዓዊ ድርጊት ነገ በወንጀል  ያስጠይቃል ። … ። አገርን በህገ አራዊት ሥርዓት ማሥተዳደር ትርፉ የከፋ ውድቀት ነው ።

“ ምን ታመጣለህ ? ተልባ  ቢንጫጫ በአንድ ሙቀጫ ! “ ማለትም  የህገ አራዊቶች የእብሪት  መንገድ ነው ።  በመንግሥትነትም የሚያሰነብት የተደላደለ መንገድ አይሆንም ። ከጉዞ አሰናካይ ሥውር መቀበሪያ ጉድጓድ  ያለበት ዘግናኝ መንገድ ነው ።

በህገ አራዊት መንገድ በመጓዝ በአማራ ክልል ውሥጥ የፌደራሉ መንግሥት ታላቅ ነውጥ ፣ አመፅ ፣ የንፁሐን መገደለን እና ሠላም ማጣትን መንግሥት እንዲከሰት በማድረግ “ ገገማ የሆነ ሉሲፈርነቱን “ አሥመሥክሯል ።   በዚህ ግጭት ፣ ሁከትና ሠላም ማጣት የምትጎዳው ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውን እንኳን እንዴት አያውቅም ? ወይሥ እያወቀ ኢትዮጵያን ለማጥፋት ተልኮ ተሰጥቶት በህቡ የሚንቀሳቀስ በዘረኝነት ያበደ መንግሥት ነው ያለን ? የሠከረ ህሊና ያለው ህገ አራዊትን የሚያራምድ  መንግሥት   እንዳለን ተግባሩ እያረጋገጠልን አይደለም እንዴ ?  …

ዛሬ ወደ አማራ ክልል የተሸጋገረው የህገ አራዊት ድርጊት ትላንት በትግራይ እብሪተኞች  የተፈፀመ ነበር ። ዘረኝነትን ፤ ጠባብነትን ፤ ትምክህትን  እና ሥግብግብነትን በህሊናቸው ያነገሱ የሕወሓት ሰዎች  በአምባገነንነት ያንን እጅግ ዘግናኝ የሆነ ጥቃት በአገር መከላከያ ሠራዊት ላይ በመፈፀም ግልፅ ጦርነት በኢትዮጵያውያን ላይ በመክፈታቸው አይደለም  እንዴ መቶ ሺዎች ፣ ኢትዮጵያን እንዴት ትደፍራላችሁ በማለት  ያንን ታሪክ በልዩ ሁኔታ የሚያወሳውን  መስዋዕትነት የከፈሉት ።

ዛሬም በግራና በቀኝ ያሉ ፣ የፊደራልና የክልል ሹመኞች ፤ ይኽንን ህገ አራዊትነት   ከህሊናቸው ካላሶገዱ ወይም እነሱ ካልተወገዱ እና እውነተኛ ፣ አሥተዋይ ፣ በተግባር ለዜጎች ሁለንተናዊ ብልፅግና የሚታትሩ የተግባር የፖለቲካ መሪዎች ፤ በኢትዮጵያ ህዝብ ይሁንታ ወደሥልጣን እሥካልመጡ ጊዜ ድረሥ በዚች ምድር የህግ የበላይነት ይሰፍናል ብለው ዜጎች አያስቡም    ። አንዳንዶችም “  የህ መንግሥት ጀዝቧል ። በየክልሉ አገሪቱን በእንደዚህ አይነት የምንግዴ አሥተዳደራዊ መንገድ የሚመሯት ጀዝባ   ጅላጅል ና  ጅላፎዎች ናቸው ።   እናም ለህዝብ የሚበጅ በተግባር የሚታይ ሥራ በመሥራት ፣ የዳቦ ና የፖለቲካ ጥያቄውን በአጭር ጊዜ ውሥጥ በተግባር የሚመልሱ ፣  የነቁ ና የበቁ  የፖለተካ ሰዎች በቅጡ  በመደራጀት ወደ ፖለቲካ ትግሉ በመምጣት አገራችንን ከውድቀት ሊያድኗት ይገባል   ። “ በማለት አምርረው ሲናገሩ ይደመጣሉ ።

እኛ ኢትዮጵያዊያን ለ 21 ኛው ክ/ዘ የሚመጥን የፖለቲካ ሥርዓት በአገራችን ማንበር  የምንችለው ፣ እንደበለፀጉት አገራት  የሰው ፖለቲካን ምርጫቸው ያደረጉ ፣ በህገ ሰው የሚመሩ አርቀው የሚያሥቡ ፣ ከሥግብግብነት የፀዱ ፣ በዕውቀትና በጥበብ የበለፀጉ ፖለቲከኞችና የፖለቲካ ፓርታዎች ሲኖሩን መሆኑንን እናውቃለን ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አቅጣጫችንንና ግባችንን የሳትነው መሠረታዊ ምክንያታችንን የሳትን እለት ነው - ጠገናው ጎሹ

ህገ አራዊት የሆነው አገዛዝ በሥግብግብነቱና በአይጠረቄነቱ ባይገባውም     ከበለፀጉት አገራት ጋር ይሚመሣሠል  ፣ ህገመንግሥት አፅድቀን በህግ የበላይነት ዜጎች እንዲተዳደሩ  በብርቱ እንፈልጋለን ።   ( በተባበረችው አሜሪካ እንኳ የሌለ  የዓለም ጎሣና ነገድ የለም ። ነገር ግን ዜጎች እንደ ዜጋ እንጂ እንደ ነገድ ና ጎሣ አይታዩም ።  የሚተዳደሩት በህግ የበላይነት ብቻ ነው ። ዜጎች ናቸው እኩል የዜግነት መብት አላቸው ።

አሜሪካ ፣ በጠንካራ ህግ አውጫዎች ፣ህግ ተርጓሚዎች ፣ህግ አሥፈፃሚዎች ና በአራተኛው ጠንካራ ተቋም በፕሬሥ ጣምራ ተቋማት ትመራለች ። በተለይም ነፃ ፕሬሥ በበለፀጉት አገራት ህግ እንዲከበርና ዜጎች ፍትህ እንዳይነፈጉ ነገርን ከሥሩ እየመረመረ የላቀ ህጋዊ እገዛ ሥለሚያደርግ ከሦሥቱ የታወቁ የመንግሥት ተቋማት በተጨማሪ “ አራተኛው መንግሥት “ እንደሆነ ታውቆ ይከበራል  ። በዚህ ነፃ እና እውነትን ይዞ የሚሟገት ፕሬሥ እየታገዘም መንግሥት በትክክለኛው የሰው የፖለታካ አመራር መንገድ በመጓዝ ዜጎችን ተጠቃሚ ያደርጋል ።

ዜጎች የግል አሥተያየታቸውን ያለ መሸማቀቅ በተለያዩ የፕሬሥ ውጤቶች  ላይ በየቀኑ ይሰጣሉ ። አፈና፣ወከባ፣እንግልት ቶርቸር የለባቸውም ። በህገ መንግሥታቸው ጥበቃ ይደረግላቸዋል  ( እንደ እኛ አገር በወረቀት ላይ ብቻ የቀረ ህግ የላቸውም ! የእኛ መንግስት ግን ለምን ተናገራቸሁ እና ፃፋችሁ  እንደ ታዲዮስ ታንቱ እና እንደ መስከረም አበራ  ወዘተ ።  የመሳሰሉትን ″ አሳብያን ″ በከንቱ ዛሬም አሥሮ እያሰቃየ ይገኛል ። እንደ ታዬ  ቦጋለ አይነቱን ደግሞ  ክፉኛ በማሰቃየት ፣ ጨካኝነቱ እንደ ጀብድ እንዲወራለት ያደርጋል  ። እንዴት ሰው በተፈጥሮ የታደለውን አንደበት  ዘግተህ ቁጭ በል ተብሎ በህዝብ ተመርጫለሁ በሚል መንግሥት ይታዘዛል ። ?

አዎ በአገራችን  የህገ አራዊትነት ሥርዓት የወለደው  ችግር አለ ። ጠቅላይ ሚኒሥቴር አብይ አህመድ ብቻቸውን አይፈቱትም ። የክልል ፕሬዝደንቶችም ለብቻቸው የሚፈቱትም አይደለም ። ሆኖም የመፍትሔው አካል  ካልሆኑ የችግሩ አካል አለመሆናቸውን በተግባር ለማሳየት ዝግጁ መሆን ይጠበቅባቸዋል ።  በሰላማዊ መንገድ የሽግግር መንግሥት የሚቋቋምበትን እና ይኼየህገ አራዊት ሥርዓት የሚቀየርበትን መንገድ ተባብረው ይጥረጉ።

በበኩሌ አመፅ፣ ሁከት ፣ግጭት ና ትርምሥ በዚህ ወቅት እንደማያሥፈልግ አምናለሁ ። የአብይ የመደመር መንገድም መክሸፉን ተገንዝቤለሁ ። በመደመር ብቻ የሚሆን ምንም አይነት የፖለቲካ ሥርዓት የለም ። የመደመር ትውልድ ብሎ ነገርም የለም ። የጠቅላዩን የጭፍለቃና የጎሣ ፖለቲካ አካሄድም የመደመር መንገድ ብዬ ልወስድላቸው እችላለሁ ።

በአናቱም ፣ የእሳቸው ቲዎሪ እንደ ደመራ የሚያነድ እንጂ የሚያበለፅግ ከቶም አይደለም ። በዘረኞች መንገድ ተጉዞ የበለፀገ አገር በዓለም ላይ የለምና !

ኢትዮጵያን  ዛሬ በመሥታወት ቤት ውሥጥ ያሥቀመጣት ይህ በህገ አራዊት መንገድ የሚጎዝ እጅ እግር የሌለው የመደመር መንገድ ነው ። ተደምሬለሁ ሥትለው አማራ ሥለሆንክ ቅንሼሃለሁ ይልሃል ።

ይኽንን የምለው ዛሬ የኦሮሞ ጦር ፣ የሱማሌ ጦር ፣ የደቡብ ጦር ፣ የትግሬ ጦር ፣ የአማራ ጦር ና የአፋር ጦር እየተባለ ፣ ዘራዊ ግጭትን በህገ አራዊትነት ተገፋፍቶ  ፣ በመከላከያ ውሥጥ ለመዝራት የሚጥሩ ፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎችን እያስተዋልኩ በመሆኑ ጭምር ነው ። ይኽ በግልፅ የመቀነስን መንገድ አጉልቶ ያሣያል ።    ይኽ በመደመር ሥም የሚካሄድ የህገ ጨራዊቶች የመቀነሥ መንገድ እጅግ አደገኛ  ነው ። በዜጎች እርብርብም  በአፋጣኝ የውድቀታችን ጉዞ መክሸፍ አለበት ።

ዛሬ መንግሥት እየተጎዘበት ያለው መንገድ ፣ የግብዝነት መንገድ ነው ። የእብሪት እና የትዕቢት  መንገድ ነው ። እናም እኛ ኢትዮጵያዊያን በዚህ አውዳሚ መንገድ መመራት አንሻም ። በቋንቋችን ፣ በባህላችን ሥም የሉሲፈርን መንግሥት ለማንበር እየተፈፀመ ያለውን ግልፅ የሆነ አገር አጥፊ ሤራንም አጥብቀን እንቃወማለን ።

 

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share