የመቃብር ጠባቂዎች ኃይል ትንሳዔውን አላስቀረውም፤ (ክርስቲያን ታደለ – የህ/ተ/ም/ቤት አባል)

በቅድሚያ በአገር ውስጥና በውጭ ለምትገኙ ለመላው ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያዊያት እንኳን ለ2015 ዓ.ም የስቅለትና የትንሳዔ በዓል በሰላም አደረሰን፤ አደረሳችሁ።

በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በታላቅ ድምቀት ከሚከበሩ በዓላት መካከል አንዱ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የስቅለትና የትንሳዔ በዓል ነው፡፡ ትንሳዔ የሚለው ቃል በክርስትና ኃይማኖት አስተምኅሮ መሰረት «መነሳት» ማለት ሲሆን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፥ አዳም በሳተ ጊዜ፥ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ብሎ በገባለት ቃል መሰረት በቀራኒዮ ተሰቅሎ በ3ኛው ሌሊት «መግነዝ ፍቱልኝ፥ መቃብር ክፈቱልኝ» ሳይልና የመቃብር ጠባቂዎች ኃይል ሳያግደው ሞትን ድል አድርጎ መነሳቱን የምናበስርበትና የምናስብበት የፍቅር፣ የደስታና የድል በዓል ነው።

የትንሳዔ በዓል ኃቅንና እውነትን ወግነው ለቆሙ ሁሉ ከሞት አጠገብ ሕይወት፤ ከመቃብር አጠገብ ትንሳዔ መኖሩን የምናስብበት፤ ፈጣሪ ለሰው ልጆች ያለውን ጥልቅ ፍቅር በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሞታችንን በሞቱ ድል አድርጎ የመዳንን ጸጋ ያገኘንበት፤ ስለ ፍቅር የሚከፈለውን መራራ መስዋእትነትን ያየንበት፤ ትኅትናንና ይቅር ባይነትን የምንማርበት ታላቅ በዓል ነው፡፡
ትንሳዔ የተስፋ መሟሸሽንና ሞትን የማሸነፍ በዓል ነው፤ በእለተ አርብ በጦር ጉልበታቸው የሚተማመኑ ሮማውያንና ሁሉን እናውቃለን በሚሉ ፈሪሳውያን የሀሰት ክስና ፍርድ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ መዋሉን ተከትሎ ፀሐይ የጨለመችበት፣ ጨረቃ ደም የለበሰችበት፣ ከዋክብት የረገፉበት እና ሞት የነገሰበት እንዲሁም ብዙዎች ተስፋ የቆረጡበት እለት ነበር፡፡ የጌታ ትንሳዔ በመከራና በጨለማ ውስጥም ሆነው ኃቅንና እውነትን ወግነው ለቆሙትና በጽናት ለጠበቁት ግን ከጨለመችው ፀሐይ ባሻገር አማናዊ ብርሃን፣ ደም ከለበሰችው ጨረቃ ባሻገር በደሙ የሚድኑ የሰው ልጆች መኖራቸውን፣ ከረግፉ ከዋክብት ባሻገር በሞቱ ሞትን ድል የሚነሳ አምላክ መኖሩን ያዩበት የድል እለት ነው፡፡
ዛሬ ላይ የዘመናችን መቃብር ጠባቂዎች የሕዝባችንን ፈተና በማብዛት እጅግ አስከፊ ለሆነ ሰቆቃ ዳርገውት ይገኛሉ። ይኼ ፈተና ትናንትም የነበረ፤ ዛሬም የቀጠለ፤…ነገ ግን በብርቱ የጋራ ትግላችን ወደ የሁሉም፥ በሁሉም የሆነች ፍትኅ የሰፈነባት፣ ነፃነት የለመለመባት፣ እኩልነት የተንሰራፋባትና ዴሞክራሲ የዳበረባት ኢትዮጵያን እውን በማድረግ በድል የምንደምቅበት ይሆናል። ነገ የሌላቸው አካላት ዛሬያችንን ቢያበላሹትም፤ ትናንት የሌላቸው ሰዎች ለትዝታ አልቦነት ደዌያቸው ፈውስ ዛሬያችንን ቢያጠለሹትም፥ ከአምላክ ጋር ወጀቡን በድል ተሻግረን በትንሳዔያችን እንደምቃለን። ይኼ ተጠየቅ የማይቀርብበት እውነታ ነው። በትናንታችን ብቻ ሳይሆን በነጋችንም ብሩኅ ተስፋ የሚቀኑ የጥፋት ማኅበርተኞች ከዚህም በላይ በብርቱ እንደሚፈትኑን ለኃቅ የቀረበ ግምት ነው። ፈተናው በበረታ ቁጥር ትንሳዔያችን እየቀረበ ለመሆኑ ማረጋገጫ ነውና፥ በጽናት እንበርታ።
የመቃብር ጠባቂዎች ኃይልና ብርታት የክርስቶስን ትንሳዔ እንዳላስቀረው ሁሉ፤ የዘመናችን መቃብር ጠባቂዎች የሕዝባችንን የፍትኅ፣ የነፃነት፣ የእኩልነትና የዴሞክራሲ ትንሳዔ የማርዘም ካልሆነ የማስቀረት አቅም ከቶውንም ሊኖራቸው አይችልም። ትንሳዔው እንደማይቀር፤ ያለስቅለትም ትንሳዔ እንደማይኖር እሙን ነው። ከተባበርን፣ ከተናበብን፣ ከተደማመጥንና በጋራ ጸንተን ቆመን የሕዝባችንን አቅም በሚገባ መጠቀም ከቻልን፥ በስቅለቱና በመከራው መጨረሻ ሕዝባችን ትንሳዔን ሲጎናፀፍ፥ የሕዝባችን ጠላቶች ደግሞ የኃፍረትን ማቅን ይለብሳሉ።
የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሳዔ በዓልን ስናከብር አንድነታችንን በማጠናከር፤ ቤት ንብረት ወድሞባቸው የተፈናቀሉትን፣ ተንከባካቢ የሚሹ አረጋውያንን፣ የጎዳና ተዳዳሪዎችን፣ የኑሮ ሁኔታ ያልተሟላላቸውን እንዲሁም የታመሙና በእስር ላይ የሚገኙ ወገኖቻችንን በመጠየቅ እንዲሆን የአደራ መልእክቴን አስተላልፋለሁ።
መልካም የስቅለትና ትንሳዔ በዓል!
ተጨማሪ ያንብቡ:  የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ ከኃላፊነታቸው ለቀቁ - አቶ ግርማ ዋቄ፤ እንዲመሩ ተሾሙ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share