April 2, 2023
17 mins read

የ አማራ ልዩ ሀይል  – አዲስ የተሰጠን የአታካሮ አጀንዳ

oromo 2 1 1
#image_title

oromo 2 1 1

መቼም  የኦህዴድ አገዛዝ ከነአጫፋሪዎቹ  በየእለቱ አዳዲስ  የአተካሮ አጀንዳዎችን  በመስጠት  እኛ አይናችንን ከኳሷ ላይ አንስተን ግራ ቀኝ ስንወዛገብ   እነርሱ አገር  የመበተን እና አማራን  የማሳደድ  ግባቸውን  በእቅዳቸው መሰረት ያለማንም ከልካይ የመተግበሩን ዘዴ ከተካኑበት ስንበትበት ብለዋል:: ሰተት ብለን ከወጥመዳቸው በመውደቅ እኛም ለእኩይ ተግባራቸው ስኬት የየድርሻችን በመወጣት ላይ እንገኛለን:: በደብረ ብርሃን ከወለጋ በግፍ የተፈናቀሉ አማሮች የድረሱልን ጩኸት ዛሬም አላባራም:: በአዲስ አበባ  አማራዎችን የማፅዳት ዘመቻው በተጠናከረ መልኩ ቀጥሎ  እንዳውም  ሁለት አብያተ  ክርስትያናትን በማፍረስ ጭምር እንደቀጠለ ዛሬ ከቤተክህነት አካባቢ የወጡ መረጃዎች ያሳያሉ::  በንፁሃን አማራዎች ላይ የሚፈፀመውን ግፍ  ተከታትለው የሚዘግቡ ጋዜጠኞች  እየተሳደዱ ወደ ኦህዴድ ግዞት እየተጋዙ ይገኛሉ:: አስቀድመው የተጋዙትም አበሳቸውን እያዩ ” ሰው ናፈቀን” እያሉ ይጮኻሉ::

እኛስ? እኛማ … አብዛኞቻችን ያለፉትን ሁለት ሳምንታት ” ዮኒ  ማኛን ማን ወደ አገር ቤት አመጣው ?” እያልን  ስንነታረክ እዚህ ደርሰናል::  እነ አቶ አያልቅበት  ዛሬም ” የአማራ ልዩ ሀይል  መበተን አለበት” የሚል አጀንዳ አስይዘውን  አማራን የማሳደድ  ስራቸውን በማቀላጠፍ ላይ ይገኛሉ:: …ሰውዬው ወደ ጏንደር  ያመራው  አሁን እውነት በተሌቪዥን መስኮት እንዳሳየን ጏንደሬይቱን ሚስቱን የፋሲልን ግንብ ሊያስጏበኛት ወይስ ሌላ  ተልእኮ አንግቦ?? እንዲያው ዝም ብሎ ሽው የሚልብኝ ጥርጣሬ ነው… የሰኔውን ጭዳ የማድረግ ልምዱን ወደ  መጋቢት  አዙሮት  እንዳይሆን… ለማንኛውም  ወደ ተነሳሁበት ነጥብ ልመለስ…

የአማራ ልዩ ሃይል

በዘመነ ህውሀት  ካልተሳሳትኩ  በሶማሌ ክልል አሀዱ ብሎ የጀመረው  የልዩ ሀይልን የማደራጀት  ስራ ሌሎች ክልሎችም ተቀባብለውት አማራ ክልል መድረሱ የቅርብ አመታት ትዝታ ነው:: በወቅቱ ክልሎች የልዩ ሀይልን የማደራጀት ህገ መንግስታዊ መሰረት የላቸውም  የሚል ጠንካራ ትችት ከየአቅጣጫው ይሰነዘር የነበረ ቢሆንም  ህውሃትዬ ግን  እንዲህ እንደአሁኑ ክፉ ቀን  ቢመጣ  ራሷን ለመከላከልም ሆነ ሌሎቹን ወደ የእርስ በርስ  ጦርነት  አዙሪት ለመዶል  a recipe for disaster መሆኑን ጠንቅቃ ስለምታውቅ  ተቺዎችን ጆሮ ዳባ ልበስ ብላ  ክልሎች የየራሳቸውን ልዩ  ሃይል መዋቅር የማደራጀቱን ስራ እንዲገፉበት አደረገች::

ከጥቂት አመታት በፊት ከአዲስ አበባ – ድሬዳዋ  የነበረኝ በረራ በጅጅጋ  ዞሮ  ድሬዳዋ የሚያርፍ ነበር:: በዚህ ጉዞዬ ከጎኔ ተቀምጦ ከነበረው የሶማሌ ክልል ተወላጅ ጋር  ጭውውት ጀመርን.. አፍታም ሳይቆይ ጨዋታችን በወቅታዊው የፖለቲካ ትኩሳት ላይ  አተኮረ:: ሰሞነኛ ርዕስ የነበረውን “ልዩ ሃይል” አንስተን  እያወጋን ቆይተን የበረራው  ወዳጄ የጉዞው መዳረሻ  ወደሆነችው ጅጅጋ  እየተቃረብን ነበር እና ጨዋታችንን ስናሳርግ እንደዋዛ  የለበጣ ፈገግታውን እየቸረኝ እንዲህ  አለ –

” የሶማሌ ልዩ ሃይል የነብስ ወከፍ መሳሪያውን እስከ አፍንጫው ታጥቋል:: የሚቀረን ከባድ መሳሪያ  ብቻ   ነው:: እናንተ ሀበሾቹ  ( ሰሜነኞቹን ማለቱ መሰል) በቅርቡ እርስ በርስ  መናጨታችሁ ስለማይቀር በቀላሉ ነፃነታችንን እናውጃለን…”

በስራው ባህሪ ምክንያት  ወደ ሶማሌ ክልል በተደጋጋሚ  ይጏዝ የነበረ የልብ ወዳጄ እንዳጫወተኝ  በወቅቱ ወደ ሶማሌ ክልል  ያደርግ በነበረው ጉዞ  በየኬላው ከነበሩ  የክልሉ  ልዩ  ሃይሎች  ጋር  የነበረው  የፊት ለፊት አጋጣሚ  ወደ ሌላ ሁለተኛ አገር የተጏዘ  ያህል  ይሰማው እንደነበር   ያጫወተኝን አስታውሳለሁ::

እንደው የሶማሌ ክልሉን ከግል ገጠመኜ ተነስቼ ለአብነት ያህል አነሳሁ እንጂ በሁሉም ክልሎች የተደራጁት ልዩ ሀይሎች  ያለቅጥ የተሰጣቸው ተጠያቂነት የሌለበት ስልጣን እና ሃይል ያላሰጋው የዚች ሀገር “ወዴት?” የሚያሳስበው ዜጋ ነበር ለማለት በእጅጉ ይቸግረኛል::

በያ ሰሞን በኦሮሚያ  ክልል ለተቃውሞ ወደ ጏዳና የወጡ ወጣቶች  ደም ሲፈስ  ” አግአዚ” ን መወንጀሉ  ቀሎ ተገኘ እንጂ  እውነተኛው ግፍ ፈፃሚ ማን እንደነበር በየከተማው እና ቀበሌው በወቅቱ የነበሩ ነዋሪዎች የሚያውቁት ነው::

የክልሎች ልዩ ሀይልን ያለልኬት እያደራጁ መሄድ ምን ይዞ እንደሚመጣ እና ምን እየተደገሰ እንደነበር በጥቂቱም ያልህ በጨረፍታ ያሳየን የሶማሌ  ክልል እና ኦሮሚያ ክልል ልዩ ሃይሎች ያደርጉት የርስበርስ ጦርነትና አስከትሎት የመጣው ዳፋ ነበር::

ሰውዬው ስልጣኑን ሲረከብ ከመጀመሪያ  ውሳኔዎቹ መካከል የክልል  ልዩ ሀይልን dissolve  ማድረግ መሆን  አለበት የሚለው ጥያቄ እና ግፊት የተገላቢጦሽ ነበር መልሱ!

የትግራይ ክልል ልዩ ሃይል – ወደ  ትግራይ መከላካያ ሀይልነት (TDF) አደገ ተመነደገ:: የህውሃት እና ደጋፊዎቿ መከታ እና የኩራት ምንጭ ሆነ::

የኦሮሚያ ልዩ ሃይል – በ አስር ሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችን መልምሎ በማሰልጠን ወደ ልዩ ሃይሉ ከመቀላቀሉም በላይ ከኤርትራ በረሀዎች የተመለሱ የ ኦ.ነ.ግ ታጣቂዎች ከፊሉ ይህንኑ ሀይል እንዲቀላቀሉ ሆነ::

የአማራ ልዩ ሃይል – በወቅቱ በትግራይ ክልል በህውሃት አማካይነት በፍጥነት እና በስፋት ሲካሄድ የነበረው የትግራይ ልዩ ሃይልን በሰው እና በመሳሪያ የማደራጀት ዘመቻ ስጋት የፈጠረባቸው  የአማራ ክልል ልዩ ሃይል አዛዥ ጄነራል አሳምነው ፅጌ ም  በፊናቸው የክልላቸውን ልዩ ሃይል የማስፋት ሩጫ ያዙ :: ይህ ሩጫቸው ከኦህዴድ አገዛዝ ጥርስ ያስገባቸው ጄነራል አሳምነው  ፅጌ  ወሎ ላይ  የአብይ አህመድን ትችት እና ዘለፋ ካስተናገዱ ከወራት በሗላ  “መንግስት በመገልበጥ” ተወንጅለው ተገደሉ::ሗላ ላይ ጌታቸው ረዳ  እንዳረዳን ” ሬሳውን እንጂ ከነነፍሱ እንዳታመጡት” ብሎ የ ኦ.ህ.ዴ.ዱ አብይ አህመድ  ቀጭን ትዕዛዝ እንዳስተላለፈ ነበር ::

Long story short…እንደሚሉት ፈረንጆቹ…ዛሬ የሀገሪቱ  ፖለቲካዊ   ተለዋዋጭ ነባራዊ ሁኔታ political dynamics  በተለይም  የገዢው ኦህዴድ  ድብቅ  አጀንዳውን ለማስፈፀም  በስርዓት አልበኝነት እና ማን አለብኝነት የሚጏዝበት ርቀት ይኸም በህዝቡ  የፈጠረው የህልውና ስጋት እና ጥርጣሬ  ” ምነው በፈረሰ!” እየተባለ ሲረገም የነበረውን የልዩ ሃይል አደረጃጀት የህልውና መሰረት ተደርጎ እንዲታመን አድርጎታል::

የ” ለራስ ሲቆርሱ … ” ፖለቲካ

ባለፉት ሁለት ቀናት የአማራ ልዩ ሀይል ይፍረስ አይፍረስ በሚለው  ጉዳይ  ዙሪያ  ከሊቅ እስከ ደቂቅ ሁሉም  የመሰለውን አስተያየት እና ትንታኔ ሲሰናዘር  ውሏል:: የኔ ትኩረት  የኪሊማንጃሮ  ጉዞው በድንገት “የሰላም መናኝ ”  ያደረገው የመደመር ካልኩሌተሩ “ፈጣሪ”  የአራት ኪሎው ዘዋሪ  የዛሬ ስድስት አመት  በሚኔሶታ በተካሄደ ስብሰባ ላይ ያደረገው ንግግር ነው:: ይህ ንግግር የተደረገው  በወቅቱ  በቢሾፍቱ  የኢሬቻ በአል አከባበር ላይ ቁጥራቸው በመቶ  የሚቆጠሩ የበአሉ ታዳሚዎች ህይወታቸው ባለፈ በማግስቱ ነው:: የ”መደመር ካልኩሌተሩ ቀማሪ” ንግግሩን የሚጀምረው በሽግግር ስርዓቱ   ኦሮሞ ምን መምሰል አለበት ምን አይነት የኦሮሞ መንግስት ነው መቋቋም ያለበት የሚለው ተጠንቶ አንድ ዶክመንት እንድሚዘጋጅ  ይህም በኦሮሞ ጠበቃዎች አለም አቀፍ ማህበር  እንደሚዘጋጅ እና ለንደን ላይ በሚካሄድ ጉባኤ ይፋ እንደሚሆን በማብሰር ሲሆን ንቅናቄያቸው በአለም አቀፍ ዲፕሎማሲው መስክ እያስገኘ ያለውን ፍሬ በንፅፅር ሲገልፅ ” በዲፕሎማሲው መስክ  እኛ እንደሚዳቋ ስንፈጥን አበሾቹ ግን እንደ ኤሊ እየተንቀረፈፉ ነው” በማለት በዚሁ ስብሰባ  ሀዘኑን እና ድጋፉን ( solidarity)ለማሳየት ተገኝቶ የነበረውን አበበ ገላውን  ተሳልቆበት ነበር:: ጆሮውን ቢቆሩጡት ኦሮምኛ የማይሰማው አበበ ገላውም  ለተዘለፈበት ንግግር አጨብጭቦ መውጣቱ  ብዙዎችን አስፈግጏ ነበር::  የንግግሩ ፍሬ ሀሳብ የኦሮሞን መከላከያ ሃይል በመገንባት ዙሪያ ነው የሚያጠነጥነው ቃል  በቃል ባይሆንም የንግግሩ አንኳር:-

“….በኦሮሚያ ክልል  ከ500 ሺህ በላይ የነፍስ ወከፍ መሳሪያ ይገኛል…የኛ ነው በውስጥም ይሁን በውጪ ካሉ ሀይሎች ጋር ለመከባበር  መሳሪያ በገፍ በእጃችን አስገብተን ጠንካራ  የኦሮሞ መከላከያ  ሀይል በመገንባት ነው….ይሄ ደግሞ ዝም ብሎ በወሬ አይመጣም በተግባር እንጂ…!”

የሚል ነው:: ይህንን ንግግር ለመቀንጨብ ያስገደደኝ  ታድያ አጅሬ ሰሞኑን አዘጋጅቶ በትኖታል  በተባለው ፅሁፍ” ልዩ ሀይል ይበተን “የሚል  ምክክር  የሚመስል  መመሪያ ለኦህዴድ መስጠቱን መስማቴ ነው :: ይህ ምክር ለምን ዛሬ ብሎ መጠየቅ  ግድ የሚል ይመስለኛል:: ምክንያታዊ ግምቶች

መከላከያ ሀይሉ ላይ የተደረገውን” ሪፎርም” መቼም  ከተመስገን ደሳለኝ የተሻለ እርቃኑን ያሰጣ የለም – ማጥራቱ ተሳክቷል

የ ኦሮሚያ ልዩ ሃይል በገፍ እየመለመለ ከማሰልጠን በተጨማሪ በሀገር መከላከያ ደረጃ እስከ አፍንጫው መታጠቁ እንዲሁም ልዩ በሀገር መከላከያ ሰራዊት ደረጃ የሚሰጡ ስልጠናዎች የወሰደ ና እየወሰደ ያለ  መኑ ይታማል

የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት  አስር ሺዎች የሚቄጠሩ ወጣቶችን አሰልጥኖ እና አስታጥቆ በስንቅም በትጥቅም የተደራጀ ሰራዊት  ተፈጥሮአል

አጅሬ የዛሬ ስድስት አመት አካባቢ ያስቀመጠው ግብ መቶ በመቶ የተሳካ ይመስላል:: ስለዚህ ቀጣዩ ምዕራፍ ያለተቀናቃኝ በሀገሪቱ ልዕለ ሀያል ለመሆን ከኦህዴድ ቁጥጥር  ራቅ ያሉትን ወይም ውጪ የሆኑትን  የተደራጁ የታጠቁ ሀይሎች  ትጥቅ ማስፈታት  ለነገ የማይባል የቤት ስራ ነው:: ስለዚህ ልዩ ሀይልን የማፍረስ ዘመቻው አሀዱ ብሎ በአማራ ክልል ይጀምራል::

ኦህዴድ  ክልሉን እና እራሱን ለማስከበር እና የበላይነቱን ለማረጋገጥ በየመስኩ  ጦር እያሰለጠነ እያስታጠቀ እያደራጀ  አማራ የህይወቱን እስትንፋስ ህልውናውን ለማቆየት  መታጠቅ የማይችልበት ምን ምድራዊ ምክንያት አለ?

አማራ ራሱን እና ቤተሰቡን በህይወት የማቆየት ተፈጥሮአዊ  መብት እና ግዴታ የለበትም?

ህውሀት የአማራ ልዩ ሃይል ትጥቁን ካልፈታ እኔም አልፈታም ብላለች አሉ:: የአማራ ልዩ ሃይል ህውሃት ላለማጥቃቷ ምን መተማመኛ አግኝቶ ትጥቅ ይፍታ?

 

 

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

blood sucker Abiy
Previous Story

በነካ እጅዎ! – አንዱ ዓለም ተፈራ

Killer abiy 1 1 1 1
Next Story

የመጨረሻው፣መጨረሻ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop