March 31, 2023
6 mins read

በኦሮሚያ ክልል በሸገር ከተማ እየተካሄደ ያለው ቤቶችን የማፍረስ እና በግዳጅ ማስነሳት እርምጃ የመኖሪያ ቤት አልባነትን አባብሷል

337527208 607354677982210 4134910670882552941 n 1 1
#image_title

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ/ኮሚሽኑ) በአዲስ አበባ ከተማ ዙሪያ የኦሮሚያ ክልል ውስጥ በቅርቡ በአዲስ መልክ በተደራጀው የሸገር ከተማ አስተዳደር የቤቶች ፈረሳ እና በግዳጅ ማስነሳት (Demolition and Forced Eviction) እየተከናወነባቸው ካሉ አካባቢዎች መካከል ቡራዩ፣ ሰበታ፣ ለገጣፎ ለገዳዲ፣ መነ አብቹ እና በዙሪያው ከሚገኙ አካባቢዎች ቤቶቻቸው የፈረሱባቸው ሰዎች በግል እና በቡድን ለኮሚሽኑ ያቀረቡትን አቤቱታ ተከትሎ ከየካቲት 27 ቀን 2015 ዓ.ም. ጀምሮ ክትትልና ምርመራ ሲያደርግ ቆይቷል። በዚህም መሠረት ለኮሚሽኑ ቅሬታ ያቀረቡ ሰዎችን፣ የሚመለከታቸውን የከተማ አስተዳደር እና የጸጥታ አካላት በማነጋገር፤ በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር ቤቶችን የማፍረስ እና በግዳጅ የማስነሳት ሂደቱ የሚከናወንበትን ሁኔታ እንዲሁም ቀደም ሲል የፈረሱ ቤቶችን የመስክ ምልከታ በማድረግ መረጃ እና ማስረጃ አሰባስቧል።

337527208 607354677982210 4134910670882552941 n 1 1

ለኢሰመኮ ቅሬታቸውን ያቀረቡት ሰዎች ለኮሚሽኑ ሲያስረዱ በየአካባቢው ከቀድሞ/ነባር ባለ ይዞታዎች ቦታ ወይም ቤት በመግዛት ኑሮ መሥርተው ሲኖሩ የነበሩ መሆናቸውን፣ በየአካባቢው ከሚገኙ ማኅበራዊ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት የውሃ እና የመብራት አገልግሎት ተጠቃሚ የነበሩ መሆናቸውን፣ ለተለያዩ የአካባቢው የልማት ሥራዎች እንደ ማንኛውም ማኅበረሰብ ክፍያዎችን ሲከፍሉ መቆየታቸውን በመጥቀስ መኖሪያ ቤቶቻቸው ያለ በቂ ቅድመ ማስጠንቀቂያ ከሕግ አግባብ ውጭ እንደፈረሱባቸው ይገልጻሉ።

ኢሰመኮ ያነጋገራቸው የሸገር ከተማ ኃላፊዎች በበኩላቸው የከተማ አስተዳደሩ እንደ አዲስ መመሥረቱን ተከትሎ “ሕጋዊ የይዞታ ማረጋገጫ የሌላቸውን” ግንባታዎች በማፍረስ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ እንዲሁም የአየር ካርታን ጨምሮ ሕጋዊ የይዞታ ማረጋገጫ የሌላቸው፣ ከነባር የአርሶ አደር ይዞታ ውጪ የሆኑ እና በተለይም ከ2005 ዓ.ም. በኋላ የተገነቡ ቤቶች እንዲፈርሱ በተወሰነው መሠረት የተከናወነ መሆኑን፣ ቤቶቹን የማፍረስ ሂደቱን በተመለከተም ከቤቶቹ ባለቤቶች ጋር በክፍለ ከተማ፣ በወረዳ እና በቀበሌ ደረጃ ውይይት ተደርጎ በቂ ግንዛቤ እንዲፈጠር በማድረግ እና በሚፈርሱ ቤቶች ላይ በቅድሚያ ምልክት ከተደረገ በኋላ እራሳቸው ግንባታውን እንዲያፈርሱ ጊዜ የሚሰጣቸው መሆኑን፣ በተሰጣቸው ጊዜ ውስጥ ግንባታውን ሳያነሱ የቀሩ ሰዎች ካሉ ግንባታዎችን በአፍራሽ ግብረ ኃይል እንደሚያፈርሱ፣ የፈረሰውን የግንባታ ቁሳቁስም በሕግ የተቀመጠውን አሠራር በመከተል ወደ ከተማ አስተዳደሩ ተወስዶ ውሳኔ የሚሰጥበት መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ኃላፊዎች ለኮሚሽኑ ጨምረው አስረድተዋል።

338047845 791364059005842 1911361756956828298 n 1 1

ኢሰመኮ በጉዳዩ ዙሪያ በለገጣፎ ለገዳዲ፣ በሰበታ አካባቢ ፉሪ እና ለቡ ተክለሃይማኖት እንዲሁም በቡራዩ ገፈርሳ ኖኖ አካባቢዎች በመዘዋወር ቀደም ሲል የፈረሱ እና የማፍረስ ተግባሩ እየተከናወነ የነበረባቸውን አካባቢዎች ተመልክቷል፡፡ ኮሚሽኑ በለገጣፎ ለገዳዲ ክፍለ ከተማ በመገኘት እየፈረሱ የነበሩ ቤቶችንም ለመመልከት ችሏል። በምልከታው የቤት ማፍረሱ እና በግዳጅ ማስነሳቱ በግብረ ኃይል እየተከናወነ እንደነበረ እና በቦታው ከፖሊስ፣ ልዩ ኃይል እና ሚሊሻ አባላት በተጨማሪ ሌሎች ዱላ የያዙ ሲቪል ሰዎች እንደነበሩም ተመልክቷል።

የክትትልና የምርመራ ሥራው ሙሉ በሙሉ ባይጠናቀቅም እስካሁን በተገኙት መረጃዎች እና ማስረጃዎች መሠረት የቤት ማፍረስ እና በግዳጅ የማንሳት እርምጃው ከሰብአዊ መብቶች አኳያ የታዩበትን ክፍተቶች እና ሊወሰዱ የሚገባቸውን የማስተካከያ እርምጃዎች በተመለከተ ኢሰመኮ የሚከተለውን ይገልጻል።

በዓለም አቀፍ ሕግ እና የሰብአዊ መብቶች መርሆች መሠረት በግዳጅ ማንሳት (Forced Eviction) ማለት አንድን ሰው ወይም ቤተሰብ ወይም ማኅበረሰብ ከሚኖርበት ቤት ወይም ቦታ ላይ ያለ ፈቃዱ፣ አማራጭ መፍትሔ ሳይሰጠው ወይም ሕጋዊ ጥበቃ ሳይደረግለት በጊዜያዊነት ወይም በዘላቂነት በኃይል አስገድዶ ማንሳትን የሚመለከት ነው።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

68878853 1 1
Previous Story

የታገሰ ጫፎ ሌባ ጣት፤ ያማራ ውርደት ዘላለማዊ ምልክት

welkeit 1 1
Next Story

ወልቃይትና ራያ በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ስር…..የኦሮሚያ ብልጽግና አመራሮች ዘረፋ….የህወሀት መሪዎች ተፈቱ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop