October 8, 2022
4 mins read

ጨው ለራስህ ስትል አትጣፍጥ! – በላይነህ አባተ

salt

ጨው ሆይ!

ድልህ አዋዜን ባሳማርክ፣ ቀይ አልጫውን ባጣፈጥክ፣
በጥርስ መንጋጋ ታኝከህ፣ በምላስ ጪልፋ ተላውሰህ፣
በማንቁርት ክርን ተገፍተህ፣ የጉረሮን ቦይ ተሻግረህ፣
በከርስ ወፍጮ ተፈጨህ፣ በእባብ አንጀትም ተበላህ፡፡

ምግቡን በአሻቦ ጣዕም አርገህ፣ ውሀንም በአንካር አጣፍጠህ፣
የተራበውን በመገብክ፣ የተጠማውን ባጠጣህ፣
የኮሰመነ ባፋፋህ፣ የመነመነ ባወፈርክ፣
ደም ግፊት አምጪ እያሉ፣ ይሉኝታ ቢሶች ኮነኑህ፡፡

ሙያ የለሹን ሰው ባረክ፣ የመብል ጣዕምን ባስተማርክ፣
ውሻ እማይነካውን ምግብ፣ ጣት አስቆርጣሚ ባደረክ፣
ሕዝብን ተንሰሳ በለየህ፣ ተሳር ጋጪነት ባወጣህ፣
እጅህ እንደ አማራ ሕዝብ፣ አመድ የሚያፍስ ሆኖብህ፣
“ለራስህ ስትል ጣፋጭ ሁን፣ አለዚያ ድንጋይ ነህ” አሉህ፡፡

እንግዲህ ተልድምህ ተማር፣ መጣፈጥ መጣም ይቅርብህ፣
ዓለም ከንቱ እንደሆነች፣ እናት ደግ እንደማትወድ ይግባህ፡፡

በልተው እንዳያጠፉህ፣ ጠጥተው እንዳይጨርሱህ፣
አትብሉኝ አትጠጡኝ በል፣ እንደ እንቆቆ እሬት አምርረህ፡፡

እንኳንስ ተእሬት ተእንቆቆ፣ ተአሸዋ ድንጋይም ተማር፣
ሲፈጩህ ወፍጮውን አንክት፣ ሲያኝኩህ ጥርስንም ስበር፡፡

ሲውጡህ እነቅ ጉርንቦን፣ ወርደህም ከርስ ሆድን ተርትር፣
በደም ተሻግረህ ኩላሊት ቀትል፣ ጣራ እስቲነካ ደም ግፊት ጨምር፣
ልብ ሥራ በዝቶባት እስክትደክም፣ በመጨረሻም ሲው እስክትል፡፡

ጨው ሆይ እባክህ ንቃ፣ የሳመ መስሎ ሱሳም አይላስህ፣
መላእክት ተእግር ብረት ውስጥ፣ ሳጥናኤል ተዙፋኑ ላይ ይታይህ፣
ሰባራው ሚዛን አይጣልህ፣ ዓለም ፍርደ ገምድሏ አታጥፋህ፡፡

ምድሪቱ ለሥጋ ለአካል ላትበጅህ፣ ሰማዩም ለፀድቅ ለምቾት ላይሆንህ፣
አንተ ተምድር ስጠፋ፣ እንደ ወንጅ ስኳር ተልሰህ፣
ህሊና ይሉኝታ ቢሱን፣ ጨው ላሹን ማፋፋት ይብቃህ፡፡

እነ ማተብ የለሾች፣ በልተው ጠጥተው የሚያሙህ፣
ገንፎ ጨምረው ሊበሉህ፣ ለከብቶቻቸው ሊያጠጡህ፣
በባልጩት ብትር ሰባብረው፣ አራት አንካሮች ሊያደርጉህ፣
እንደ ውቃቢ ሲጠጉህ፣ እንደ እርኩስ መንፈስ ሊወሩህ፣
እንደ ቀጋ እሾህ ተዋጋ፣ ዝናሮችህን አጥብቀህ፡፡

በጅል በከብቱ ተጎርሰህ፣ በሽግናሞችም ታኝከህ ተመዋጥ፣
በፈርሳም ጨጓራ ተፈጭተህ፣ ተአንጀት ቱቦ ውስጥ ተመስመጥ፣
ሲመክሩህ ስማ ድፍን ጨው፣ ለራስህ ስትል አትጣፍጥ፡፡

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)
መስከረም ሁለት ሺ አስራ አምስት ዓ.ም.

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Angargachew
Previous Story

አንዳርጋቸው ጽጌ ሣይቀር የሚሣለቅበት አማራ ይህችን የጨለማ ዘመን ካለፈ ምንም አይል – ሥርጉት ካሣሁን (አዲስ አበባ)

310373593 5553234168094670 5902404330092376771 n
Next Story

በካይሮ የተዘረጋው ሰሞነኛ ህወሃታዊ ሴራ ከግብፅ፣ ሩዋንዳ እና ሱዳን እስከ ደደቢት በረሃ – በእስሌማን አባይ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop