“በሥመ አብ! ” በሉ የኑሮ ውድነቱ የማይቀለበስ አደጋ ሊያሥከትል ይችላልና! – መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

“ በስመአብ ! በስመአብ! … በ3000 ብር በዲግሪ የተመረቀ ተማሪን መቅጠር ? ማለት ምን ማለት ነው ?” አማተቡ አንጋፋው ኢኮኖሚሥት ፣ ኢየሱስ ወርቅ ዛፉ ።  በሸገር 102 ኤፍ ኤም  ቢዝነስ ዜና ላይ ፣በወቅቱ የኑሮ ውድነት ጉዳይ አሥተያየት እንዲሰጡ   በአዘጋጁ የዲግሪ ምሩቅ ደሞዝ በአንዳንድ የመንግሥትና የግል ድርጅቶች 3000 በመሆኑ በዚህ ኑሮ ውድነት እንዴት ኑሮን መግፋት ይችላል ? በማለት ሲጠየቁ ።  መልሳቸውን በመገረም ድምፀት ቀጠሉ ። ” … መኖሪያ ቦታ እንዴት ያገኛል ? …በ3000 ብር …ምን አላት 3000 ብር  ? …ገበያ ወጥተኽስ ምን ትገዛለች ? … በቢዝነሱ ዓለም በእኔ ሴክተር የጠቀስከውን እጥፍ ብር ነው የሚከፈለው ፣  ለዲግሪ ተመራቂ ። ( በዜሮ ዓመት   የሥራ ልምድ  ። )  …” አሉ ። የ3000 ብር ደሞዝተኛ ባለ ዲግሪ በኢትዮጵያ መኖሩን ያለማወቃቸው አያሥገርምም።

የሸገሩ 102 ኤፍ ኤም ጋዜጠኛ ያነሳው ጉዳይ ግን ወቅታዊ እና በእውነት ላይ የተመሠረተ  ነው ። የመንግሥትና የግል ድርጅቶች የግል ትምህርት ቤቶችን ጨምሮ ለዲግሪ ተመራቂ በዜሮ ዓመት ልምድ ሲቀጥሩ ከአራት ሺ ከፍ አይሉም ። አራት ሺ ምናምን ላይ ይቆማሉ ። በየመሥሪያ ቤቱ እና በየኢንዱስትሪ ፖርኩም ያለው ክፋያ ለዲግሪ ምሩቃን 6000 አይሞላም ። ( የመንግሥት የልማት ድርጅቶች በአንፃራዊነት ቢሻልም ፣ 2000 ብር ተከፋይ የለም ማለት አይቻልም። አንዳንዶቹ ከሚያመርቱት ምርት ፋይዳ አንፃር ፋብሪካዎቻቸውን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመገንባት የበለጠ ምርታማ በማድረግ የሠራተኞችን ደሞዝ ማሻሻል ይጠበቅባቸዋል     ።)

ወዳጄ እርግጥ የኑሮ ውድነቱ በራሱ በሥመአብ ! ብለህ እንድታማትብ ያሥገድድሃል ። ለምን ብትል በየቀኑ የምትሰማው የምግብ ሸቀጦች ላይ እና እህሎች ላይ ጭማሬ ነውና ! ያውም የተጋነነ ። እና  በ3000 ብር  ደሞዝ አዲስ አበባ ውስጥ ቤት ከሌለህ ተቀጥረህ ለመሥራት እንዴት ትችላለህ ?  የተሻለች ቅልብጭ ያለች  አንድ አልጋ የምታዘረጋ ቤት  ከ3000 ብር በታች አታገኝም ። ያውም በደላላ ጥረት ኮሚሽን ከፍለህ ነው ቤቷን የምታገኘው ። በዚህ ወጪ ላይ የምግብ ፣ የታክሲን ፣ የንፅህና መጠበቂያን ወጪ ጨምርበት ። ታዲየስ ? ይሄ “ በሥመ አብ ! “ አያሰኝም ትላለህ ?????

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያ አንድነት ፈተናዎች - ከአበበ ከበደ

ለምሳሌ ያህል በዚህ ደሞዝ  የመምህርንን ድካም በጥልቀት  አሥበው  እስቲ ? ቁልጭ ፣ ቁልጭ የሚሉ አሣዛኝ የነገ ተሥፋዎችን ዓይን ማየቱ በራሱ የህሊና ፈተና ውሥጥ የሚጥል ትውልድን የመቅረፅ ሥራ ነው የሚሰሩት ። እነዚህ ታደጊ ወጣቶች እና ወጣቶች     ወደ ቀድሞ ፊደል ቆጠራህ ዞር ብለህ  እንድትመለከት የሚያሥገድዱህ ናቸው   ። እናም እነዚህን አሣዛኝ ፣ ልበ ንፁሆች  ዕውቀት ለመመገብ ሣትሰለች  ደጋግመህ ማሥረዳት ይጠበቅብሃል ። በዚህ የተነሳ ጉሮሮህ ይደርቃል ። ይኽንን ግን ማንም አይገነዘብልህም ። በዛ ላይ የጠመኔው ብናኝ ፣ ወይም የቀለሙ ሽታ አለ ። የግል ተምህርት ቤት ባለቤቶች ቢያንሥ ምሣና አንድ ሌትር ውሃ ቢችሉህ መልካም ነበር ፣ እንደ መንግሥት ትምህርት ቤት አይከፍሉህምና በዚህ ቢክሱህ ትወድ ነበር ። ሲያምርህ ይቀራል ። እናም የጠዋቱን የትምህርት ክፍለ ጊዜ  ጨርሰህ ምሣህን ከተማሪዎችህ እጅግ ያነሰ ዝቅተኛ ምግብ ( ዳቦ በሻይ ) ምሳህን በልተህ የከሰዓቱን ፔሬድ እንደምንም ትደመድማለህ ። ከዛም በእግርህ የቤትህን መንገድ ትያያዘዋለህ ። …

የደሞዝ አነሥተኝነት ፣  አሥተማሪውን እንዴት ምሥኪን እንዳደረገው አሥተዋልክ ?  እንደርሱ ሁሉ   ፣ በካምፕ የማይኖረውን ወታደር ፣ ፖሊስ፣ዳኛ እና ጠበቃ የሚከፈለው ደሞዝ  ከወቅቱከመሠረታዊ ፍላጎት ወጪው ጋር ባለመሄዱ እጅግ እንደጎዳው  አሥተውል ። የዚህ ህግ አሥከባሪ  አካል መጎዳት  ደግሞ እጅግ መጥፎ ሁኔታን ይከስታል ። … ። በዚህ ጉዳይ ብዙ ማለት አልፈልግም ። ይሁን እንጂ በእነዚህ ተቋማት የሚሰሩ ዝቅተኛ ደሞዝ ብቻ የሚከፈላቸው ፣ ቤትና ጥቅማጥቅም የሌላቸውን በማሥተዋል የዋጋ ውድነቱን በመንተራስ፣ አሥቸኳይ የደሞዝ ማሥተካከያ ማድረግ አሥፈላጊ እንደሆነ መንግሥት የሚገነዘብ ይመሥለኛል ። …

ተጨማሪ ያንብቡ:  ወንጌልና ወንጀል፤ ቁራንና ቅጥፈት፤ ምን አገናኛቸው ?!  ( አሥራደው ከካናዳ )

እሺ ተራው ህዝብስ ምን ይሁን ? ዘይት ፣ በርበሬ፣ ስኳር ፣ዛሬ ደግሞ ሽንኩርት እና ቲማቲም እየናፈቀው ይኑር ? ከተሜው ፣ ሽሮ እየበጠበጠ በውድ ዋጋ እንጀራ እየገዛ በቀን አንድ ጊዜ እየተመገበ አንጀቱ እያረረ ወደ ፈጣሪው ያንጋጥ  ? በገጠር ከተሞች አካባቢ ደግሞ ከዚህ የባሰ ጎሥቋላ ኑሮ አለ ና የበቆሎ ቆሎ  ቆርጥሞ እሥከመቼ ይኖራል ? …ወደ ጎደናስ ልጆቹ እሥከመቼ ይወጣሉ ?

ይህን እውነት ፣ የመንግሥት ባለሥልጣናት ካላወቃችሁ እወቁ ። የምትበሉትን በምግብ ጠረጴዛችሁ ላይ የተቆለለውን ቡፌ ከእሱ አንድ እፍኝ የበቆሎ ቆሎ ጋር እሥቲ ለአፍታ አሥተያዩ ?   በዕዝን ልቦናችሁ ሥትመለከቱ ምን ተሰማችሁ ? … የምትመገቡትን ምግብ ትታቸው  ፣ ወደ ውጪ በመውጣት ሥውር ቦታ ፈልጋችሁ አለቀሳችሁ ? ወይስ “ የ40 ቀን እድሉ ነው :: ” በማለት ተሳለቃችሁበት  ? …

ይኽ የ40 ቀን ዕድል ጉዳይ አይደለም ። የተቀበላችሁት የማሥተዳደር ጉዳይ እንጂ ! በዚህ ደሃ ህዝብ ሥም ነው ከፍታ ላይ የተገኛችሁት ። ቢያንስ ለራሳችሁ ፡፡ …  ልታሥቡለት ፣ ህይወቱ እንዲቀየር ልትረዱት የሚገባው ነበረ ይኽ ምስኪን ሆኖም አስተዋይ በለአገር ። ዜጋን የማገልገል ግዴታችሁ  ነው ።

በእውነቱ ይኽንን ግዴታውን የሚያውቅ ሹመኛ  የበዛ ቢሆን ኖሮ ፣ ይኽቺ አገር በአጭር ጊዜ ሀብታም ትሆን ነበር ። ( ሰማህ  እዛ ማዶ ያለኸው  ? ጭቁንን ፣ ደሃውን ፣ ባለአገሩን  እየገደልክና እየዘረፍክ እንዴት ለህዝብ ቋሜያለሁ ፤ በማለት አፍህን ሞልተህ ትናገራለህ ? በባርነት ያልኖረውን የትግራይ ህዝብ አንተ በሐሰት ትርክት ከማነው ነፃ የምታወጣው ?  ) ህዝብን    አገለግላለው  የሚል ሁሉ ህዝብን በተጨባጭ ካላገለገለ እና ሥልጣንን መክበሪያና መንደላቀቅያ ካደረገ አጠቃላይ ህዝቡን መጥቀም እንዴት ይቻለዋል ?????????

የትም ክልል ብትሄዱ ያለው ችግር ይኽ እኮ  ነው ። “ በሥልጣን መገልገል እንጂ ማገልገል  የለም ። “ ባመዛኙ ። ከቀበሌ ጀምሮ በየምክንያቱ ፣ በሰበብ አሥባቡ ፣ በመታወቂያ ሽያጭ  ሣይቀር ኪሱን የሚያሣብጥ ባለሥልጣንን ነው የምታስተውሉት  ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሌባ ዓይነ ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ - ሰማነህ ታምራት ጀመረ፤ ኦታዋ፤ ካናዳ

ዛሬም ሥልጣን የባለሥልጣናት  መበልፀጊያ ሆኗል ። የሰፊው ህዝብ መበልፀጊያ “ ፀረ _ ሌብነት ፖሊስ “ የብልፅግና  ፖርታ መቼ ይሆን የሚያወጣው ?  ይኽ ቆራጥ የሆነ እርምጃን የያዘ የፀረ ሌብነት ፖሊስ በአሥቸኳይ ወጥቶ ካልተተገበረ በስተቀር የኑሮ ውድነቱ እጅግ እየባሰ ይሄዳል ። ሌቦቹ አንድ ኪሎ ሥጋ 2000 ቢገባ ጉዳያቸው አይደለም ።  የሥርቆት ብር ሥላላቸው ለምን ለነሱ ሲል  5000 አይገባም ?  ሥለ ጥራጥሬ እና አትክልት ውድነትም መስሚያ ጊዜ የላቸውም ። እነሱ ሁሌም በፊሽታ እና ሀብት በማከማቸት ተጠምደዋልና …

ደሞዝተኛው ግን  ኑሮ ክበበው ገዳ ከዓመታት በፊት እንደ ቀለደው ቀልድ ሆኖበታል ።

ክበበው በበላተኛው ብዛት ሥለጠፋው በሬ ነበር የቀለደው ።

” …ወደፊት ለልጆቻችን ስናወራ ፤ አንድ በሬ የሚባል እንስሳ ነበረ ፤ እርሱን ተቃርጠን ሥጋውን በቢላዋ እየመተርን በማጥሚጣ እያጠቀስን  እንዲህ እያደረግን  እንበላ ነበር ። ” ብለን እናወራለን ። በማለት   ። የሚገርመው በሬው ሳይጠፋ ፣ አሁን እና ዛሬ ፣ ትንቢቱ መፈፀሙ ነው ።ዛሬ ለብዙሃኑ ኢትዮጵያዊ ብዙ አሥፈላጊ ዕለታዊ ምግቦች  እጅግ ተወደውበት ፣ በአይኑ ከመመገብ በዘለለ መላ ቅዱሱ እንደጠፋበት ይታወቃል ።

ደሞዝተኛው ሁሉ ፤ ባንክን እና አየር መንገድን ሳይጨምር ፤  ደሞዙ እዛው ነው ። ጡረተኛው ደሞዙ በአንድ ብር ከፍ አላለም ። ። ገበያው ግን በየቀኑ  እሳት እየሆነ  ነው ። ከተሜው  ትላንት እንደልብ የሚበለው ዳቦ በሻይ እንኳን በሥኳሩ  ውድነት ሳቢያ ህልም ሆኖበታል ።

ይኽ እውነት ነው ። ተረት ተረት አይደለም ። መንግሥት ለሚያሥተዳድረው ህዝብ በመጨነቅ ፈጥኖ ካልደረሰ እና ገብያውን ለማረጋጋት ካልሰራ ፤ የኑሮ ውድነቱ  የማይቀለበሥ አደጋ ያመጣል የሚል ሥጋት ይኽ ፀሐፊ አለው ።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share